ግንቦት 4, 2022
ጋና
ተሻሽሎ የተዘጋጀው አዲስ ዓለም ትርጉም በችዊ (አሳንቴ) ቋንቋ ወጣ
እሁድ፣ ሚያዝያ 24, 2022 የበላይ አካል አባል የሆነው ወንድም ማርክ ሳንደርሰን ተሻሽሎ የተዘጋጀው አዲስ ዓለም ትርጉም መጽሐፍ ቅዱስ በችዊ (አሳንቴ) መውጣቱን አበሰረ። ልክ ንግግሩ እንዳበቃ መጽሐፍ ቅዱሱን በዲጂታል ፎርማት ማውረድ ተችሏል። የታተመውን መጽሐፍ ቅዱስ ከነሐሴ ጀምሮ ማግኘት ይቻላል።
ችዊ (አሳንቴ) እና ችዊ (አኩዋፔም) በምዕራብ አፍሪካ በሚኖሩ በሚሊዮኖች በሚቆጠሩ ሰዎች በሚነገረው የአካን የቋንቋ ቤተሰብ ውስጥ ይካተታሉ። በችዊ ቋንቋ መጽሐፍ ቅዱስ መጀመሪያ የተተረጎመው በ1871 ቢሆንም በወቅቱ የተተረጎመው በችዊ (አኩዋፔም) ብቻ ነበር። በ1897 በችዊ (አኩዋፔም) ሌላ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም ወጣ። በችዊ (አሳንቴ) ቋንቋ የመጀመሪያው የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም የወጣው በ1964 ነው። በ2012 የይሖዋ ምሥክሮች በችዊ (አሳንቴ) ቋንቋ አዲስ ዓለም ትርጉም አወጡ።
አንድ ተርጓሚ ስለ ትርጉም ሥራው ሲናገር እንዲህ ብሏል፦ “መጀመሪያ ላይ ሥራው ከአቅማችን በላይ እንደሆነ ተሰምቶን ነበር። ሆኖም በተደጋጋሚ በመጸለያችን እንዲሁም በይሖዋ መንፈስ ሙሉ በሙሉ በመታመናችን፣ በሥራው ባሳለፍነው በእያንዳንዱ ቀን የይሖዋን እጅ ተመልክተናል።”
በችዊ (አሳንቴ) የወጣው ተሻሽሎ የተዘጋጀው አዲስ ዓለም ትርጉም የችዊ ተናጋሪ የሆኑ ወንድሞቻችንና እህቶቻችን ለጋሱን አምላካችንን ይሖዋን በተሻለ ሁኔታ እንዲያገለግሉ የሚረዳ ተጨማሪ ስጦታ ነው።—ያዕቆብ 1:17