መሳፍንት 8:1-35

  • ኤፍሬማውያን ከጌድዮን ጋር ተጣሉ (1-3)

  • ምድያማውያን ነገሥታትን አሳደው በመያዝ ገደሏቸው (4-21)

  • ጌድዮን ሊያነግሡት ሲሉ እንቢ አለ (22-27)

  • የጌድዮን ሕይወት (28-35)

8  ከዚያም የኤፍሬም ሰዎች ጌድዮንን “እንዴት እንዲህ ያለ ነገር ታደርግብናለህ? ከምድያማውያን ጋር ለመዋጋት ስትወጣ ያልጠራኸን ለምንድን ነው?”+ አሉት። የመረረ ጥልም ተጣሉት።+  እሱ ግን እንዲህ አላቸው፦ “እናንተ ካደረጋችሁት ጋር ሲነጻጸር እኔ ምን አደረግኩ? የኤፍሬም ቃርሚያ+ ከአቢዔዜር+ የወይን መከር አይሻልም?  አምላክ የምድያማውያንን መኳንንት ኦሬብን እና ዜብን አሳልፎ የሰጠው ለእናንተ ነው፤+ ታዲያ እናንተ ካደረጋችሁት ጋር ሲነጻጸር እኔ ምን አደረግኩ?” እነሱም በዚህ መንገድ ሲያነጋግራቸው* ቁጣቸው በረደ።*  ከዚያም ጌድዮን ወደ ዮርዳኖስ መጥቶ ወንዙን ተሻገረ። እሱም ሆነ ከእሱ ጋር የነበሩት 300 ሰዎች ደክሟቸው የነበረ ቢሆንም ጠላቶቻቸውን ከማሳደድ ወደኋላ አላሉም ነበር።  ስለዚህ ጌድዮን የሱኮትን ሰዎች “የምድያማውያን ነገሥታት የሆኑትን ዘባህን እና ጻልሙናን በማሳደድ ላይ ስለሆንኩና የሚከተሉኝም ሰዎች ስለደከማቸው እባካችሁ ዳቦ ስጧቸው” አላቸው።  የሱኮት መኳንንት ግን “ለሠራዊትህ ዳቦ የምንሰጠው ለመሆኑ የዘባህ እና የጻልሙና መዳፍ እጅህ ገብቷል?” አሉት።  በዚህ ጊዜ ጌድዮን “እንግዲያው ይሖዋ ዘባህን እና ጻልሙናን በእጄ አሳልፎ ሲሰጠኝ በምድረ በዳ እሾህና አሜኬላ ሥጋችሁን እተለትላለሁ”+ አላቸው።  ከዚያም ወደ ጰኑኤል ወጣ፤ ለእነሱም ተመሳሳይ ጥያቄ አቀረበላቸው፤ የጰኑኤል ሰዎችም የሱኮት ሰዎች የሰጡትን ዓይነት መልስ ሰጡት።  ስለዚህ የጰኑኤልንም ሰዎች “በሰላም በምመለስበት ጊዜ ይህን ግንብ አፈርሰዋለሁ”+ አላቸው። 10  በዚህ ጊዜ ዘባህ እና ጻልሙና ከሠራዊታቸው ጋር በቃርቆር ሰፍረው ነበር፤ የሠራዊቱም ቁጥር ወደ 15,000 ገደማ ነበር። ቀደም ሲል 120,000 የሚያህሉ ሰይፍ የታጠቁ ወንዶች ተገድለው ስለነበር ከመላው የምሥራቅ ሰዎች+ ሠራዊት የቀሩት እነዚህ ብቻ ነበሩ። 11  ጌድዮንም ከኖባህ እና ከዮግበሃ+ በስተ ምሥራቅ የሚኖሩ ዘላኖች የሚሄዱበትን መንገድ ተከትሎ ወጣ፤ የጠላት ሠራዊት ተዘናግቶ ባለበትም ወቅት በሰፈሩ ላይ ጥቃት ሰነዘረ። 12  ሁለቱ ምድያማውያን ነገሥታት ማለትም ዘባህ እና ጻልሙና በሸሹም ጊዜ አሳዶ ያዛቸው፤ መላውን ሠራዊትም አሸበረው። 13  ከዚያም የዮአስ ልጅ ጌድዮን ወደ ሄሬስ ሽቅብ በሚያስወጣው መንገድ በኩል አድርጎ ከውጊያው ተመለሰ። 14  እሱም በመንገድ ላይ የሱኮት ሰው የሆነ አንድ ወጣት ያዘ፤ እሱንም መረመረው። በመሆኑም ወጣቱ የሱኮት መኳንንትና ሽማግሌዎች የሆኑ የ77 ሰዎችን ስም ጻፈለት። 15  ጌድዮንም ወደ ሱኮት ሰዎች ሄዶ “‘ለደከሙት ሰዎችህ ዳቦ የምንሰጠው ለመሆኑ የዘባህ እና የጻልሙና መዳፍ እጅህ ገብቷል?’ በማለት የተሳለቃችሁብኝ ዘባህ እና ጻልሙና እነዚሁላችሁ” አላቸው።+ 16  ከዚያም የከተማዋን ሽማግሌዎች ወሰደ፤ በምድረ በዳ እሾህና አሜኬላም ለሱኮት ሰዎች ትምህርት ሰጣቸው።+ 17  እንዲሁም የጰኑኤልን ግንብ አፈረሰ፤+ የከተማዋንም ሰዎች ገደለ። 18  ጌድዮንም ዘባህን እና ጻልሙናን “ለመሆኑ በታቦር የገደላችኋቸው ሰዎች ምን ዓይነት ነበሩ?” አላቸው። እነሱም መልሰው “እንደ አንተ ዓይነት ነበሩ፤ እያንዳንዳቸውም የንጉሥ ልጅ ይመስሉ ነበር” አሉት። 