በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የምታደርጉት መዋጮ ጥቅም ላይ እየዋለ ያለው እንዴት ነው?

ከአምላክ ጋር የሚያቀራርቡ መዝሙሮች

ከአምላክ ጋር የሚያቀራርቡ መዝሙሮች

ኅዳር 1, 2021

 ሙዚቃ ከይሖዋ ያገኘነው ልዩ ስጦታ ነው። አስተሳሰባችንን የመቅረጽ፣ ስሜታችንን የማነቃቃት እንዲሁም ለሥራ እንድንነሳሳ የማድረግ ኃይል አለው። ከኦሪጅናል መዝሙሮቻችን ጋር በተያያዘም ይህ እውነት ነው። እንዲያውም እነዚህ መዝሙሮች ከዚህ ያለፈ ጥቅምም አላቸው፤ ከይሖዋ ጋር እንድንቀራረብ ይረዱናል።

 ከ2014 ወዲህ ከ70 የሚበልጡ ኦሪጅናል መዝሙሮች ወጥተዋል፤ በአሁኑ ወቅት ከ500 የሚበልጡ ቋንቋዎች ከእነዚህ መዝሙሮች ቢያንስ አንዱን አውጥተዋል። ሆኖም እነዚህ ጥያቄዎች ይፈጠሩብህ ይሆናል፦ ‘እነዚህን መዝሙሮች የሚያዘጋጃቸው ማን ነው? መዝሙሮቹን ለማዘጋጀትስ ምን ሥራ ይከናወናል?’

ከበስተ ጀርባ የሚከናወነው ሥራ

 ኦሪጅናል መዝሙሮችን የሚያዘጋጀው በኦዲዮ/ቪዲዮ አገልግሎት ውስጥ ያለው የሙዚቃ ቡድን ነው፤ ይህ ቡድን የሚሠራው በበላይ አካሉ የትምህርት ኮሚቴ ሥር ሆኖ ነው። የሙዚቃ ቡድኑ 13 ወንድሞችንና እህቶችን ያቀፈ ነው። ከሚያከናውኗቸው ሥራዎች መካከል ዜማ መድረስ፣ ሙዚቃ ማቀናበር፣ ሥራ መመደብ እንዲሁም ሌሎች ድጋፍ ሰጪ ሥራዎች ይገኙበታል። በተጨማሪም የትምህርት ኮሚቴው በዓለም ዙሪያ የሚገኙ የርቀት ፈቃደኛ ሠራተኞች በሥራው እገዛ እንዲያበረክቱ ፈቃድ ሰጥቷል፤ ከእነዚህ ፈቃደኛ ሠራተኞች መካከል የግጥምና የዜማ ደራሲዎች፣ ሙዚቀኞች እንዲሁም ዘማሪዎች ይገኙበታል። እነዚህ ወንድሞችና እህቶች እውቅና እንዲሰጣቸው ሳይጠብቁ ተሰጥኦዋቸውን በትሕትና እየተጠቀሙበት ነው።

 ታዲያ አንድ ኦሪጅናል መዝሙር የሚዘጋጀው እንዴት ነው? በመጀመሪያ የትምህርት ኮሚቴው፣ ለመዝሙሩ መሠረት የሚሆኑትን ጥቅሶች እንዲሁም መዝሙሩ ሊያስተላልፍ የሚገባውን ስሜት ይወስናል። ከዚያም የሙዚቃ ቡድኑ ዜማውን ለሚያቀናብሩና ግጥሙን ለሚደርሱ ሰዎች ሥራ ይመድባል። ቀጥሎም የናሙና ቅጂ ይዘጋጃል። የትምህርት ኮሚቴው የናሙና ቅጂውን ከገመገመ በኋላ ተጨማሪ መመሪያ ይሰጣል። በኋላም የሙዚቃ ቡድኑ አስፈላጊውን ማስተካከያ አድርጎ የመጨረሻውን ቅጂ ያዘጋጃል። እነዚህ መዝሙሮች የሚቀዱት በተለያዩ ቦታዎች ነው፤ ለምሳሌ በቅርንጫፍ ቢሮዎች ወይም በግለሰብ ቤቶች ባሉ ስቱዲዮዎች ውስጥ ሊቀዱ ይችላሉ።

 ወንድሞቻችን ኦሪጅናል መዝሙሮቹን ለማቀናበርና ለመቅዳት የተለያዩ የኮምፒውተር ፕሮግራሞችን ይጠቀማሉ። ለሥራው የሚያስፈልጉ ሌሎች ቁሳቁሶችም አሉ፤ ለምሳሌ የሙዚቃ መሣሪያዎች፣ ሚክሰር፣ የድምፅ ማጉያና ማይክሮፎን ያስፈልጋል። የእያንዳንዱ ማይክሮፎን ዋጋ ከ100 እስከ 1,000 የአሜሪካ ዶላር ሊደርስ ይችላል። በ2020 የሙዚቃና የቅጂ መሣሪያዎችን ለመግዛት 116,000 የአሜሪካ ዶላር አውጥተናል።

