ሕዝቅኤል 4:1-17

  • የኢየሩሳሌም ከበባ በምሳሌያዊ ሁኔታ ተገለጸ (1-17)

    • በደሉን ለ390 ቀናትና ለ40 ቀናት ይሸከማል (4-7)

4  “አንተም የሰው ልጅ ሆይ፣ አንድ ጡብ ወስደህ በፊትህ አስቀምጥ። በላዩም ላይ የኢየሩሳሌምን ከተማ ቅረጽበት።  ከተማዋን ክበብ፤+ ለከበባ የሚያገለግል ግንብ ሥራባት፤+ የአፈር ቁልል ደልድልባት፤+ የጦር ሰፈሮችን ሥራባት እንዲሁም በዙሪያዋ የመደርመሻ መሣሪያዎችን ደግንባት።+  የብረት ምጣድ ወስደህ በአንተና በከተማዋ መካከል እንደ ብረት ቅጥር አቁመው። ፊትህንም በእሷ ላይ አዙር፤ ከተማዋም ትከበባለች፤ አንተም ትከባታለህ። ይህ ለእስራኤል ቤት ምልክት ይሆናል።+  “ከዚያም በግራ ጎንህ ትተኛለህ፤ የእስራኤልንም ቤት በደል በላይህ ላይ* ታኖራለህ።+ በጎንህ በተኛህበት ቀን ቁጥር በደላቸውን ትሸከማለህ።  እኔም በደል በፈጸሙባቸው ዓመታት መጠን 390 ቀናት በአንተ ላይ እመድባለሁ፤+ አንተም የእስራኤልን ቤት በደል ትሸከማለህ።  እነዚህንም ቀናት ማጠናቀቅ ይኖርብሃል። “ከዚያም ለሁለተኛ ጊዜ በቀኝ ጎንህ ትተኛለህ፤ የይሁዳንም ቤት በደል+ ለ40 ቀናት ትሸከማለህ። ለአንድ ዓመት አንድ ቀን፣ ለአንድ ዓመት አንድ ቀን ሰጥቼሃለሁ።  ክንድህን ገልጠህ ፊትህን ወደ ኢየሩሳሌም ከበባ+ ታዞራለህ፤ በእሷም ላይ ትንቢት ትናገራለህ።  “እነሆ፣ የከበባህን ጊዜ እስክታጠናቅቅ ድረስ ከአንዱ ጎንህ ወደ ሌላው መገላበጥ እንዳትችል በገመድ አስርሃለሁ።  “አንተም ስንዴ፣ ገብስ፣ ባቄላ፣ ምስር፣ ማሽላና አጃ ወስደህ በአንድ ዕቃ ውስጥ አስቀምጣቸው፤ ለራስህም ዳቦ ጋግር። በጎንህ በምትተኛባቸው 390 ቀናት ትበላዋለህ።+ 10  በየቀኑ 20 ሰቅል* እየመዘንክ ትበላለህ። በየተወሰነ ጊዜ ትበላዋለህ። 11  “ደግሞም የሂን አንድ ስድስተኛ* ለክተህ ውኃ ትጠጣለህ። በየተወሰነ ጊዜ ትጠጣዋለህ። 12  “የገብስ ሙልሙል እንደምትበላ ትበላዋለህ፤ የደረቀን የሰው ዓይነ ምድር እንደ ማገዶ ተጠቅመህ በፊታቸው ትጋግረዋለህ።” 13  ከዚያም ይሖዋ “ልክ እንደዚሁ እስራኤላውያንም እነሱን በምበትንባቸው ብሔራት መካከል የረከሰ ምግብ ይበላሉ” አለ።+ 14  ከዚያም እንዲህ አልኩ፦ “ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ ሆይ፣ ይህስ አይሁን! እኔ* ከልጅነቴ ጀምሮ እስካሁን ድረስ ሞቶ የተገኘም ሆነ አውሬ የቦጫጨቀው እንስሳ ሥጋ በልቼ የረከስኩበት ጊዜ የለም፤+ የረከሰም * ሥጋ ወደ አፌ ገብቶ አያውቅም።”+ 15  እሱም እንዲህ አለኝ፦ “መልካም፣ በሰው ዓይነ ምድር ፋንታ የከብት ኩበት እንድትጠቀም ፈቅጄልሃለሁ፤ የምትበላውንም ዳቦ በእሱ ትጋግራለህ።” 16  ከዚያም እንዲህ አለኝ፦ “የሰው ልጅ ሆይ፣ በኢየሩሳሌም የምግብ አቅርቦቱ እንዲቋረጥ አደርጋለሁ፤*+ እነሱም እየተመጠነ የሚሰጣቸውን ዳቦ በሚዛን እየለኩ በከፍተኛ ጭንቀት ይበላሉ፤+ እየተመጠነ የሚሰጣቸውንም ውኃ እየለኩ በስጋት ይጠጣሉ።+ 17  ይህም የሚሆነው ምግብና ውኃ አጥተው እርስ በርስ በድንጋጤ እንዲተያዩ እንዲሁም ከበደላቸው የተነሳ እንዲመነምኑ ነው።

የግርጌ ማስታወሻ

ቃል በቃል “በላዩ ላይ።” የሕዝቅኤልን ግራ ጎን ያመለክታል።
ወደ 230 ግራም ገደማ ነው። ከተጨማሪው መረጃ ላይ ለ14ን ተመልከት።
ወደ 0.6 ሊትር ገደማ ነው። ከተጨማሪው መረጃ ላይ ለ14ን ተመልከት።
ወይም “ነፍሴ . . . በልታ የረከሰችበት ጊዜ የለም።”
ወይም “የገማም።”
ቃል በቃል “የዳቦ በትሮቹን እሰብራለሁ።” ዳቦ ለማስቀመጥ የሚያገለግሉ በትሮችን የሚያመለክት ሳይሆን አይቀርም።