በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ሙታን ስላላቸው ተስፋ

ሙታን ስላላቸው ተስፋ

ከኢየሱስ ምን እንማራለን?

ሙታን ስላላቸው ተስፋ

ኢየሱስ ቢያንስ ሦስት ሰዎችን ከሞት በማስነሳት ሙታን ተስፋ እንዳላቸው አሳይቷል። (ሉቃስ 7:11-17፤ 8:49-56፤ ዮሐንስ 11:1-45) ሙታን ስላላቸው ተስፋ ለመረዳት እንድንችል ሰዎች የሚሞቱት ለምን እንደሆነና ሞት መቼ እንደጀመረ ማወቅ አለብን።

የምንታመመውና የምንሞተው ለምንድን ነው?

ኢየሱስ ኃጢአታቸውን ይቅር ሲልላቸው ሰዎች ከሕመማቸው ይፈወሱ ነበር። ለምሳሌ ያህል፣ ሰዎች ሽባ የሆነ ሰው ወደ እሱ ባመጡ ጊዜ ኢየሱስ እንዲህ ብሏል፦ “‘ኀጢአትህ ይቅር ተብሎልሃል’ ከማለትና ‘ተነሥተህ ሂድ’ ከማለት የቱ ይቀላል? ነገር ግን የሰው ልጅ በምድር ላይ ኀጢአትን የማስተስረይ ሥልጣን እንዳለው እንድታውቁ ነው ብሎ፣ ሽባውን፣ ‘ተነሣ! ቃሬዛህን ይዘህ ወደ ቤትህ ሂድ’ አለው።” (ማቴዎስ 9:2-6) ስለዚህ ሰዎች የሚታመሙትና የሚሞቱት በኃጢአት ምክንያት ነው። ኃጢአትን የወረስነው ደግሞ ከመጀመሪያው ሰው ከአዳም ነው።—ሉቃስ 3:38፤ ሮሜ 5:12

ኢየሱስ የሞተው ለምንድን ነው?

ኢየሱስ ኃጢአት አልነበረበትም። በመሆኑም መሞት አይገባውም ነበር። ሆኖም ኢየሱስ በእኛ ምትክ በመሞት ለኃጢአታችን ዋጋ ከፍሏል። ደሙ ‘ስለ ብዙዎች የኀጢአት ይቅርታ እንደሚፈስ’ ተናግሯል።—ማቴዎስ 26:28

በተጨማሪም ኢየሱስ “የሰው ልጅ እንዲያገለግሉት ሳይሆን፣ ለማገልገልና ነፍሱንም ለብዙዎች ቤዛ አድርጎ ለመስጠት መጥቶአል” ብሏል። (ማቴዎስ 20:28) ኢየሱስ የከፈለውን ዋጋ “ቤዛ” በማለት ጠርቶታል፤ ምክንያቱም ቤዛው ሰዎችን ከሞት ባርነት ነፃ ያደርጋል። በተጨማሪም “[እኔ] ሕይወት እንዲኖራቸውና እንዲትረፈረፍላቸው መጥቻለሁ” ሲል ተናግሯል። (ዮሐንስ 10:10) ሙታን ስላላቸው ተስፋ የተሟላ ግንዛቤ ለማግኘት አሁን ስላሉበት ሁኔታም ማወቅ ይኖርብናል።

ሰው ሲሞት ምን ይሆናል?

ኢየሱስ፣ ወዳጁ አልዓዛር በሞተበት ወቅት ሰው ሲሞት ምን እንደሚሆን ተናግሯል። ኢየሱስ፣ ለደቀ መዛሙርቱ “‘ወዳጃችን አልዓዛር ተኝቶአል፤ እኔም ከእንቅልፉ ላስነሣው [ወደ ቢታንያ] እሄዳለሁ’ አላቸው። . . . ደቀ መዛሙርቱ ግን እንቅልፍ ስለ መተኛቱ የተናገረ መሰላቸው። ስለዚህም በግልጽ እንዲህ አላቸው፤ ‘አልዓዛር ሞቶአል።’” በዚህ መንገድ ኢየሱስ ሙታን አንቀላፍተው እንዳሉና ምንም እንደማያውቁ ግልጽ አድርጓል።—ዮሐንስ 11:1-14

ኢየሱስ፣ ወዳጁን አልዓዛርን ያስነሳው ከሞተ ከአራት ቀን በኋላ ነበር። ያም ሆኖ አልዓዛር፣ ሞቶ በቆየባቸው ቀናት ውስጥ ምን እንዳጋጠመው ስለመናገሩ የሚገልጽ ዘገባ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አናገኝም። አልዓዛር በሞት አንቀላፍቶ በቆየባቸው ቀናት በድን ስለነበር ምንም የሚያውቀው ነገር አልነበረም።—መክብብ 9:5, 10፤ ዮሐንስ 11:17-44

ሙታን ምን ተስፋ አላቸው?

ሙታን ዳግም ሕያው ሆነው ለዘላለም የመኖር አጋጣሚ ያገኛሉ። ኢየሱስ ‘መቃብር ውስጥ ያሉ ሁሉ ድምፁን [የኢየሱስን ድምፅ] ሰምተው የሚወጡበት ጊዜ እንደሚመጣ’ ተናግሯል።—ዮሐንስ 5:28, 29

የትንሣኤ ተስፋ የአምላክ ፍቅር መግለጫ ነው። ኢየሱስ እንዲህ ብሏል፦ “በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስከ መስጠት ድረስ ዓለምን እንዲሁ ወዶአል።”—ዮሐንስ 3:16፤ ራእይ 21:4, 5

ተጨማሪ ማብራሪያ ለማግኘት ትክክለኛው የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ምንድን ነው? * የተባለውን መጽሐፍ ምዕራፍ 6⁠ን ተመልከት።

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.15 በይሖዋ ምሥክሮች የተዘጋጀ።