በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የመጽሐፍ ቅዱስ ጥያቄዎችና መልሶቻቸው

የመጽሐፍ ቅዱስ ጥያቄዎችና መልሶቻቸው

አምላክን በተመለከተ እውነቱን ማወቅ እንችላለን?

አምላክ እውነትን እንድናውቅ የሚፈልገው ለምንድን ነው? ዮሐንስ 17:3ን አንብብ

አምላክ ሐሳቡን ለሰው ልጆች ገልጿል። ሐሳቡን በመጽሐፍ ቅዱስ ጸሐፊዎች አእምሮ ውስጥ ለማስቀመጥ መንፈስ ቅዱስን ወይም በሥራ ላይ ያለው ኃይሉን ተጠቅሟል። (2 ጴጥሮስ 1:20, 21) መጽሐፍ ቅዱስን በማንበብ ስለ አምላክ እውነቱን ማወቅ እንችላለን።—ዮሐንስ 17:17ን እና 2 ጢሞቴዎስ 3:16ን አንብብ።

በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አምላክ ስለ ራሱ ብዙ ነገር ገልጾልናል። ሰዎችን የፈጠረው ለምን እንደሆነ፣ ወደፊት ለሰው ልጆች ምን እንደሚያደርግላቸው እንዲሁም ምን ዓይነት ሕይወት እንድንመራ እንደሚፈልግ አሳውቆናል። (የሐዋርያት ሥራ 17:24-27) ይሖዋ አምላክ ስለ እሱ እውነቱን እንድናውቅ ይፈልጋል።—1 ጢሞቴዎስ 2:3, 4ን አንብብ።

አምላክ እውነት ወዳድ የሆኑ ሰዎች ወደ እሱ እንዲመጡ የሚያደርገው ለምንድን ነው?

ይሖዋ የእውነት አምላክ ነው፤ ደግሞም ለሰው ልጆች እውነትን እንዲያስተምር ልጁን ኢየሱስን ወደ ምድር ልኮታል። በመሆኑም እውነትን የሚወዱ ሰዎች የኢየሱስን ትምህርት ይቀበላሉ። (ዮሐንስ 18:37) አምላክ እንዲህ ያሉ ሰዎች እሱን እንዲያመልኩት ይፈልጋል።—ዮሐንስ 4:23, 24ን አንብብ።

ሰይጣን ዲያብሎስ አምላክን በተመለከተ የሐሰት ትምህርቶች በማስፋፋት ብዙ ሰዎች አምላክን እንዳያውቁ አድርጓል። (2 ቆሮንቶስ 4:3, 4) መልካም የሆነውን ነገር የማይወዱ ሰዎች እንዲህ ላሉ የሐሰት ትምህርቶች ጆሮ ይሰጣሉ። (ሮም 1:25) ሆኖም በሚሊዮን የሚቆጠሩ ቅን ልብ ያላቸው ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስን በማጥናት ስለ አምላክ እውነቱን እየተማሩ ነው።—የሐዋርያት ሥራ 17:11ን አንብብ።