በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ለዘመናችንም የሚጠቅም

ለዘመናችንም የሚጠቅም

ለዘመናችንም የሚጠቅም

“ሕግህ ለእግሬ መብራት፣ ለመንገዴም ብርሃን ነው።”​—መዝሙር 119:105

መጽሐፍ ቅዱስን የተለየ የሚያደርገው ምንድን ነው? አንዳንድ ጽሑፎች ግሩም የሥነ ጽሑፍ ሥራዎች እንደሆኑ ተደርገው ይቆጠሩ ይሆናል፤ ሕይወታችንን ለመምራት የሚረዳ አስተማማኝ መመሪያ ግን ሊሰጡን አይችሉም። በዘመናችን የሚዘጋጁ ስለ አንድ ነገር አሠራር የሚገልጹ መመሪያዎችም በየጊዜው መታረም ያስፈልጋቸዋል። በሌላ በኩል ግን መጽሐፍ ቅዱስ፣ በውስጡ ስለያዘው ሐሳብ ሲናገር “ቀደም ብሎ የተጻፈው ነገር ሁሉ ለእኛ ትምህርት እንዲሆን ተጽፏል” ይላል።​—ሮም 15:4

ምሳሌ፦ መጽሐፍ ቅዱስ የሕክምና መጽሐፍ ባይሆንም ስሜታዊም ሆነ አካላዊ ጤንነታችንን ለመጠበቅ የሚያስችሉን ጠቃሚ ሐሳቦች ይዟል። ለምሳሌ ያህል፣ “ሰላም ያለው ልብ ለሰውነት ሕይወት ይሰጣል” ይላል። (ምሳሌ 14:30) እንዲሁም “ወዳጅነትን የማይፈልግ ሰው የራሱን ፍላጎት ብቻ ይከተላል፤ ቅን የሆነውን ፍርድ ሁሉ ይቃወማል” በማለት ያስጠነቅቃል። (ምሳሌ 18:1) በሌላ በኩል ደግሞ “ከመቀበል ይልቅ መስጠት የበለጠ ደስታ ያስገኛል” በማለት ይናገራል።​—የሐዋርያት ሥራ 20:35

የምርምር ውጤቶች ምን ያሳያሉ? ውስጣዊ ሰላም፣ ጠንካራ ወዳጅነት እንዲሁም ለጋስነት የተሻለ ጤንነት እንዲኖርህ አስተዋጽኦ ያደርጋሉ። ዘ ጆርናል ኦቭ ዚ አሜሪካን ሜዲካል አሶሲዬሽን እንዲህ ይላል፦ “ቁጣቸውን ከሚቆጣጠሩ ወንዶች ጋር ሲነጻጸሩ በቁጣ የመገንፈል ችግር ያለባቸው ወንዶች በአንጎላቸው ውስጥ ደም በመፍሰሱ ለሕመም የመጋለጣቸው አጋጣሚ በሁለት እጥፍ ከፍ ያለ ነው።” በአውስትራሊያ ለአሥር ዓመት የተደረገ አንድ ጥናት እንዳሳየው “ከወዳጆቻቸውና ሚስጥራቸውን ከሚያካፍሏቸው ሰዎች ጋር ጥሩ ግንኙነት ያላቸው” አረጋውያን ረዘም ያለ ዕድሜ ይኖራሉ። በካናዳና በዩናይትድ ስቴትስ የሚገኙ ተመራማሪዎች ደግሞ በ2008 ባካሄዱት ጥናት “ገንዘብን ራስን ለማስደሰት ከማዋል ይልቅ ሌሎችን ለመጥቀም ማዋሉ የበለጠ ደስታ እንደሚያስገኝ” አረጋግጠዋል።

ታዲያ ምን ይመስልሃል? ተጽፎ ካለቀ ወደ 2,000 የሚጠጉ ዓመታት ያለፉት ሌላ ጥንታዊ መጽሐፍ በጤና ጉዳይ ላይ የሚሰጠውን ምክር እምነት ልትጥልበት ትችላለህ? ወይስ መጽሐፍ ቅዱስ ልዩ የሆነ መጽሐፍ ነው ትላለህ?

[በገጽ 8 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

“መጽሐፍ ቅዱስ በጣም ይማርከኛል፤ . . . ምክንያቱም ከጤና ጋር የተያያዙ ግሩም ምክሮችን ይሰጣል።”​—ሃዋርድ ኬሊ፣ የሕክምና ዶክተር፣ የጆንስ ሆፕኪንስ ዩኒቨርሲቲ የሕክምና ክፍል መሥራች አባል