ለዮሐንስ የተገለጠለት ራእይ 19:1-21

  • ለወሰደው የፍርድ እርምጃ “ያህን አወድሱ!” (1-10)

    • የበጉ ሠርግ (7-9)

  • የነጭ ፈረስ ጋላቢ (11-16)

  • “ታላቁ የአምላክ ራት” (17, 18)

  • አውሬው ድል ተነሳ (19-21)

19  ከዚህ በኋላ በሰማይ እንደ ብዙ ሠራዊት ድምፅ ያለ ታላቅ ድምፅ ሰማሁ። እንዲህም አሉ፦ “ያህን አወድሱ!*+ ማዳን፣ ክብርና ኃይል የአምላካችን ነው፤  ምክንያቱም ፍርዶቹ እውነትና ጽድቅ ናቸው።+ ምድርን በዝሙቷ* ባረከሰችው በታላቂቱ አመንዝራ ላይ የፍርድ እርምጃ ወስዷልና፤ እንዲሁም ስለ ባሪያዎቹ ደም ተበቅሏታል።”*+  ወዲያውኑም ለሁለተኛ ጊዜ “ያህን አወድሱ!*+ ከእሷ የሚወጣው ጭስም ለዘላለም ወደ ላይ ይወጣል” አሉ።+  ደግሞም 24ቱ ሽማግሌዎችና+ አራቱ ሕያዋን ፍጥረታት+ ተደፍተው በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው አምላክ ሰገዱ፤ እንዲሁም “አሜን! ያህን አወድሱ!”* አሉ።+  በተጨማሪም ከዙፋኑ የወጣ አንድ ድምፅ “እሱን የምትፈሩ ባሪያዎቹ ሁሉ፣+ ታናናሾችና ታላላቆች፣+ አምላካችንን አወድሱ” አለ።  እንደ ብዙ ሠራዊት ድምፅ፣ እንደ ብዙ ውኃዎች ድምፅና እንደ ኃይለኛ ነጎድጓድ ድምፅ ያለ ነገር ሰማሁ። እንዲህም አሉ፦ “ያህን አወድሱ፤*+ ምክንያቱም ሁሉን ቻይ የሆነው አምላካችን ይሖዋ*+ ነግሦአል!+  የበጉ ሠርግ ስለደረሰና ሙሽራዋ ራሷን ስላዘጋጀች እንደሰት፤ ሐሴትም እናድርግ፤ ለእሱም ክብር እንስጠው።  አዎ፣ የሚያንጸባርቅና ንጹሕ የሆነ ጥሩ በፍታ እንድትለብስ ተሰጥቷታል፤ ይህ ጥሩ በፍታ የቅዱሳንን የጽድቅ ተግባር ያመለክታልና።”+  እሱም “ይህን ጻፍ፦ ወደ በጉ ሠርግ+ የራት ግብዣ የተጠሩ ደስተኞች ናቸው” አለኝ። ደግሞም “እነዚህ እውነተኛ የአምላክ ቃሎች ናቸው” አለኝ። 10  እኔም በዚህ ጊዜ ልሰግድለት በእግሩ ፊት ተደፋሁ። እሱ ግን “ተጠንቀቅ! ፈጽሞ እንዳታደርገው!+ እኔ ከአንተም ሆነ ስለ ኢየሱስ የመመሥከር ሥራ ካላቸው ወንድሞችህ ጋር አብሬ የማገለግል ባሪያ ነኝ።+ ለአምላክ ስገድ!+ ትንቢት የሚነገረው ስለ ኢየሱስ ለመመሥከር ነውና” አለኝ።+ 11  እኔም ሰማይ ተከፍቶ አየሁ፤ እነሆም፣ ነጭ ፈረስ ነበር።+ በእሱም ላይ የተቀመጠው “ታማኝና+ እውነተኛ”+ ተብሎ ይጠራል፤ እሱም በጽድቅ ይፈርዳል እንዲሁም ይዋጋል።