ሕዝቅኤል 44:1-31

  • የምሥራቁ በር እንደተዘጋ ይኖራል (1-3)

  • የባዕድ አገር ሰዎችን በተመለከተ የወጡ ደንቦች (4-9)

  • ሌዋውያንንና ካህናትን በተመለከተ የወጡ ደንቦች (10-31)

44  ከምሥራቅ ትይዩ ወደሆነው ወደ ውጨኛው የመቅደሱ በር ወደሚወስደው መንገድ መልሶ አመጣኝ፤+ በሩም ዝግ ነበር።+  ከዚያም ይሖዋ እንዲህ አለኝ፦ “ይህ በር እንደተዘጋ ይኖራል። መከፈት የለበትም፤ ደግሞም ማንም ሰው አይገባበትም፤ የእስራኤል አምላክ ይሖዋ በዚያ በኩል ገብቷልና፤+ ስለዚህ እንደተዘጋ ይኖራል።  አለቃው ግን አለቃ ስለሆነ በይሖዋ ፊት ምግብ ለመብላት በዚያ ይቀመጣል።+ በበሩ መተላለፊያ በረንዳ በኩል ይገባል፤ በዚያም ይወጣል።”+  ከዚያም በስተ ሰሜን በሚገኘው በር በኩል ከቤተ መቅደሱ ፊት ለፊት ወዳለው ቦታ አመጣኝ። እኔም ባየሁ ጊዜ የይሖዋ ክብር፣ የይሖዋን ቤተ መቅደስ ሞልቶት ተመለከትኩ።+ በዚህ ጊዜ በግንባሬ መሬት ላይ ተደፋሁ።+  ይሖዋም እንዲህ አለኝ፦ “የሰው ልጅ ሆይ፣ ስለ ይሖዋ ቤተ መቅደስ ደንቦችና ሕጎች የምነግርህን ሁሉ በትኩረት ተከታተል፤ በዓይኖችህም ተመልከት እንዲሁም በጥሞና አዳምጥ። የቤተ መቅደሱን መግቢያና የመቅደሱን መውጫዎች ሁሉ ልብ በል።+  ዓመፀኛ ለሆኑት የእስራኤል ቤት ሰዎች እንዲህ በላቸው፦ ‘ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ “የእስራኤል ቤት ሰዎች ሆይ፣ አስጸያፊ ልማድ መፈጸማችሁ ከእንግዲህ ይብቃ!  ልባቸውንና ሥጋቸውን ያልተገረዙትን የባዕድ አገር ሰዎች ወደ መቅደሴ ስታመጧቸው ቤተ መቅደሴን ያረክሳሉ። በምትፈጽሟቸው አስጸያፊ ልማዶች ሁሉ የተነሳ ቃል ኪዳኔ እየፈረሰ ሳለ እናንተ ግን ምግቤን ይኸውም ስቡንና ደሙን ታቀርባላችሁ።  ቅዱስ ከሆኑት ነገሮቼ ጋር በተያያዘ ያለባችሁን ኃላፊነት አልተወጣችሁም።+ ይልቁንም በመቅደሴ ውስጥ ያሉትን ሥራዎች እንዲያከናውኑ ሌሎች ሰዎችን መደባችሁ።”’  “‘ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ “ልቡንና ሥጋውን ያልተገረዘ በእስራኤል የሚኖር ማንኛውም የባዕድ አገር ሰው ወደ መቅደሴ አይግባ።”’ 10  “‘ይሁንና እስራኤላውያን አስጸያፊ የሆኑ ጣዖቶቻቸውን* ለመከተል ሲሉ ከእኔ በራቁ ጊዜ ከእኔ የራቁት ሌዋውያን+ በደላቸው የሚያስከትልባቸውን መዘዝ ይቀበላሉ። 11  ከዚያም በመቅደሴ የቤተ መቅደሱን በሮች የሚቆጣጠሩ+ እንዲሁም በቤተ መቅደሱ ውስጥ የሚያገለግሉ አገልጋዮች ይሆናሉ። ሙሉ በሙሉ የሚቃጠለውን መባና መሥዋዕት ለሕዝቡ ያርዳሉ፤ ደግሞም ሕዝቡን ለማገልገል በፊታቸው ይቆማሉ። 12  አስጸያፊ በሆኑት ጣዖቶቻቸው ፊት ስላገለገሏቸውና የእስራኤል ቤት ሰዎች ኃጢአት እንዲሠሩ የማሰናከያ ድንጋይ ስለሆኑባቸው+ በመሐላ እጄን በእነሱ ላይ አንስቻለሁ’ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ፤ ‘እነሱም የሠሩት በደል የሚያስከትልባቸውን መዘዝ ይሸከማሉ። 13  ካህናቴ ሆነው ለማገልገል ወደ እኔ አይቀርቡም፤ ደግሞም ቅዱስ ወይም እጅግ ቅዱስ ወደሆኑት ነገሮቼ አይቀርቡም፤ በሠሯቸውም አስጸያፊ ነገሮች የተነሳ የሚደርስባቸውን ኀፍረት ይሸከማሉ። 14  ይሁንና በቤተ መቅደሱ ውስጥ በኃላፊነት እንዲሠሩ ይኸውም በውስጡ የሚካሄደውን አገልግሎትና መሠራት ያለበትን ሥራ ሁሉ እንዲያከናውኑ አደርጋለሁ።’