በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ጥሩ ሰዎች ሁሉ ወደ ሰማይ ይሄዳሉ?

ጥሩ ሰዎች ሁሉ ወደ ሰማይ ይሄዳሉ?

ጥሩ ሰዎች ሁሉ ወደ ሰማይ ይሄዳሉ?

ኢየሱስ ከመገደሉ በፊት ከሐዋርያቱ ጋር ለመጨረሻ ጊዜ እራት ከበላ በኋላ ለሐዋርያቱ በሰማይ ላይ መኖሪያ እንደሚያዘጋጅላቸው ቃል ገባላቸው። እንዲህ ብሏቸው ነበር፦ “በአባቴ ቤት ብዙ መኖሪያ አለ። እንዲህ ባይሆን ኖሮ እነግራችሁ ነበር፤ ምክንያቱም የምሄደው ለእናንተ ቦታ ለማዘጋጀት ነው።” (ዮሐንስ 14:2) ኢየሱስ በሰማይ መኖሪያ የሚያዘጋጅላቸው ለምንድን ነው? እነዚህ ሰዎች እዚያ ሄደው ምን ይሠራሉ?

ኢየሱስ ይህን ሲናገር ለደቀ መዛሙርቱ ልዩ የሆነ ተልዕኮ እንደሚጠብቃቸው በአእምሮው ይዞ ነው። በዚያው ምሽት እንዲህ ብሏቸው ነበር፦ “እናንተ በፈተናዎቼ ከጎኔ ሳትለዩ ቆይታችኋል፤ አባቴ ከእኔ ጋር ቃል ኪዳን እንዳደረገ ሁሉ እኔም ከእናንተ ጋር ለመንግሥት ቃል ኪዳን አደርጋለሁ።” (ሉቃስ 22:28, 29) አምላክ ለኢየሱስ ንጉሥ እንደሚሆን ቃል ገብቶለታል፤ እሱ ንጉሥ ሆኖ የሚያስተዳድረው መንግሥት ደግሞ የሰው ልጆች በጣም የሚያስፈልጋቸውን መልካም አስተዳደር ያመጣል። ኢየሱስ ሰዎችን ከችግር ይገላግላቸዋል፤ የሚጨቁኗቸውንም ያደቃል። ኢየሱስ ግዛቱ “እስከ ምድር ዳርቻ” ድረስ የሚስፋፋ ቢሆንም ዙፋኑ የሚገኘው በሰማይ ነው።—መዝሙር 72:4, 8፤ ዳንኤል 7:13, 14

ይሁን እንጂ ኢየሱስ የሚገዛው ብቻውን አይደለም። በመሆኑም ለሐዋርያቱ በሰማይ ቦታ እንደሚያዘጋጅላቸው ቃል ገብቶላቸዋል። ሐዋርያቱ ‘በምድርም ላይ ነገሥታት ሆነው ለመግዛት’ ከተመረጡት መካከል የመጀመሪያዎቹ ነበሩ።—ራእይ 5:10

ወደ ሰማይ የሚሄዱት ሰዎች ቁጥራቸው ምን ያህል ነው? ልክ እንደ ማንኛውም ሰብዓዊ መንግሥታት ሁሉ በሰማይ የሚገኘው የአምላክ መንግሥት ገዥዎች ቁጥርም በመንግሥቱ ሥር ከሚተዳደሩት ሰዎች አንጻር ሲታይ አነስተኛ ነው። ኢየሱስ አብረውት ለሚገዙት ሰዎች “አንተ ትንሽ መንጋ፣ አባታችሁ መንግሥትን ሊሰጣችሁ ስለፈቀደ አትፍሩ” ብሏቸዋል። (ሉቃስ 12:32) የዚህ “ትንሽ መንጋ” አባላት ቁጥር 144,000 ነው። (ራእይ 14:1) የዚህ መንጋ አባላት ቁጥር በመንግሥቱ ሥር ከሚተዳደሩት በምድር ላይ ለዘላለም ከሚኖሩት በሚሊዮን የሚቆጠሩ ታማኝ ተገዥዎች ቁጥር ጋር ሲወዳደር አነስተኛ ነው።—ራእይ 21:4

በመሆኑም ጥሩ ሰዎች ሁሉ ወደ ሰማይ አይሄዱም። ሐዋርያው ጴጥሮስ ንጉሥ ዳዊትን አስመልክቶ ሲናገር “ዳዊት ወደ ሰማያት አልወጣም” ብሏል። (የሐዋርያት ሥራ 2:34) መጥምቁ ዮሐንስ ጥሩ ሰው ነበር። ያም ሆኖ ኢየሱስ፣ መጥምቁ ዮሐንስ በሰማይ ንጉሥ ሆኖ የመግዛት መብት እንደማያገኝ ጠቁሟል። ኢየሱስ እንዲህ በማለት ተናግሯል፦ “ከሴት ከተወለዱት መካከል ከመጥምቁ ዮሐንስ የሚበልጥ አልተነሳም፤ ሆኖም በመንግሥተ ሰማያት ዝቅተኛ የሆነው እንኳ ይበልጠዋል።”—ማቴዎስ 11:11

ጥሩ ሰዎች የሚያገኙትን ሽልማት አንተም ማግኘት ትችል ይሆን?

አንድ ሰው በምድር ላይ ለዘላለም የመኖርን ሽልማት ለማግኘት ምን ማድረግ አለበት? ኢየሱስ እንዲህ ብሏል፦ “አምላክ ዓለምን እጅግ ከመውደዱ የተነሳ በልጁ እንደሚያምን በተግባር የሚያሳይ ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ ሲል አንድያ ልጁን ሰጥቷል።” (ዮሐንስ 3:16) አምላክ ሰዎች ሁሉ የዘላለም ሕይወት የሚያገኙበትን ዝግጅት እንዲያደርግ ያነሳሳው ለዓለም ያለው ፍቅር እንደሆነ ልብ በል፤ ይህን ሽልማት የሚያገኙት ግን ‘በልጁ እንደሚያምኑ በተግባር የሚያሳዩ’ ሰዎች ብቻ ናቸው።

እምነት በትክክለኛ እውቀት ላይ መመሥረት አለበት። (ዮሐንስ 17:3) አንተም ይሖዋ ለሰው ልጆች ያለውን ዓላማ በመማር ጥሩ ሰው መሆንህን ማሳየት ትችላለህ። የተማርከውን ነገር ተግባራዊ በማድረግ እምነት እንዳለህ አሳይ። የዘላለም ሕይወት የምታገኝበት አጋጣሚ ለአንተም እንደተከፈተልህ እርግጠኛ ሁን።

[በገጽ 7 ላይ የሚገኝ ሣጥን]

መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይላል?

ጥያቄ፦

ጥሩ ሰዎች ሲሞቱ ምን ይሆናሉ?

መልስ፦

“ሙታን ግን ምንም አያውቁም።”መክብብ 9:5

ጥያቄ፦

ጥሩ ሰዎች ወደፊት ምን ተስፋ አላቸው?

መልስ፦

“በመታሰቢያ መቃብር ያሉ ሁሉ [የኢየሱስን ድምፅ] የሚሰሙበት ሰዓት ይመጣል።”ዮሐንስ 5:28, 29

ጥያቄ፦

አብዛኞቹ ጥሩ ሰዎች ወደፊት የሚኖሩት የት ነው?

መልስ፦

“ጻድቃን ምድርን ይወርሳሉ፤ በእርሷም ለዘላለም ይኖራሉ።”መዝሙር 37:29