በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የመጽሐፍ ቅዱስ ጥያቄዎችና መልሶቻቸው

የመጽሐፍ ቅዱስ ጥያቄዎችና መልሶቻቸው

የሞቱ ሰዎች ተስፋ አላቸው?

ሞት ልክ እንደ እንቅልፍ ነው፤ የሞቱ ሰዎች ምንም የማያውቁ ከመሆኑም ሌላ ሊያከናውኑት የሚችሉት ነገር የለም። ይሁን እንጂ ሕይወትን የፈጠረው አምላክ የሞቱ ሰዎችን ያስነሳቸዋል። ኢየሱስ በአምላክ ኃይል የሞቱ ሰዎችን ማስነሳቱ የሞቱ ሰዎች ወደፊት እንደሚነሱ ማረጋገጫ ይሆነናል።መክብብ 9:5ን እና ዮሐንስ 11:11, 43, 44ን አንብብ።

ሞት ከእንቅልፍ ጋር የሚመሳሰለው እንዴት ነው?

አምላክ፣ የሞቱ ሰዎችን አስታውሶ እንደሚያስነሳቸውና ጽድቅ በሰፈነበት አዲስ ዓለም ውስጥ ሕይወት እንደሚሰጣቸው ቃል ገብቷል። አምላክ ይህን ለማድረግ የወሰነው ጊዜ እስኪደርስ ድረስ የሞቱ ሰዎች አንቀላፍተው ይቆያሉ። ሁሉን ቻይ የሆነው አምላክ የሞቱ ሰዎችን ለማስነሳት ይጓጓል።ኢዮብ 14:14, 15ን አንብብ።

ትንሣኤ ሲባል ምን ማለት ነው?

የሞቱ ሰዎች በትንሣኤ ሲነሱ የቀድሞ ሕይወታቸውን እንዲሁም ወዳጅ ዘመዶቻቸውን ማስታወስ ይችላሉ። አንድ ሰው ሲሞት ሰውነቱ ቢበሰብስም አምላክ፣ ያው ግለሰብ አዲስ አካል ኖሮት እንዲነሳ ማድረግ ይችላል።1 ቆሮንቶስ 15:35, 38ን አንብብ።

የተወሰነ ቁጥር ያላቸው ሰዎች ከሞት ተነስተው ወደ ሰማይ ይሄዳሉ። (ራእይ 20:6) ከሞት የሚነሱ አብዛኞቹ ሰዎች ደግሞ ምድር ገነት ስትሆን በዚያ ይኖራሉ። እነዚህ ሰዎች ሕይወታቸውን እንደ አዲስ የመምራት አጋጣሚ የሚያገኙ ሲሆን ለዘላለም የመኖር ተስፋ ይዘረጋላቸዋል።መዝሙር 37:29ን እና የሐዋርያት ሥራ 24:15ን አንብብ።