በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

እህቶች ለዘላለም በደስታ ኑር! የተባለውን ብሮሹር ለጎብኚዎች እያሳዩ፤ ከጀርባቸው “የአእምሮ ጤንነት—መጽሐፍ ቅዱስ የሚሰጠው እርዳታ” የሚለው መጠበቂያ ግንብ የፊት ገጽ ይታያል

መስከረም 19, 2023
ቦሊቪያ

በቦሊቪያ በቀረበ ዓለም አቀፍ የመጻሕፍት አውደ ርዕይ ላይ ለአእምሮ ጤና ጉዳይ ትኩረት ተሰጠ

በቦሊቪያ በቀረበ ዓለም አቀፍ የመጻሕፍት አውደ ርዕይ ላይ ለአእምሮ ጤና ጉዳይ ትኩረት ተሰጠ

ከግንቦት 31 እስከ ሰኔ 11, 2023 ቦሊቪያ ውስጥ በሳንታ ክሩዝ ዴ ላ ሲዬራ፣ የሳንታ ክሩዝ ዓለም አቀፍ የመጻሕፍት አውደ ርዕይ ተካሂዷል። አውደ ርዕዩን ከ120,000 የሚበልጡ ሰዎች ጎብኝተውታል። ለወንድሞች በተመደበው ቦታ ላይ “የአእምሮ ጤንነት—መጽሐፍ ቅዱስ የሚሰጠው እርዳታ” የሚል ርዕስ ያለው መጠበቂያ ግንብ ቁጥር 1 2023 በጉልህ ይታይ ነበር።

“የአእምሮ ጤንነት—መጽሐፍ ቅዱስ የሚሰጠው እርዳታ” የሚለው መጠበቂያ ግንብ ቁጥር 1 2023 በስፓንኛ

በአውደ ርዕዩ ላይ ወደ 200 የሚጠጉ ወንድሞችና እህቶች ለይሖዋ ምሥክሮች በተመደበው ቦታ ላይ የሠሩ ሲሆን ከ20,000 የሚበልጡ ጎብኚዎችን አነጋግረዋል። ከድረ ገጻችን ላይ የተወሰዱ ቪዲዮዎች በቴሌቪዥን ቀርበዋል፤ እንዲሁም ጎብኚዎች jw.org​ን በመጠቀም በተለያዩ ርዕሶች ላይ ምርምር ማድረግ የሚችሉት እንዴት እንደሆነ ተጠቁመዋል። ወደ 5,500 የሚሆኑ ጽሑፎች ተበርክተዋል፤ እንዲሁም 600 ገደማ ቪዲዮዎች ታይተዋል። በተጨማሪም ለይሖዋ ምሥክሮች የተመደበውን ክፍል የጎበኙ 45 ሰዎች የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት እንዲመራላቸው በ​jw.org አማካኝነት ጠይቀዋል።

የአእምሮ ጤና የሚለውን ርዕስ የተመለከተች አንዲት ሴት ወደ አንዲት እህት ቀርባ እናቷ የአእምሮና ጤና እና የስሜት መቃወስ ችግር እንዳለባት ገለጸችላት። እሷ ራሷም በጣም እንደምትጨነቅና ድባቴ እንደሚያስቸግራት ነገረቻት። እህትም ስለ አእምሮ ጤና የሚናገረውን መጠበቂያ ግንብ መጽሔት እና ለዘላለም በደስታ ኑር! ብሮሹር ስልኳ ላይ እንድታወርድት ረዳቻት። ሴትየዋም በ​jw.org ላይ ያለውን የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት መጠየቂያ ቅጽ ወዲያውኑ ሞላች።

የተለያዩ ወንድሞችና እህቶች በአውደ ርዕዩ በተመደበላቸው ቦታ ቆመው

በአውደ ርዕዩ ላይ ስለ አእምሮ ጤና የሚናገረውን መጠበቂያ ግንብ የወሰደ አንድ የሥነ ልቦና ባለሙያ እንዲህ በማለት አስተያየት ሰጥቷል፦ “በዚህ ጽሑፍ ላይ ያለውን ሐሳብ ለታካሚዎቼ ለማካፈል አስቤያለሁ። በጽሑፉ ላይ የሰፈረው መረጃና የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶቹ እንደሚጠቅሟቸው እርግጠኛ ነኝ።” እናቷን በቅርቡ በሞት ያጣች ሌላ ሴት ደግሞ jw.org ላይ “ሰላም እና ደስታ” በሚለው ዓምድ ሥር “ወላጅ ሲሞት” የሚለውን ርዕስ ስትመለከት ተበረታታለች።

በዛሬው ጊዜ ብዙዎች የአእምሮ ጤና ችግርና የስሜት መቃወስ ያጋጥማቸዋል፤ በቦሊቪያ የሚኖሩ ወንድሞቻችንና እህቶቻችን ይሖዋ በቃሉ በመጽሐፍ ቅዱስ አማካኝነት የሚሰጠውን ተግባራዊ ምክርና ማጽናኛ እንዲያገኙ ሰዎችን በመርዳታቸው ተደስተዋል።—መዝሙር 34:18