በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ልጆቻችሁን አስተምሩ

የመርዳት ፍላጎት ነበራት

የመርዳት ፍላጎት ነበራት

በጣም የታመመ ሰው አይተህ ታውቃለህ?— ይህን ሰው ለመርዳት አንድ ነገር ማድረግ ብትችል ኖሮ ደስ ይልህ ነበር?— ይህ ሰው ከሌላ አገር የመጣ ወይም ከአንተ የተለየ ሃይማኖት ያለው ቢሆንስ? ጤንነቱ እንዲሻሻል ለመርዳት ፈቃደኛ ትሆን ነበር?— ከ3,000 ዓመታት ገደማ በፊት በእስራኤል ትኖር የነበረች አንዲት ትንሽ ልጅ አንድን ሰው ጤንነቱ እንዲሻሻል ረድታ ነበር። እስቲ በዚያን ወቅት ምን እንደተፈጸመ እንመልከት።

ይህች ልጅ በምትኖርበት በጥንቷ እስራኤልና በአቅራቢያዋ በምትገኘው የሶርያ ግዛት መካከል በተደጋጋሚ ጦርነት ይደረግ ነበር። (1 ነገሥት 22:1) በአንድ ወቅት ሶርያውያን ወደ እስራኤል በመምጣት ይህችን ትንሽ ልጅ ማርከው ወደ አገራቸው ወሰዷት። በዚያም ይህች ልጅ፣ የሶርያ ንጉሥ ጦር አዛዥ የነበረው የንዕማን ሚስት አገልጋይ ሆነች። ንዕማን በሥጋ ደዌ በሽታ ተይዞ ነበር፤ ይህ በሽታ ደግሞ የአንድ ሰው ሥጋ ከሰውነቱ ላይ እየተቀረፈ እንዲወድቅ የሚያደርግ ነው።

ይህች ልጅ ለንዕማን ሚስት፣ ባሏ ከበሽታው እንዴት ሊፈወስ እንደሚችል ነገረቻት። ‘ንዕማን በሰማርያ ያለውን የይሖዋን ነቢይ ኤልሳዕን ሄዶ ቢያገኘው እኮ ይፈውሰው ነበር’ አለቻት። ንዕማን ይህች ልጅ ስለ ኤልሳዕ የተናገረችውን ነገር ሲሰማ ይህ ነቢይ በእርግጥ ሊፈውሰው እንደሚችል አመነ። በዚህም የተነሳ ንዕማን ከሶርያው ንጉሥ ከቤን ሀዳድ ፈቃድ ከጠየቀ በኋላ ከተወሰኑ አገልጋዮቹ ጋር በመሆን ኤልሳዕን ለማግኘት 150 ኪሎ ሜትር ገደማ የሚሆነውን ረጅም ጉዞ ተያያዘው።

ንዕማንና አገልጋዮቹ በመጀመሪያ የእስራኤል ንጉሥ ወደሆነው ወደ ኢዮራም ሄዱ። ከዚያም ለንዕማን እርዳታ እንዲደረግለት የሚጠይቀውን የንጉሥ ቤን ሀዳድን ደብዳቤ አሳዩት። ሆኖም ኢዮራም በይሖዋም ሆነ በነቢዩ ኤልሳዕ ላይ እምነት አልነበረውም። ኢዮራም፣ ቤን ሀዳድ ከእሱ ጋር ለመዋጋት ሰበብ እየፈለገ እንዳለ ሆኖ ተሰማው። ኤልሳዕ ግን ጉዳዩን ሲሰማ ለንጉሥ ኢዮራም “ሰውየው ወደ እኔ ይምጣ” አለው። ይህ ነቢይ፣ አምላክ ንዕማንን ከያዘው መጥፎ በሽታ የመፈወስ ኃይል እንዳለው ለማሳየት ፈልጎ ነበር።—2 ነገሥት 5:1-8

ንዕማን በፈረሶቹና በሠረገሎቹ ታጅቦ ኤልሳዕ ቤት ደረሰ፤ ነቢዩም “ሂድና በዮርዳኖስ ሰባት ጊዜ ታጠብ፤ ሥጋህ ይፈወሳል” ብሎ እንዲነግረው መልእክተኛ ላከበት። ንዕማን ይህን ሲሰማ ተቆጣ። ኤልሳዕ ወደ እሱ መጥቶ በመዳሰስ ከሥጋ ደዌ በሽታው እንደሚፈውሰው አስቦ ነበር። ይሁን እንጂ ወደ እሱ የመጣው መልእክተኛው ነበር! በመሆኑም ንዕማን ተቆጥቶ ወደ አገሩ ለመመለስ ጉዞ ጀመረ።—2 ነገሥት 5:9-12

ከንዕማን አገልጋዮች አንዱ ብትሆን ኖሮ ምን ታደርግ ነበር?— የንዕማን አገልጋዮች እንዲህ አሉት:- “ነቢዩ ከዚህ ከበድ ያለ ነገር እንድታደርግ ቢነግርህ ኖሮ አታደርገውም ነበርን? ታዲያ፣ ‘ታጠብና ንጻ’ ቢልህ ምኑ አስቸገረህ?” ንዕማንም ምክራቸውን በመስማት “በዮርዳኖስ ሰባት ጊዜ ብቅ ጥልቅ አለ፤ ሥጋውም እንደ ትንሽ ልጅ ሥጋ ሆነ።”

ንዕማንም ወደ ኤልሳዕ ተመልሶ “እነሆ በእስራኤል አገር እንጂ በዓለም ሁሉ ሌላ አምላክ አለመኖሩን ተረድቻለሁ” አለው። በተጨማሪም ከይሖዋ በቀር “ለማንኛውም አምላክ የሚቃጠል ወይም ሌላ መሥዋዕት [እንደማያቀርብ]” ቃል ገባለት።—2 ነገሥት 5:13-17

አንተስ እንደዚህች ትንሽ ልጅ፣ ሰዎች ስለ ይሖዋና ማድረግ ስለሚችላቸው ነገሮች እንዲያውቁ መርዳት ትፈልጋለህ?— ኢየሱስ ምድር ላይ በነበረበት ወቅት በሥጋ ደዌ የተያዘ አንድ ሰው በእሱ በማመን ‘እኔን ለመርዳት ብትፈልግ እኮ ልታነጻኝ ትችላለህ’ አለው። ኢየሱስ ምን ምላሽ እንደሰጠው ታውቃለህ?— “ፈቃዴ ነው” አለው። ይሖዋ ንዕማንን እንደፈወሰው ሁሉ ኢየሱስም ሰውየውን ከበሽታው አዳነው።—ማቴዎስ 8:2, 3

ይሖዋ ሁሉም ሰዎች ጤናማ ሆነው ለዘላለም መኖር የሚችሉበት አዲስ ዓለም እንደሚያዘጋጅ ታውቃለህ?— (2 ጴጥሮስ 3:13፤ ራእይ 21:3, 4) ከሆነ ስለ እነዚህ አስደናቂ ነገሮች ለሰዎች መናገር እንደምትፈልግ ምንም ጥርጥር የለውም!