በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ለሁሉም ነገር ጊዜ አለው

ለሁሉም ነገር ጊዜ አለው

ለሁሉም ነገር ጊዜ አለው

መጽሐፍ ቅዱስ “ለሁሉም ነገር ጊዜ አለው፤ ከሰማይ በታች ለሚከናወነው ለማንኛውም ነገር ወቅት አለው” ይላል። ይህንን ሐሳብ የጻፈው በጥንት ዘመን የኖረው ጠቢቡ ንጉሥ ሰለሞን፣ ለመወለድና ለመሞት ብሎም ለመገንባትና ለማፍረስ እንዲሁም ለመውደድና ለመጥላት ጊዜ እንዳለው አክሎ ተናግሯል። ሰለሞን ሐሳቡን ሲደመድም “ሠራተኛ ከጥረቱ የሚያገኘው ትርፍ ምንድን ነው?” ብሎ ነበር።—መክብብ 3:1-9

አንዳንዶች ከላይ ያለውን ጥቅስ በሚያነቡበት ጊዜ መጽሐፍ ቅዱስ ‘ሁሉም ነገር አስቀድሞ ተወስኗል’ ብሎ እንደሚያስተምር ይሰማቸዋል፤ በሌላ አባባል በዕድል ማመንን መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚደግፍ ያስባሉ። በእርግጥ ይህ እውነት ነው? መጽሐፍ ቅዱስ በሕይወታችን ውስጥ የሚያጋጥሙን ነገሮች በሙሉ አስቀድመው እንደተወሰኑ ያስተምራል? “ቅዱስ መጽሐፉ ሁሉ በአምላክ መንፈስ መሪነት የተጻፈ” በመሆኑ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የምናነበው ነገር በሙሉ እርስ በርስ የሚስማማ መሆን አለበት። እንግዲያው የአምላክ ቃል በሆነው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኙት ሌሎች ጥቅሶች ስለዚህ ጉዳይ ምን እንደሚሉ እንመልከት።—2 ጢሞቴዎስ 3:16

መጥፎ ጊዜና ያልተጠበቁ ክስተቶች

ሰለሞን በመክብብ መጽሐፍ ላይ እንዲህ ሲል ጽፏል፦ “ሌላም ነገር ከፀሐይ በታች አየሁ: ሩጫ ለፈጣኖች፣ ውጊያም ለኀያላን አይደለም፤ እንጀራ ለጥበበኞች፣ ወይም ባለጠግነት ለብልኆች፣ ወይም ሞገስ ለዐዋቂዎች አይሆንም።” ለምን? ሰለሞን እንዲህ ያለበትን ምክንያት ሲናገር “ሁሉም መጥፎ ጊዜና ያልተጠበቁ ክስተቶች ያጋጥሟቸዋል” (NW) ብሏል።—መክብብ 9:11

ሰለሞን ይህን ሲል የሰው ልጆች በሕይወታቸው ውስጥ የሚያጋጥሟቸው ነገሮች ሁሉ አስቀድመው እንደተወሰኑ መናገሩ አልነበረም፤ ከዚህ ይልቅ ሰዎች ‘መጥፎ ጊዜና ያልተጠበቁ ክስተቶች ስለሚያጋጥሟቸው’ የጥረታቸውን ውጤት አስቀድመው ማወቅ እንደማይችሉ መጠቆሙ ነበር። ብዙውን ጊዜ ሰዎች አንድ ነገር የሚያጋጥማቸው፣ በትክክለኛው ጊዜ ትክክለኛው ቦታ ላይ በመገኘታቸው አሊያም በአጉል ጊዜ አጉል ቦታ ላይ በመገኘታቸው ነው።

