በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የወደፊቱን ጊዜ ማን ሊያውቅ ይችላል?

የወደፊቱን ጊዜ ማን ሊያውቅ ይችላል?

የወደፊቱን ጊዜ ማን ሊያውቅ ይችላል?

“እኔ አምላክ ነኝ፤ . . . የመጨረሻውን ከመጀመሪያው፣ ገና የሚመጣውንም ከጥንቱ ተናግሬአለሁ።” —ኢሳይያስ 46:9, 10

ሁኔታዎች በፍጥነት በሚለዋወጡበት በዚህ ጊዜ የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና የማኅበራዊ ጉዳይ ተንታኞች ታሪክንና የጊዜያችንን ሁኔታ በማጥናት ስለ ወደፊቱ ጊዜ ለመተንበይ ይሞክራሉ። ሌሎች ደግሞ የወደፊቱን ጊዜ ለማወቅ ስለሚጓጉ ወደ ኮከብ ቆጣሪዎች ወይም ወደ መናፍስት ጠሪዎች ይሄዳሉ። እንዲህ ያሉ ሰዎች አብዛኛውን ጊዜ፣ ሁኔታው እንዳሰቡት ስለማይሆን ማዘናቸው አይቀርም። ይሁን እንጂ የእኛን ጨምሮ የቤተሰቦቻችንና የዚህ ዓለም ዕጣ ምን እንደሚሆን ፈጽሞ ማወቅ አይቻልም ማለት ነው? የወደፊቱን ጊዜ በትክክል ሊያውቅ የሚችል ይኖር ይሆን?

ሁሉን ቻይ አምላክ የሆነው ይሖዋ፣ ለነቢዩ ኢሳይያስ በነገረው በመግቢያው ላይ ባለው ሐሳብ ላይ የወደፊቱን ጊዜ የማወቅ ችሎታ እንዳለው ገልጿል። አምላክ በኢሳይያስ በኩል የጥንት እስራኤላውያን ከባቢሎን ግዞት ነፃ እንደሚወጡና ወደ አገራቸው ተመልሰው ኢየሩሳሌምንና ቤተ መቅደሱን ዳግም እንደሚገነቡ አስቀድሞ ተናግሯል። ይህ ትንቢት ምን ያህል ዝርዝር ጉዳዮችን ይዟል? ኢሳይያስ፣ ባቢሎንን ድል የሚያደርገው ንጉሥ ስሙ ቂሮስ እንደሚባል ከ200 ዓመታት ገደማ በፊት በትክክል ተንብዮአል። ከዚህም በተጨማሪ ኢሳይያስ፣ ቂሮስ ከተማዋን ከጥቃት ለመከላከል ያገለግል የነበረውን የኤፍራጥስን ወንዝ አቅጣጫ እንደሚያስቀይር በመግለጽ ንጉሡ የሚጠቀምበትን የጦር ስልት ገልጿል። ሌላው ቀርቶ ኢሳይያስ ግዙፍ የነበረው የከተማዋ በር ቂሮስ በቀላሉ ድል ማድረግ እንዲችል በቸልታ ሳይዘጋ ክፍት ሆኖ እንደሚያገኘው አስቀድሞ ተናግሯል።—ኢሳይያስ 44:24 እስከ 45:7

የሰው ልጅ እንደ አምላክ የወደፊቱን ጊዜ የማወቅ ችሎታ የለውም። ጠቢቡ ንጉሥ ሰሎሞን “ነገ በሚሆነው አትመካ፤ ቀን የሚያመጣውን አታውቅም” በማለት ጽፏል። (ምሳሌ 27:1) ሰሎሞን የተናገረው ይህ ሐሳብ በዛሬው ጊዜም ይሠራል። አንድ ሰው ስለ ዓለማችን የወደፊት ሁኔታ ይቅርና እሱ ራሱ ምን እንደሚያጋጥመው እንኳ ማወቅ አይችልም። አምላክ ከሰዎች የተለየ የሚያደርገው ምንድን ነው? የሰዎችን ባሕርይና ዝንባሌ ጨምሮ ፍጥረታቱን በሚገባ ያውቃል። አምላክ አስፈላጊ ሆኖ ሲያገኘው እያንዳንዱ ግለሰብም ሆነ መላው የሰው ዘር ወደፊት ምን እንደሚያጋጥመው በትክክል ማወቅ ይችላል። ከዚህም በተጨማሪ አምላክ የወደፊቱ ሁኔታዎች የሚያስከትሉትን ውጤት ለመቆጣጠር የሚያስችል ገደብ የለሽ ኃይል አለው። አምላክ፣ አንድ ነገር ይፈጸማል ብሎ በነቢያቱ አማካኝነት ትንቢት ከተናገረ ‘የባሪያዎቹን ቃል ይፈጽማል፤ የመልእክተኞቹንም ምክር ያጸናል።’ (ኢሳይያስ 44:26) እንዲህ ማድረግ የሚችለው ደግሞ ይሖዋ አምላክ ብቻ ነው።

ኢሳይያስ የኖረው መሲሑ ኢየሱስ ከመወለዱ ከ700 ዓመታት ገደማ በፊት ነው። ያም ሆኖ ኢሳይያስ ስለ መሲሑ አመጣጥ ተንብዮአል። ይሁንና ከ18ኛው መቶ ዘመን ጀምሮ የመጽሐፍ ቅዱስ ተቺዎች የኢሳይያስ መጽሐፍ ትክክለኛ ስለመሆኑ ጥያቄ ሲያነሱ ቆይተዋል። እነዚህ ተቺዎች፣ የኢሳይያስ ትንቢት የተጻፈው ሁኔታው ከተፈጸመ በኋላ በመሆኑ አስቀድሞ የተነገረ አይደለም በማለት ይከራከራሉ። ይሁንና ይህ ትክክል ነው? በ1947 የኢሳይያስ መጽሐፍ፣ በሙት ባሕር አቅራቢያ ባለ ዋሻ ውስጥ ከሌሎች ጥንታዊ ጥቅልሎች ጋር ተገኘ። ምሁራን፣ ይህ ቅጂ የተዘጋጀው ይመጣል ተብሎ የተነገረለት መሲሕ ወይም ክርስቶስ ከመወለዱ ከመቶ ዓመታት ቀደም ብሎ መሆኑን አረጋግጠዋል። አዎን፣ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ወደፊቱ ጊዜ በትክክል ይተነብያል!

ኢሳይያስና ሌሎች የመጽሐፍ ቅዱስ ጸሐፊዎች ስለ ወደፊቱ ሁኔታዎች አስቀድመው የተናገሩት በራሳቸው ጥበብ አልነበረም። ከዚህ ይልቅ “በመንፈስ ቅዱስ ተመርተው” ነው። (2 ጴጥሮስ 1:21) በቀጣዮቹ ርዕሶች ላይ ኢሳይያስ፣ ስለ ኢየሱስ ምድራዊ ሕይወት አስቀድሞ የተናገራቸውን አንዳንድ ዝርዝር ጉዳዮች እንመለከታለን። ከዚያም ኢየሱስና ደቀ መዛሙርቱ ስለ ዘመናችን እንዲሁም ስለ ወደፊቱ ጊዜ የተናገሯቸውን ትንቢቶች እንመረምራለን።