ጥር 3, 2022
ዓለም አቀፋዊ ዜና
በርካታ አገራት በይሖዋ ምሥክሮች ላይ የሚደርሰው ስደት እንዲቆም የሚጠይቅ የጋራ መግለጫ አወጡ
ታኅሣሥ 17, 2021 የዓለም አቀፉ ሃይማኖታዊ ነፃነት ወይም እምነት ኅብረት a (IRFBA) በእምነታቸው ምክንያት ስደት እየደረሰባቸው ላሉ የይሖዋ ምሥክሮች ድጋፉን ለመግለጽ የጋራ መግለጫ አወጣ። መግለጫው በእስር ላይ ያሉ ሁሉም የይሖዋ ምሥክሮች ነፃ እንዲወጡ እንዲሁም በይሖዋ ምሥክሮች ላይ እየተፈጸመ ያለው እንግልት ወይም አካላዊ ጥቃት፣ የቤት ብርበራና መድልዎ እንዲቆም የሚጠይቅ ነው።
በዓለም ዙሪያ እንደ ሲንጋፖር፣ ሩሲያ፣ ታጂኪስታን፣ ኤርትራና ክራይሚያ ባሉ አገሮች የሚኖሩ በእምነታቸው ምክንያት የታሰሩ ከ150 የሚበልጡ የይሖዋ ምሥክሮች አሉ። የዓለም አቀፉ ሃይማኖታዊ ነፃነት ወይም እምነት ኅብረት አባል አገራት ‘በይሖዋ ምሥክሮች ላይ እየደረሰ ያለው ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ የመጣ ስደት በጣም እንዳሳሰባቸው’ ገልጸዋል፤ በተጨማሪም የይሖዋ ምሥክሮች “ያለአንዳች ፍርሃት፣ ጥቃት፣ መድልዎ ወይም ስደት” እምነታቸውን የማራመድ መብት እንዳላቸው በአጽንኦት ተናግረዋል።
የአምልኮ መብታችንን ደግፈው የተናገሩትን እነዚህን ቀና አስተሳሰብ ያላቸው መንግሥታት እናደንቃለን። ከሁሉ በላይ ግን ይሖዋ በሙሉ ልባቸው በእሱ ለሚታመኑ ስደት እየደረሰባቸው ያሉ ወንድሞቻችን እና እህቶቻችን ጥበቃ ማድረጉን እንደሚቀጥል እንተማመናለን።—ኢሳይያስ 26:3