“ሩጫ ለፈጣኖች . . . አይሆንም” የሚለውን ሐሳብ እንደ ምሳሌ እንውሰድ። በ1984 በካሊፎርኒያ፣ ዩናይትድ ስቴትስ ተካሂዶ በነበረው የሎስ አንጀለስ የኦሎምፒክ ውድድር ላይ ስለተደረገው የ3000 ሜትር የሴቶች ሩጫ ታስታውስ ወይም አንብበህ ይሆናል። በዚህ አስገራሚ ውድድር ላይ ብሪታንያንና ዩናይትድ ስቴትስን ወክለው የቀረቡ ሁለት ተወዳዳሪዎች የወርቅ ሜዳሊያውን ለማግኘት ተስፋ በማድረግ ይፎካከሩ ነበር። ይሁን እንጂ በውድድሩ አጋማሽ አካባቢ ሁለቱ አትሌቶች እርስ በርሳቸው ተጋጩ። አንደኛዋ በመውደቋ ምክንያት ውድድሩን አቋርጣ ስትወጣ ሌላኛዋ ደግሞ ተስፋ ቆርጣ ስለነበር ውድድሩን ሰባተኛ ሆና አጠናቀቀች።

እነዚህ አትሌቶች እንዲህ ዓይነት ሁኔታ ያጋጠማቸው ዕድላቸው አስቀድሞ ስለተወሰነ ነው? አንዳንዶች እንደዚህ ይሰማቸው ይሆናል። ይሁንና አትሌቶቹ ማሸነፍ ያልቻሉት ያልጠበቁት ክስተት በመፈጠሩ ይኸውም እርስ በርስ በመጋጨታቸው ምክንያት ነው። ታዲያ መጋጨታቸው አስቀድሞ የተወሰነ ነገር ነበር ማለት ነው? አሁንም አንዳንዶች እንደዚህ ይሉ ይሆናል። ይሁን እንጂ የስፖርት ጋዜጠኞች እንደተናገሩት ከሆነ ሁኔታው የተከሰተው ተመጣጣኝ ችሎታ ያላቸው ሁለት ጠንካራ አትሌቶች አንዳቸው ሌላውን ለመቅደም ባደረጉት ኃይለኛ ፉክክር የተነሳ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚናገረው “ሁሉም መጥፎ ጊዜና ያልተጠበቁ ክስተቶች ያጋጥሟቸዋል።” አንድ ሰው ምንም ያህል ጥረት ቢያደርግ በሚያገኘው ውጤት ላይ ተጽዕኖ የሚያሳድሩ አንዳንድ ያልተጠበቁ ሁኔታዎች መኖራቸው አይቀርም፤ ስለዚህ የሚገኘው ውጤት ከዕድል ጋር ምንም ግንኙነት የለውም።

ታዲያ መጽሐፍ ቅዱስ “ለሁሉም ነገር ጊዜ አለው” ሲል ምን ማለቱ ነው? በሕይወታችን ላይ ለውጥ ለማምጣት ማድረግ የምንችለው ነገር ይኖራል?

ማንኛውንም ነገር ለማከናወን የተሻለ ጊዜ አለ

በመንፈስ ቅዱስ ተመርቶ ከላይ ያለውን ሐሳብ የጻፈው ጠቢቡ ሰለሞን የተናገረው የሰዎች ዕድል አስቀድሞ ስለመወሰኑ ሳይሆን ስለ አምላክ ዓላማና ይህ ዓላማ የሰው ልጆችን እንዴት እንደሚነካቸው ነው። በጥቅሱ ዙሪያ ካለው ሐሳብ ይህን ለመረዳት እንችላለን። ሰለሞን “ለሁሉም ነገር ጊዜ [እንዳለው]” በመግለጽ በርከት ያሉ ነገሮችን ከዘረዘረ በኋላ እንደሚከተለው ሲል ጽፏል፦ “ሰዎች ይደክሙበት ዘንድ እግዚአብሔር የሰጣቸውን ከባድ የሥራ ጫና አየሁ። ሁሉንም ነገር በጊዜው ውብ አድርጎ ሠራው።”—መክብብ 3:10, 11