+ 15  “‘እስራኤላውያን ከእኔ በራቁ ጊዜ+ የመቅደሴን አገልግሎት ያከናውኑ የነበሩት የሳዶቅ+ ልጆች የሆኑት ሌዋውያን ካህናት ያገለግሉኝ ዘንድ ወደ እኔ ይቀርባሉ፤ ለእኔም ስቡንና+ ደሙን ለማቅረብ በፊቴ ይቆማሉ’+ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ። 16  ‘ወደ መቅደሴ የሚገቡት እነሱ ናቸው፤ እኔን ለማገልገልም ወደ ገበታዬ* ይቀርባሉ፤+ በእኔ ፊት ያለባቸውንም ኃላፊነት ይወጣሉ።+ 17  “‘ወደ ውስጠኛው ግቢ በሚያስገቡት በሮች በሚገቡበት ጊዜ በፍታ መልበስ ይኖርባቸዋል።+ በውስጠኛው ግቢ በሮች ወይም በውስጥ ባሉት ቦታዎች ሲያገለግሉ የሱፍ ልብስ መልበስ የለባቸውም። 18  በራሳቸው ላይ ከበፍታ የተሠራ ጥምጥም ያድርጉ፤ በወገባቸውም ላይ የበፍታ ቁምጣ ይታጠቁ።+ እንዲያልባቸው የሚያደርግ ማንኛውም ዓይነት ልብስ መልበስ የለባቸውም። 19  ወደ ውጨኛው ግቢ ይኸውም ሕዝቡ ወዳለበት ግቢ ከመውጣታቸው በፊት አገልግሎታቸውን ሲያከናውኑ ለብሰውት የነበረውን ልብስ አውልቀው+ ቅዱስ በሆኑት የመመገቢያ ክፍሎች*+ ውስጥ ማስቀመጥ አለባቸው። ከዚያም ቅድስናን ወደ ሕዝቡ እንዳያስተላልፉ* ሌላ ልብስ ይለብሳሉ። 20  ራሳቸውን አይላጩ፤+ ወይም ፀጉራቸውን አያስረዝሙ። ይልቁንም ፀጉራቸውን ይከርክሙ። 21  ካህናቱ ወደ ውስጠኛው ግቢ በሚገቡበት ጊዜ የወይን ጠጅ አይጠጡ።+ 22  መበለት የሆነች ወይም ከባሏ የተፋታች ሴት አያግቡ፤+ ይሁንና የእስራኤል ዘር የሆነች ድንግል ወይም የካህን ሚስት የነበረች መበለት ማግባት ይችላሉ።’+ 23  “‘ቅዱስ በሆነና ተራ በሆነ ነገር መካከል ያለውን ልዩነት ለሕዝቤ ያስተምሩ፤ ንጹሕ ባልሆነውና ንጹሕ በሆነው ነገር መካከል ያለውንም ልዩነት ያሳውቋቸው።+ 24  ፍርድ ነክ ጉዳዮችን ይዳኙ፤+ በድንጋጌዎቼ መሠረት ይፍረዱ።+ ከሁሉም በዓሎቼ ጋር የተያያዙትን ሕጎቼንና ደንቦቼን ይጠብቁ፤+ እንዲሁም ሰንበቶቼን ይቀድሱ። 25  ወደ ሞተ ሰው አይቅረቡ፤ አለዚያ ይረክሳሉ። ሆኖም ለአባታቸው፣ ለእናታቸው፣ ለወንድ ወይም ለሴት ልጃቸው፣ ለወንድማቸው ወይም ላላገባች እህታቸው ሲሉ ራሳቸውን ሊያረክሱ ይችላሉ።+ 26  ደግሞም አንድ ካህን ከነጻ በኋላ ለሰባት ቀን ሊያቆዩት ይገባል። 27  በተቀደሰው ስፍራ ለማገልገል፣ በውስጠኛው ግቢ ወደሚገኘው ቅዱስ ስፍራ በሚገባበት ቀን የኃጢአት መባውን ያቅርብ’+ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ። 28  “‘የእነሱም ውርሻ ይህ ይሆናል፦ ውርሻቸው እኔ ነኝ።+ በእስራኤል ምንም ዓይነት ርስት አትስጧቸው፤ ርስታቸው እኔ ነኝና። 29  የእህሉን መባ፣+ የኃጢአቱን መባና የበደሉን መባ ይበላሉ፤+ በእስራኤል ምድር ቅዱስ ለሆነ ነገር የተለየ ሁሉ የእነሱ ይሆናል።+ 30  መጀመሪያ ላይ ከደረሱት ፍሬዎች ሁሉና መዋጮ አድርጋችሁ ከምትሰጡት ነገር ሁሉ ምርጥ የሆነው ለካህናቱ ይሆናል።+ የተፈጨውንም የእህል በኩር ለካህኑ ስጡ።+ እንዲህ የምታደርጉ ከሆነ ቤተሰቦቻችሁ ይባረካሉ።+ 31  ካህናቱ ሞቶ የተገኘውንም ሆነ በአራዊት የተዘነጠለውን ማንኛውም ወፍ ወይም እንስሳ መብላት የለባቸውም።’+

የግርጌ ማስታወሻ

እዚህ ላይ የገባው የዕብራይስጥ ቃል “ፋንድያ” ከሚለው ቃል ጋር ዝምድና ሊኖረው የሚችል ሲሆን ንቀትን ለማመልከት ተሠርቶበታል።
ወይም “መሠዊያዬ።”
ወይም “ቅዱስ በሆኑት ክፍሎች።”
ቃል በቃል “ሕዝቡን እንዳይቀድሱ።”