ሚልክያስ 1:1-14

  • ይሖዋ ለሕዝቡ ያለው ፍቅር (1-5)

  • እንከን ያለበት መሥዋዕት ያቀረቡ ካህናት (6-14)

    • የአምላክ ስም በብሔራት መካከል ታላቅ ይሆናል (11)

1  የፍርድ መልእክት፦ በሚልክያስ* በኩል ለእስራኤል የተነገረው የይሖዋ ቃል ይህ ነው፦  “እኔ ፍቅር አሳይቻችኋለሁ”+ ይላል ይሖዋ። እናንተ ግን “ፍቅር ያሳየኸን እንዴት ነው?” አላችሁ። “ኤሳው የያዕቆብ ወንድም አልነበረም?”+ ይላል ይሖዋ። “እኔ ግን ያዕቆብን ወደድኩ፤  ኤሳውንም ጠላሁ፤+ ተራሮቹን ባድማ አደረግኩ፤+ ርስቱንም ለምድረ በዳ ቀበሮዎች ሰጠሁ።”+  “ኤዶም* ‘ተደምስሰናል፤ ሆኖም ተመልሰን የፈራረሱትን ዳግመኛ እንገነባለን’ ቢልም የሠራዊት ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ ‘እነሱ ይገነባሉ፤ እኔ ግን አፈርሳለሁ፤ ቦታዎቹ “የክፋት ምድር፣” እነሱ ደግሞ “ይሖዋ ለዘላለም ያወገዘው ሕዝብ” ተብለው ይጠራሉ።+  የገዛ ዓይናችሁ ይህን ያያል፤ እናንተም “ይሖዋ በእስራኤል ምድር ከፍ ከፍ ይበል” ትላላችሁ።’”  “እናንተ ስሜን የምታቃልሉ ካህናት ሆይ፣+ ‘ልጅ አባቱን፣ አገልጋይም ጌታውን ያከብራል።+ እኔ አባት ከሆንኩ+ ለእኔ የሚገባው ክብር የት አለ?+ ጌታስ* ከሆንኩ መፈራቴ* የት አለ?’ ይላል የሠራዊት ጌታ ይሖዋ። “‘እናንተ ግን “ስምህን ያቃለልነው እንዴት ነው?” ትላላችሁ።’  “‘በመሠዊያዬ ላይ የረከሰ ምግብ* በማቅረብ ነው።’ “‘ደግሞም “ያረከስንህ እንዴት ነው?” ትላላችሁ።’ “‘“የይሖዋ ገበታ+ የተናቀ ነው” በማለታችሁ ነው።  ዕውሩን እንስሳ መሥዋዕት አድርጋችሁ ስታቀርቡ “ምንም ችግር የለውም” ትላላችሁ። ደግሞም አንካሳ ወይም የታመመ እንስሳ ስታቀርቡ “ምንም ችግር የለውም” ትላላችሁ።’”+ “እነዚህን እንስሳት እስቲ ለገዢህ ለማቅረብ ሞክር። በአንተ ደስ ይለዋል? ወይስ በሞገስ ዓይን ይቀበልሃል?” ይላል የሠራዊት ጌታ ይሖዋ።  “አሁንም እባካችሁ፣ ሞገስ እንዲያሳየን አምላክን ተማጸኑ። እንዲህ ያሉ መባዎች በገዛ እጃችሁ ስታቀርቡ ከእናንተ መካከል የእሱን ሞገስ የሚያገኝ ይኖራል?” ይላል የሠራዊት ጌታ ይሖዋ። 10  “ከእናንተ መካከል በሮቹን ለመዝጋት ፈቃደኛ የሚሆን ማን ነው?*+ በመሠዊያዬ ላይ እሳት ለማንደድ እንኳ ክፍያ ትጠይቃላችሁና።+ በእናንተ ፈጽሞ ደስ አልሰኝም” ይላል የሠራዊት ጌታ ይሖዋ፤ “ስጦታ አድርጋችሁ በምታቀርቡት በየትኛውም መባ አልደሰትም።”+ 11  “ከፀሐይ መውጫ እስከ ፀሐይ መግቢያ* ድረስ ስሜ በብሔራት መካከል ታላቅ ይሆናል።+ በየቦታው ለስሜ የሚጨስ መሥዋዕትና መባ ተቀባይነት ያለው ስጦታ ሆኖ ይቀርባል፤ ምክንያቱም ስሜ በብሔራት መካከል ታላቅ ይሆናል”+ ይላል የሠራዊት ጌታ ይሖዋ። 12  “እናንተ ግን ‘የይሖዋ ገበታ የረከሰ ነው፤ ፍሬው ይኸውም ምግቡ የተናቀ ነው’ በማለት ታረክሱታላችሁ።*+ 13  በተጨማሪም እናንተ ‘እንዴት አድካሚ ነው!’ ትላላችሁ፤ ደግሞም ትጸየፉታላችሁ” ይላል የሠራዊት ጌታ ይሖዋ። “የተሰረቀን፣ አንካሳውንና የታመመውን እንስሳ ታመጣላችሁ። አዎ፣ እንዲህ ያሉ ነገሮችን ስጦታ አድርጋችሁ ታቀርባላችሁ! ታዲያ ይህን ከእጃችሁ ልቀበል ይገባል?”+ ይላል ይሖዋ። 14  “በመንጎቹ መካከል ተባዕት እንስሳ እያለው፣ ስእለት ተስሎ እንከን ያለበትን ለይሖዋ መሥዋዕት አድርጎ በማቅረብ የሚያታልል የተረገመ ነው። እኔ ታላቅ ንጉሥ ነኝና”+ ይላል የሠራዊት ጌታ ይሖዋ፤ “ስሜም በብሔራት መካከል የተፈራ ይሆናል።”+

የግርጌ ማስታወሻ

“መልእክተኛዬ” የሚል ትርጉም አለው።
ዘፍ 25:30 እና ዘፍ 36:1 ላይ በተገለጸው መሠረት ኤዶም የኤሳው ሁለተኛ ስም ነው።
ወይም “ታላቅ ጌታስ።”
ወይም “መከበሬ።”
ቃል በቃል “ዳቦ።”
ኃላፊነት ወስዶ የቤተ መቅደሱን በሮች ለመዝጋት ፈቃደኛ መሆንን ያመለክታል።
ወይም “ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ።”
“እኔን ታረክሳላችሁ” ማለትም ሊሆን ይችላል።