አምላክ የሰው ልጆች ሊሠሯቸው የሚችሉ በርካታ ነገሮችን የሰጣቸው ሲሆን ሰለሞንም ከእነዚህ መካከል የተወሰኑትን ጠቅሷል። በተጨማሪም አምላክ መሥራት የምንፈልገውን ነገር የመምረጥ ነፃነት ሰጥቶናል። ይሁን እንጂ እያንዳንዱን ሥራ በተሳካ ሁኔታ ለማከናወን የሚያስችል ተስማሚ ወይም አመቺ ጊዜ አለ። በመክብብ 3:2 ላይ የሚገኘውን ሰለሞን የተናገረውን ሐሳብ እንደ ምሳሌ እንመልከት፦ “ለመትከል ጊዜ አለው፤ ለመንቀልም ጊዜ አለው።” ገበሬዎች እያንዳንዱ ዘር ሊዘራበት የሚገባ ተስማሚ ጊዜ እንዳለው ያውቃሉ። አንድ ገበሬ ይህን ሐቅ ችላ በማለት አንድን ዘር አለጊዜው ወይም አለወቅቱ ቢዘራስ? ይህ ገበሬ ጥሩ ምርት ባያገኝ ዕድሉን ማማረር ይገባዋል? በጭራሽ! ገበሬው ጠንክሮ ሠርቶ ሊሆን ይችላል። ይሁን እንጂ ዘሩን በተገቢው ጊዜ አልዘራም። ይህ ገበሬ፣ ፈጣሪ ባወጣው የተፈጥሮ ሕግ ተመርቶ ቢሆን ኖሮ የተሻለ ምርት ማግኘት ይችል ነበር።

በመሆኑም አምላክ የሰዎችን ዕድል ወይም የሚያከናውኗቸው ነገሮች የሚያስገኙትን ውጤት አስቀድሞ አልወሰነም፤ ከዚህ ይልቅ ሰዎች ሊመሩባቸው የሚገቡና ከዓላማው ጋር የሚስማሙ አንዳንድ ሥርዓቶችን አስቀድሞ አስቀምጧል። ሰዎች በሚያከናውኑት ነገር ስኬታማ ለመሆን ከፈለጉ አስተዋዮች በመሆን ከአምላክ ዓላማና ከወሰነው ጊዜ ጋር በሚስማማ መንገድ መሥራት ይገባቸዋል። አምላክ አስቀድሞ የወሰነው እንዲሁም ሊለወጥ የማይችለው ዓላማው ነው እንጂ የግለሰቦች ዕድል አይደለም። ይሖዋ በነቢዩ ኢሳይያስ አማካኝነት እንዲህ ብሏል፦ “ከአፌ የሚወጣውም ቃሌ፣ በከንቱ ወደ እኔ አይመለስም፤ ነገር ግን የምሻውን ያከናውናል፤ የተላከበትንም ዐላማ ይፈጽማል።”—ኢሳይያስ 55:11

ታዲያ “የተላከበትን . . . ይፈጽማል” የተባለው የአምላክ ‘ቃል’ ወይም ከምድር እና ከሰው ልጆች የወደፊት ሕይወት ጋር የተያያዘው የአምላክ ዓላማ ምንድን ነው?

አምላክ የወሰነውን ጊዜ መረዳት

ሰለሞን ፍንጭ ሰጥቶናል። “[አምላክ] ሁሉንም ነገር በጊዜው ውብ አድርጎ ሠራው” ብሎ ከተናገረ በኋላ እንዲህ ብሏል፦ “በሰዎችም ልብ ዘላለማዊነትን አኖረ፤ ይሁን እንጂ እግዚአብሔር ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ያደረገውን ማወቅ አይችሉም።”—መክብብ 3:11

