በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

 የሽፋኑ ርዕሰ ጉዳይ | የመጽሐፍ ቅዱስ መልእክት ምንድን ነው?

“መሲሑን አገኘነው”!

“መሲሑን አገኘነው”!

በዕብራይስጥ የተጻፈው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የመጨረሻ መጽሐፍ ከተጻፈ ከአራት መቶ ዓመታት ገደማ በኋላ፣ ሚክያስ ስለ መሲሑ የተናገረው ትንቢት ተፈጸመ፤ ይኸውም ኢየሱስ በቤተልሔም ተወለደ። ይህ ከሆነ ከ30 ዓመታት ገደማ በኋላ ማለትም በ29 ዓ.ም. ደግሞ ዳንኤል ስለ መሲሑ መምጣት የተናገረው ትንቢት ተፈጸመ። በዚህ ወቅት ኢየሱስ የተጠመቀ ሲሆን አምላክም በመንፈስ ቅዱስ ቀባው። ለረጅም ጊዜ ሲጠበቅ የኖረው መሲሕ ይኸውም ዘሩ አስቀድሞ በተነገረለት ጊዜ መጣ!

ኢየሱስ ‘የአምላክን መንግሥት ምሥራች በማወጅ’ ወዲያውኑ አገልግሎቱን ጀመረ። (ሉቃስ 8:1) ልክ በትንቢቱ እንደተነገረው ኢየሱስ ደግ፣ ገርና ለሌሎች ከልብ የሚያስብ ሰው ነበር። የሚያስተምረው ነገር ጠቃሚና ፍቅር የሚንጸባረቅበት ነበር፤ እንዲሁም “ማንኛውንም ዓይነት ሕመም” በመፈወስ አምላክ ከእሱ ጋር እንደሆነ በግልጽ አሳይቷል። (ማቴዎስ 4:23) በማንኛውም የዕድሜ ክልል የሚገኙ ሰዎች ወደ እሱ ይጎርፉ የነበረ ሲሆን እነዚህ ሰዎች፣ “መሲሑን . . . አገኘነው” ብሎ እንደተናገረው የኢየሱስ ደቀ መዝሙር ተሰምቷቸዋል!—ዮሐንስ 1:41

ኢየሱስ፣ የእሱ መንግሥት ምድርን መግዛት ከመጀመሩ ጥቂት ቀደም ብሎ ዓለም በጦርነት፣ በምድር ነውጥና በሌሎች በርካታ ችግሮች እንደሚታመስ ትንቢት ተናግሯል። በመሆኑም ሁላችንንም “ምንጊዜም ነቅታችሁ ጠብቁ” በማለት አሳስቦናል።—ማርቆስ 13:37

ኢየሱስ ለአምላክ እስከ መጨረሻው ታዛዥ የሆነ ፍጹም ሰው ቢሆንም የኋላ ኋላ ጠላቶቹ አስገደሉት። ኢየሱስ መሞቱ አዳምና ሔዋን ያሳጡንን ነገር ይኸውም በገነት ውስጥ ፍጻሜ የሌለው ሕይወት የማግኘት አጋጣሚን እንደገና መልሰን ለማግኘት የሚያስችለን ተመጣጣኝ ዋጋ እንዲከፈል አድርጓል።

ኢየሱስ እንደሚሞት እንዲሁም አምላክ ከሦስት ቀን በኋላ ኃያል መንፈሳዊ ፍጡር አድርጎ እንደሚያስነሳው የተነገሩት ትንቢቶች ተፈጽመዋል። ኢየሱስ ከሞት ከተነሳ በኋላ ከ500 ለሚበልጡ ደቀ መዛሙርቱ ተገልጦላቸዋል። ኢየሱስ፣ ስለ እሱና ስለ መንግሥቱ የሚገልጸውን ምሥራች ‘ለሁሉም ብሔራት’ እንዲያደርሱ ወደ ሰማይ ከማረጉ በፊት ተከታዮቹን አዘዛቸው። (ማቴዎስ 28:19) ታዲያ ተከታዮቹ ይህን ተልዕኮ በተሟላ ሁኔታ ፈጽመዋል?

በማቴዎስ፣ በማርቆስ፣ በሉቃስ፣ በዮሐንስ እና በ1 ቆሮንቶስ መጻሕፍት ላይ የተመሠረተ