19  በዚህ ጊዜ “እነሱ የእናቴ ልጆች ወንድሞቼ ነበሩ። ሕያው በሆነው በይሖዋ እምላለሁ፣ በሕይወት ትታችኋቸው ቢሆን ኖሮ አልገድላችሁም ነበር” አላቸው። 20  ከዚያም የበኩር ልጁን የቴርን “ተነስ፤ ግደላቸው” አለው። ወጣቱ ግን ሰይፉን አልመዘዘም፤ ምክንያቱም ገና ወጣት ስለሆነ ፈርቶ ነበር። 21  በመሆኑም ዘባህ እና ጻልሙና “የሰው ማንነት የሚለካው በኃይሉ ስለሆነ አንተው ራስህ ተነስና ግደለን” አሉት። በመሆኑም ጌድዮን ተነስቶ ዘባህን እና ጻልሙናን+ ገደላቸው፤ በግመሎቻቸው አንገት ላይ የነበሩትንም የሩብ ጨረቃ ቅርጽ ያላቸው ጌጣጌጦች ወሰደ። 22  ከጊዜ በኋላም የእስራኤል ሰዎች ጌድዮንን “ከምድያማውያን እጅ ስለታደግከን አንተ፣ ልጆችህና የልጅ ልጆችህ ግዙን” አሉት።+ 23  ጌድዮን ግን “እኔ አልገዛችሁም፤ ልጄም ቢሆን አይገዛችሁም። የሚገዛችሁ ይሖዋ ነው”+ አላቸው። 24  ከዚያም ጌድዮን “አንድ ነገር ልጠይቃችሁ፦ እያንዳንዳችሁ በምርኮ ካገኛችሁት ላይ የአፍንጫ ሎቲዎችን ስጡኝ” አላቸው። (ምክንያቱም ድል የሆኑት ሕዝቦች እስማኤላውያን+ ስለነበሩ የወርቅ የአፍንጫ ሎቲዎች ነበሯቸው።) 25  እነሱም “በደስታ እንሰጣለን” አሉት። ከዚያም መጎናጸፊያ አነጠፉ፤ እያንዳንዱም ሰው በምርኮ ካገኘው ውስጥ የአፍንጫ ሎቲውን እዚያ ላይ ጣለ። 26  የሩብ ጨረቃ ቅርጽ ካላቸው ጌጣጌጦች፣ ከአንገት ሐብል ማጫወቻዎች፣ የምድያም ነገሥታት ይለብሷቸው ከነበሩት ቀይ ሐምራዊ ቀለም የተነከሩ የሱፍ ልብሶች እንዲሁም በግመሎቹ ላይ ከነበሩት የአንገት ጌጦች በተጨማሪ እንዲሰጡት የጠየቃቸው የወርቅ የአፍንጫ ሎቲዎች ክብደት 1,700 የወርቅ ሰቅል* ነበር።+ 27  ጌድዮንም በወርቁ ኤፉድ+ ሠራ፤ ሰዎች እንዲያዩትም በከተማው በኦፍራ+ አስቀመጠው፤ እስራኤላውያንም በሙሉ በዚያ ከእሱ ጋር መንፈሳዊ ምንዝር ፈጸሙ፤+ ኤፉዱም ለጌድዮንና ለቤተሰቡ ወጥመድ ሆነ።+ 28  በዚህ መንገድ ምድያማውያን+ ለእስራኤላውያን ተገዙ፤ ከዚያ በኋላም ተገዳድረዋቸው አያውቁም፤* በጌድዮን ዘመን ምድሪቱ ለ40 ዓመት አረፈች።* + 29  የዮአስ ልጅ የሩባአልም+ ወደ ቤቱ ተመልሶ በዚያ መኖሩን ቀጠለ። 30  ጌድዮንም ብዙ ሚስቶች ስለነበሩት 70 ወንዶች ልጆች* ነበሩት። 31  በሴኬም የነበረችው ቁባቱም ወንድ ልጅ ወለደችለት፤ እሱም ስሙን አቢሜሌክ+ አለው። 32  የዮአስ ልጅ ጌድዮንም ዕድሜ ጠግቦ ሞተ፤ የአቢዔዜራውያን+ በሆነችው በኦፍራ በሚገኘው በአባቱ በዮአስ መቃብር ተቀበረ። 33  እስራኤላውያን ጌድዮን ከሞተ ብዙም ሳይቆይ እንደገና ከባአል ጋር መንፈሳዊ ምንዝር ፈጸሙ፤+ ባአልበሪትንም አምላካቸው አደረጉት።+ 34  እስራኤላውያንም በዙሪያቸው ከነበሩት ጠላቶቻቸው ሁሉ እጅ የታደጋቸውን+ አምላካቸውን ይሖዋን አላስታወሱም፤+ 35  እንዲሁም የሩባአል የተባለው ጌድዮን ለእስራኤል ያደረገውን ጥሩ ነገር ሁሉ አስበው ለቤተሰቡ ታማኝ ፍቅር አላሳዩም።+

የግርጌ ማስታወሻ

ቃል በቃል “ይህን ቃል ሲነግራቸው።”
ቃል በቃል “መንፈሳቸው እሱን ከመቃወም በረደ።”
አንድ ሰቅል 11.4 ግራም ነው። ከተጨማሪው መረጃ ላይ ለ14ን ተመልከት።
ቃል በቃል “ራሳቸውን ቀና አላደረጉም።”
ወይም “ሰላም አገኘች።”
ቃል በቃል “ከጭኑ የወጡ 70 ወንዶች ልጆች።”