በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ክርስቲያናዊ ሕይወት

አደጋ ከደረሰ በኋላ እርዳታ ማበርከት የሚቻለው እንዴት ነው?

አደጋ ከደረሰ በኋላ እርዳታ ማበርከት የሚቻለው እንዴት ነው?

በዛሬው ጊዜ የተፈጥሮ አደጋዎች በጣም የተለመዱ እየሆኑ መጥተዋል። አደጋ ሲያጋጥም የእርዳታ እንቅስቃሴው በሚገባ የተደራጀና ውጤታማ በሆነ መንገድ የተቀናጀ መሆን ይኖርበታል። ለዚህም ሲባል የበላይ አካሉ በእያንዳንዱ ቅርንጫፍ ቢሮ ውስጥ የአደጋ ጊዜ እርዳታ ዲፓርትመንት እንዲቋቋም አድርጓል።

በዚህ ዲፓርትመንት ውስጥ የሚያገለግሉት ወንድሞች አደጋ መድረሱን እንደሰሙ፣ አስፋፊዎች ምን ዓይነት እርዳታ እንደሚያስፈልጋቸው ለማወቅ በአካባቢው ያሉትን ሽማግሌዎች ያነጋግራሉ። አደጋው ያስከተለው ጉዳት በአካባቢው ካሉት አስፋፊዎች አቅም በላይ ከሆነ ቅርንጫፍ ቢሮው ብቃት ያላቸው ወንድሞች የእርዳታ ሥራውን እንዲያደራጁ ዝግጅት ያደርጋል። እነዚህ ወንድሞች፣ ፈቃደኛ የሆኑ ክርስቲያኖች በሥራው ለመካፈል ራሳቸውን እንዲያቀርቡ ወይም አንዳንድ ቁሳቁሶችን በልግስና እንዲሰጡ ሊጠይቁ ይችላሉ። ወይም ደግሞ አስፈላጊዎቹን ቁሳቁሶች ገዝተው ሊያከፋፍሉ ይችላሉ።

ሥራው በዚህ መንገድ መከናወኑ ብዙ ጥቅሞች አሉት። ወንድሞች በራሳቸው እርምጃ ቢወስዱ ከሚፈጠረው አላስፈላጊ ልፋት፣ ትርምስና የገንዘብም ሆነ የቁሳቁስ ብክነት ይጠብቃል።

ቅርንጫፍ ቢሮው የሾማቸው ወንድሞች፣ ለእርዳታ ሥራው ምን ያህል ገንዘብና ምን ያህል ፈቃደኛ ሠራተኞች እንደሚያስፈልጉ መወሰን ይችላሉ። በተጨማሪም ከአካባቢው ባለሥልጣናት ጋር ለመግባባት ጥረት ሊያደርጉ ይችላሉ፤ ይህም የእርዳታ ሥራው በተቃና መንገድ እንዲከናወን ሊረዳ ይችላል። ስለዚህ ግለሰቦች ካልተጠየቁ በቀር በራሳቸው ተነሳሽነት ገንዘብ ለማሰባሰብ፣ የእርዳታ ቁሳቁሶችን ለመላክ ወይም አደጋው ወደደረሰበት አካባቢ ለመሄድ መሞከር አይኖርባቸውም።

እውነት ነው፣ አደጋ ሲደርስ እርዳታ ማበርከት እንፈልጋለን። (ዕብ 13:16) ወንድሞቻችንን እንወዳቸዋለን! ታዲያ ምን ማድረግ እንችላለን? ከሁሉ ይበልጥ አስፈላጊ የሆነው፣ በአደጋው ለተጎዱት እንዲሁም በእርዳታ ሥራው ለሚካፈሉት ወንድሞች መጸለያችን ነው። ለዓለም አቀፉ ሥራ መዋጮ ማድረግም እንችላለን። ቅርንጫፍ ቢሮዎች በበላይ አካሉ አመራር ሥር ሆነው፣ በመዋጮ የተገኘው ገንዘብ ከሁሉ በተሻለ መንገድ ጥቅም ላይ መዋል የሚችለው እንዴት እንደሆነ መወሰን ይችላሉ። በእርዳታ ሥራው በቀጥታ መካፈል የምንፈልግ ከሆነ ደግሞ የአካባቢ ንድፍ/ግንባታ ፈቃደኛ ሠራተኞች ማመልከቻ (DC-50) በመሙላት ራሳችንን ማቅረብ እንችላለን።

በብራዚል የተከሰተው አውዳሚ የጎርፍ መጥለቅለቅ የሚለውን ቪዲዮ ተመልከት፤ ከዚያም የሚከተለውን ጥያቄ ለመመለስ ሞክር፦

በ2020 በብራዚል የጎርፍ አደጋ ከደረሰ በኋላ የይሖዋ ምሥክሮች ካከናወኑት የእርዳታ ሥራ ትኩረትህን የሳበው ምንድን ነው?