ሰዎች ይህን ጥቅስ በተመለከተ ብዙ ማብራሪያ ሰጥተዋል። የዚህ ጥቅስ ዋና መልእክት ግን ሁላችንም በሆነ ወቅት ላይ የሕይወት ትርጉም ምን እንደሆነና ወደፊት ምን እንደምንሆን የማወቅ ጉጉት እንደሚያድርብን የሚገልጽ ነው። ሰዎች ሕይወታቸውን ሙሉ ሲለፉ ኖረው መጨረሻቸው ሞት መሆኑ የሰው ልጆች በታሪክ ዘመናት ሁሉ ሊዋጥላቸው ያልቻለ ነገር ነው። የሰው ልጆች፣ ሕይወት ካላቸው ሌሎች ፍጥረታት የምንለየው አሁን ስላለው ሕይወታችን ብቻ ሳይሆን ስለ ሞት ብሎም ከዚያ በኋላ ስለሚኖረው ሁኔታ የምናስብ በመሆናችን ነው። ሌላው ቀርቶ ለዘላለም ለመኖር እንኳ እንመኛለን። እንዲህ ዓይነት ምኞት ሊኖረን የቻለው ለምንድን ነው? መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚናገረው ይህ የሆነው አምላክ ‘በሰዎች ልብ ዘላለማዊነትን ስላኖረ’ ነው።

የሰው ልጆች ይህን ምኞታቸውን ለማርካት ሲሉ ‘ከሞት በኋላ ሕይወት አለ’ የሚለውን ጽንሰ ሐሳብ ለመረዳት ጥረት ሲያደርጉ ቆይተዋል። አንዳንዶች፣ በውስጣችን ያለ አንድ ነገር ከሞትን በኋላ መኖሩን ይቀጥላል ወደሚል መደምደሚያ ደርሰዋል። ሌሎች ስንሞት እንደገና እየተወለድን ሕልውናችን ለዘላለም እንደሚቀጥል ያምናሉ። አንዳንዶች ደግሞ ዕድል ወይም አምላክ በሕይወት ውስጥ የሚያጋጥማቸውን ማንኛውም ነገር እንደወሰኑትና ይህን ለመለወጥ ምንም ማድረግ እንደማይችሉ ይሰማቸዋል። የሚያሳዝነው ግን እነዚህ ሁሉ ማብራሪያዎች ለሰው ልጅ አጥጋቢ መልስ አልሰጡትም። መጽሐፍ ቅዱስ ይህ የሆነበትን ምክንያት ሲገልጽ “[ሰዎች] እግዚአብሔር ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ያደረገውን ማወቅ አይችሉም” ይላል።

ባለፉት ዘመናት የኖሩ ምሑራንና ፈላስፎች ከላይ ለተነሳው ጥያቄ መልስ ለማግኘት ከፍተኛ ፍላጎት ቢኖራቸውም ይህን ማድረግ አለመቻላቸው አእምሯቸውን ሲበጠብጠው ቆይቷል። ወደፊት ምን እንደምንሆን የማወቅ ፍላጎት በልባችን ውስጥ እንዲኖር ያደረገው አምላክ እስከሆነ ድረስ ይህን ምኞታችንን ለማርካት የእሱን እርዳታ መሻታችን ተገቢ አይሆንም? መጽሐፍ ቅዱስም ቢሆን ስለ ይሖዋ ሲናገር እንዲህ ይላል፦ “አንተ እጅህን ትዘረጋለህ፤ የሕያዋን ፍጥረታትንም ሁሉ ፍላጎት ታረካለህ።” (መዝሙር 145:16) የአምላክ ቃል የሆነውን መጽሐፍ ቅዱስን በማጥናት ሕይወትንና ሞትን እንዲሁም አምላክ ለምድርና ለሰው ዘር ያለውን ዘላለማዊ ዓላማ በተመለከተ አጥጋቢ መልስ ማግኘት ትችላለህ።—ኤፌሶን 3:11

[በገጽ 5 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

“ሩጫ ለፈጣኖች . . . አይሆንም።”—መክብብ 9:11

[በገጽ 6 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

አንድ ገበሬ ዘሩን በጊዜው ሳይዘራ ቀርቶ ጥሩ ምርት ባያገኝ ዕድሉን ማማረር ይገባዋል?

[በገጽ 7 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

ስለ ሕይወትና ስለ ሞት የማወቅ ፍላጎት ሊኖረን የቻለው አምላክ ‘በሰዎች ልብ ዘላለማዊነትን ስላኖረ’ ነው