+ 12  ዓይኖቹ የእሳት ነበልባል ናቸው፤+ በራሱም ላይ ብዙ ዘውዶች አሉ። ከራሱ በቀር ማንም የማያውቀው ስም ተጽፎበታል፤ 13  ደም የነካው* መደረቢያም ለብሷል፤ ደግሞም “የአምላክ ቃል”+ በሚል ስም ይጠራል። 14  በተጨማሪም በሰማይ ያሉት ሠራዊቶች በነጭ ፈረሶች ተቀምጠው ይከተሉት ነበር፤ እነሱም ነጭና ንጹሕ የሆነ ጥሩ በፍታ ለብሰው ነበር። 15  እሱም ብሔራትን ይመታበት ዘንድ ከአፉ ረጅም ስለታም ሰይፍ+ ይወጣል፤ እንደ እረኛም በብረት በትር ይገዛቸዋል።*+ በተጨማሪም ሁሉን ቻይ የሆነውን የአምላክን የመዓቱን የቁጣ ወይን ጠጅ መጭመቂያ ይረግጣል።+ 16  በመደረቢያው አዎ፣ በጭኑ ላይ “የነገሥታት ንጉሥና የጌቶች ጌታ”+ የሚል ስም ተጽፏል። 17  በተጨማሪም አንድ መልአክ በፀሐይ መካከል ቆሞ አየሁ፤ እሱም በታላቅ ድምፅ ጮኾ በሰማይ መካከል* ለሚበርሩት ወፎች ሁሉ እንዲህ አለ፦ “ወደዚህ ኑ፤ ወደ ታላቁ የአምላክ ራት ተሰብሰቡ፤+ 18  የነገሥታትን ሥጋ፣ የጦር አዛዦችን ሥጋ፣ የብርቱ ሰዎችን ሥጋ፣+ የፈረሶችንና የፈረሰኞችን ሥጋ+ እንዲሁም የሁሉንም ሥጋ ይኸውም የነፃ ሰዎችንና የባሪያዎችን፣ የታናናሾችንና የታላላቆችን ሥጋ ብሉ።” 19  ከዚህ በኋላ አውሬው፣ የምድር ነገሥታትና ሠራዊታቸው በፈረሱ ላይ ከተቀመጠውና ከሠራዊቱ ጋር ለመዋጋት ተሰብስበው አየሁ።+ 20  አውሬውም ተያዘ፤ በፊቱ ተአምራዊ ምልክቶች የፈጸመው ሐሰተኛው ነቢይም+ ከእሱ ጋር ተያዘ፤ ይህ ነቢይ በእነዚህ ምልክቶች አማካኝነት፣ የአውሬውን ምስል የተቀበሉትንና+ ለምስሉ የሰገዱትን+ አስቷል። ሁለቱም በሕይወት እንዳሉ በድኝ ወደሚነደው የእሳት ሐይቅ ተወረወሩ።+ 21  የቀሩት ግን በፈረሱ ላይ ከተቀመጠው አፍ በወጣው ረጅም ሰይፍ ተገደሉ።+ ወፎችም ሁሉ ሥጋቸውን በልተው ጠገቡ።+

የግርጌ ማስታወሻ

ወይም “ሃሌሉያህ!” “ያህ” የይሖዋ ስም አጭር መጠሪያ ነው።
ግሪክኛ፣ ፖርኒያ። የቃላት መፍቻው ላይ “የፆታ ብልግና” የሚለውን ተመልከት።
ቃል በቃል “(የባሪያዎቹን ደም) ከእጇ ተበቅሏል።”
ወይም “ሃሌሉያህ!” “ያህ” የይሖዋ ስም አጭር መጠሪያ ነው።
ወይም “ሃሌሉያህ!” “ያህ” የይሖዋ ስም አጭር መጠሪያ ነው።
ወይም “ሃሌሉያህ!” “ያህ” የይሖዋ ስም አጭር መጠሪያ ነው።
ከተጨማሪው መረጃ ላይ ሀ5ን ተመልከት።
“ደም የተረጨበት” ማለትም ሊሆን ይችላል።
ቃል በቃል “እንደ እረኛ በብረት በትር ያግዳቸዋል።”
ወይም “በአየር ላይ፤ ከላይ።”