 ታዲያ በመዋጮ የተገኘውን ገንዘብ ለመቆጠብ ምን ጥረት ተደርጓል? ቤቴል ውስጥ ትልቅ የሙዚቃ ቡድን እንዲኖር ከማድረግ ይልቅ በርካታ የርቀት ፈቃደኛ ሠራተኞችን እየተጠቀምን ነው። በተጨማሪም ወንድሞች ኦርኬስትራ ለመቅዳት ሲሉ ብዙ ሰዎች እንዲሰባሰቡ ከማድረግ ይልቅ የተለያዩ የሙዚቃ መሣሪያዎችን ድምፅ የሚፈጥሩ የኮምፒውተር ፕሮግራሞችን ይጠቀማሉ።

“በመንፈሳዊ የደም ሥር ሆነውልኛል”

 ወንድሞችና እህቶች ኦሪጅናል መዝሙሮቹን ማዳመጥ ያስደስታቸዋል። በጀርመን የምትኖረው ታራ እንዲህ ብላለች፦ “መዝሙሮቹ፣ ስጨነቅ ዘና እንድል ይረዱኛል። መዝሙሮቹን በአፍ መፍቻ ቋንቋዬ ሳዳምጥ ይሖዋ እቅፍ እንዳደረገኝ ይሰማኛል።” በካዛክስታን የሚኖር ዲሚትሪ የተባለ ወንድም እንዲህ ብሏል፦ “መዝሙሮቹን ‘ከመጽሐፍ ቅዱስ መመሪያዎች ጋር የሚጋጭ ነገር ይኖራቸው ይሆን?’ ብዬ ሳልሳቀቅ ማዳመጥ መቻሌ ያስደስተኛል። በተጨማሪም ሁሌም በመንፈሳዊ ነገሮች ላይ እንዳተኩር ይረዱኛል።”

 በደቡብ አፍሪካ የምትኖረው ደሊያ ስለ ኦሪጅናል መዝሙሮች ያላትን ስሜት ስትገልጽ እንዲህ ብላለች፦ “መዝሙሮቹ በመንፈሳዊ የደም ሥር ሆነውልኛል። ሲከፋኝ ወይም አንድ ችግር ሲያጋጥመኝ ሁልጊዜም ከእኔ ሁኔታ ጋር የሚስማማ መዝሙር አገኛለሁ። ብዙውን ጊዜ ገና ማጀቢያ ሙዚቃውን ስሰማ ነው ስሜቴ የሚቀየረው!”

 አንዳንድ ኦሪጅናል መዝሙሮች በብዙዎች ዘንድ ተወዳጅ ሆነዋል። በደቡብ አፍሪካ የምትኖረው ለራቶ እንዲህ ብላለች፦ “‘ሩቅ አይደለም ያ ጊዜ’ እና ‘ያ አዲስ ዘመን’ የተባሉት መዝሙሮች በአዲሱ ዓለም ውስጥ የምወዳትን እናቴን የምቀበልበትን ጊዜ በዓይነ ሕሊናዬ እንድስል ይረዱኛል። መዝሙሮቹን ባዳመጥኩ ቁጥር እናቴ እኔን ለማቀፍ እጇን ዘርግታ ወደ እኔ ስትሮጥ ይታየኛል።”

 በስሪ ላንካ የምትኖር አንዲት ወጣት ጠቃሚ ሆኖ ያገኘችው አንድ ኦሪጅናል መዝሙር አለ። እንዲህ ብላለች፦ “የሳይንስ አስተማሪዬ የይሖዋ ምሥክር በመሆኔ ብቻ በክፍሉ ተማሪዎች ፊት ስለ እኔ መጥፎ ነገር ተናገረች። ከመፍራቴ የተነሳ የምለው ነገር ጠፋኝ። ወደ ቤት ስመለስ እናቴ ‘ጥናት ያጠነክርሃል’ (እንግሊዝኛ) የሚለውን መዝሙር እንዳዳምጥ አበረታታችኝ። መዝሙሩን ሳዳምጥ፣ ምርምር ማድረግና ምን ብዬ እንደምመልስ መዘጋጀት አስፈላጊ እንደሆነ ተገነዘብኩ። በቀጣዩ ቀን አስተማሪዬን አነጋገርኳት። እሷም አዳመጠችኝ፤ አሁን ስለ ይሖዋ ምሥክሮች እምነት የተሻለ ግንዛቤ እንዳገኘች ነገረችኝ። እንዲህ ያሉ የሚያበረታቱ መዝሙሮች ስላዘጋጀልን የይሖዋን ድርጅት ማመስገን እፈልጋለሁ።”

 እነዚህን መዝሙሮች ማዘጋጀት የሚጠይቀው ወጪ የሚሸፈነው እንዴት ነው? ለዓለም አቀፉ ሥራ በሚደረገው መዋጮ ነው፤ ብዙዎች መዋጮ የሚያደርጉት donate.pr418.com ላይ የተጠቀሱትን ዘዴዎች ተጠቅመው ነው። በልግስና ለምታደርጉት መዋጮ እናመሰግናችኋለን።