በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

id-work/DigitalVision Vectors via Getty Images

ነቅታችሁ ጠብቁ!

ጥላቻ ይህን ያህል የበዛው ለምንድን ነው?—መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይላል?

ጥላቻ ይህን ያህል የበዛው ለምንድን ነው?—መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይላል?

 ስለ ጥላቻ ንግግር፣ በጥላቻ ምክንያት ስለሚፈጸም ወንጀል፣ ከዘረኝነት ጋር ስለተያያዙ ጥቃቶችና ስለ ጦርነት የሚገልጹ ዜናዎች መገናኛ ብዙኃንን አጥለቅልቀዋል።

  •   “በእስራኤልና በጋዛ መካከል የተፈጠረው ግጭት የጽንፈኞች ቆስቋሽነት ተጨምሮበት በማኅበራዊ ሚዲያዎች ላይ የሚታየው የጥላቻ ንግግር በእጅጉ እንዲጨምር ምክንያት ሆኗል።”—ዘ ኒው ዮርክ ታይምስ፣ ኅዳር 15, 2023

  •   “ከጥቅምት 7 ወዲህ በዓለም ላይ ጥላቻ፣ የጥላቻ ንግግርና በጥላቻ ምክንያት የሚፈጸም ወንጀል አስደንጋጭ በሆነ መጠን ጨምሯል።”—ዴኒስ ፍራንሲስ፣ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ጠቅላላ ጉባኤ ፕሬዚዳንት፣ ኅዳር 3, 2023

 የጥላቻ ንግግር፣ ዓመፅና ጦርነት አሁን የመጡ ነገሮች አይደሉም። እንዲያውም መጽሐፍ ቅዱስ በጥንት ጊዜ ስለነበሩ ‘መርዘኛ ቃላቸውን እንደ ቀስት የሚያነጣጥሩ’ እንዲሁም ጦርነትና ዓመፅን የሚወዱ ሰዎች ተናግሯል። (መዝሙር 64:3፤ 120:7፤ 140:1) ሆኖም መጽሐፍ ቅዱስ ዛሬ እየታየ ያለው ጥላቻ በዓይነቱ ልዩ እንደሆነም ይገልጻል።

ጥላቻ—የዘመናችን መለያ ምልክት

 መጽሐፍ ቅዱስ በዛሬው ጊዜ ጥላቻ ይህን ያህል የተስፋፋባቸውን ሁለት ምክንያቶች ይናገራል።

  1.  1. ‘የብዙዎች ፍቅር የሚቀዘቅዝበት’ ጊዜ እንደሚመጣ አስቀድሞ ተናግሯል። (ማቴዎስ 24:12) በጥቅሉ ሲታይ ሰዎች ከፍቅር ይልቅ ጥላቻን የሚያነሳሱ ባሕርያትን ያንጸባርቃሉ።—2 ጢሞቴዎስ 3:1-5

  2.  2. በዛሬው ጊዜ ጥላቻ ይህን ያህል አስከፊ ደረጃ ላይ መድረሱ፣ ሰይጣን ዲያብሎስ እያሳደረ ያለው ተጽዕኖ ምን ያህል ከባድ እንደሆነ የሚያሳይ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ “መላው ዓለም . . . በክፉው ቁጥጥር ሥር” እንደሆነ ይናገራል።—1 ዮሐንስ 5:19፤ ራእይ 12:9, 12

 በሌላ በኩል ግን መጽሐፍ ቅዱስ አምላክ ለክፋት መንስኤ የሆኑትን ነገሮች በሙሉ በቅርቡ እንደሚያስወግድ ይገልጻል። ከዚህም በተጨማሪ አምላክ በጥላቻ ምክንያት ለብዙ ሥቃይ የተዳረጉ ሰዎችን ቁስል ይፈውሳል። መጽሐፍ ቅዱስ የሚከተለውን ተስፋ ሰጥቷል፦

  •   አምላክ “እንባን ሁሉ ከዓይናቸው ያብሳል፤ ከእንግዲህ ወዲህ ሞት አይኖርም፤ ሐዘንም ሆነ ጩኸት እንዲሁም ሥቃይ ከእንግዲህ ወዲህ አይኖርም። ቀድሞ የነበሩት ነገሮች አልፈዋል።”—ራእይ 21:4