ለሮም ሰዎች የተጻፈ ደብዳቤ 9:1-33

  • ጳውሎስ ለሥጋዊ እስራኤላውያን አዘነላቸው (1-5)

  • የአብርሃም እውነተኛ ዘር (6-13)

  • የአምላክን ምርጫ በተመለከተ ጥያቄ ማንሳት አንችልም (14-26)

    • የቁጣና የምሕረት ዕቃዎች (22, 23)

  • “የሚድኑት ቀሪዎች ብቻ ናቸው” (27-29)

  • እስራኤል ተሰናከለ (30-33)

9  የክርስቶስ ተከታይ እንደመሆኔ መጠን የምናገረው እውነት ነው፤ ሕሊናዬ በመንፈስ ቅዱስ እየተመራ ከእኔ ጋር ሆኖ ስለሚመሠክር አልዋሽም፤  ታላቅ ሐዘንና የማያቋርጥ ሥቃይ በልቤ ውስጥ አለ።  የሥጋ ዘመዶቼ ስለሆኑት ስለ ወንድሞቼ ስል እኔ ራሴ የተረገምኩ ሆኜ ከክርስቶስ ብለይ በወደድኩ ነበርና።  እነሱ እስራኤላውያን ናቸው፤ አምላክ ልጆቹ አድርጎ የወሰዳቸው፣+ ክብር ያገኙት፣ ቃል ኪዳን የተገባላቸው፣+ ሕግ የተሰጣቸው፣+ ቅዱስ አገልግሎት የማቅረብ መብት ያገኙትና+ ተስፋ የተሰጣቸው+ እነሱ ናቸው።  አባቶችም የእነሱ ናቸው፤+ ክርስቶስም በሥጋ የተገኘው ከእነሱ ነው።+ የሁሉ የበላይ የሆነው አምላክ ለዘላለም ይወደስ። አሜን።  ይሁን እንጂ የአምላክ ቃል ከንቱ ሆኖ ቀርቷል ማለት አይደለም። ከእስራኤል የተወለደ ሁሉ በእርግጥ “እስራኤል” አይደለምና።+  በተጨማሪም የአብርሃም ዘር ስለሆኑ+ ሁሉም ልጆቹ ናቸው ማለት አይደለም፤ ከዚህ ይልቅ “ዘርህ የሚጠራልህ በይስሐቅ በኩል ይሆናል” ተብሎ ተጽፏል።+  ይህም ሲባል በሥጋ ልጆች የሆኑ በእርግጥ የአምላክ ልጆች አይደሉም፤+ በተስፋው ልጆች+ የሆኑት ግን ዘሩ እንደሆኑ ተደርገው ይቆጠራሉ።  የተስፋው ቃል “የዛሬ ዓመት በዚህ ጊዜ እመጣለሁ፤ ሣራም ወንድ ልጅ ትወልዳለች” ይላልና።+ 10  ተስፋው የተሰጠው በዚያን ጊዜ ብቻ ሳይሆን ርብቃ ከአባታችን ከይስሐቅ መንታ ልጆች በፀነሰች ጊዜ ጭምር ነው፤+ 11  ምርጫውን በተመለከተ የአምላክ ዓላማ በሥራ ሳይሆን በጠሪው ላይ የተመካ ሆኖ ይቀጥል ዘንድ ልጆቹ ከመወለዳቸውና ጥሩም ሆነ ክፉ ከማድረጋቸው በፊት 12  ርብቃ “ታላቁ የታናሹ ባሪያ ይሆናል” ተብሎ ተነግሯት ነበር።+ 13  ይህም “ያዕቆብን ወደድኩ፤ ኤሳውን ግን ጠላሁ” ተብሎ እንደተጻፈው ነው።+ 14  እንግዲህ ምን እንበል? አምላክ ፍትሕ ያዛባል ማለት ነው? በፍጹም!+ 15  ሙሴን “ልምረው የምፈልገውን እምረዋለሁ፤ ልራራለት የምፈልገውን ደግሞ እራራለታለሁ” ብሎታልና።+ 16  ስለዚህ ይህ የተመካው በአንድ ሰው ፍላጎት ወይም ጥረት* ሳይሆን ምሕረት በሚያደርገው አምላክ ላይ ነው።+ 17  ቅዱስ መጽሐፉ ስለ ፈርዖን ሲናገር “በሕይወት ያቆየሁህ ኃይሌን በአንተ ለማሳየትና ስሜ በመላው ምድር እንዲታወጅ ለማድረግ ነው” ይላል።+ 18  ስለዚህ አምላክ የፈለገውን ይምራል፤ የፈለገውን ደግሞ ግትር እንዲሆን ይፈቅዳል።+ 19  በመሆኑም “እንደዚህ ከሆነ ታዲያ ሰዎችን ለምን ይወቅሳል?* ደግሞስ ፈቃዱን ማን መቃወም ይችላል?” ትለኝ ይሆናል። 20  ለመሆኑ ለአምላክ የምትመልሰው አንተ ማን ነህ?+ አንድ ዕቃ ቅርጽ አውጥቶ የሠራውን ሰው “ለምን እንዲህ አድርገህ ሠራኸኝ?” ይለዋል?+ 21  ሸክላ ሠሪው ከዚያው ከአንዱ ጭቃ፣ አንዱን ዕቃ ክቡር ለሆነ አገልግሎት ሌላውን ዕቃ ደግሞ ክብር ለሌለው አገልግሎት ለመሥራት በጭቃው ላይ ሥልጣን እንዳለው+ አታውቅም? 22  አምላክ ቁጣውን ለማሳየትና ኃይሉ እንዲታወቅ ለማድረግ ቢፈልግም እንኳ ጥፋት የሚገባቸውን የቁጣ ዕቃዎች በብዙ ትዕግሥት ችሏቸው እንደሆነስ ምን ታውቃለህ? 23  ይህን ያደረገው ታላቅ ክብሩን አስቀድሞ ለክብር ባዘጋጃቸው የምሕረት ዕቃዎች+ ላይ ለመግለጥ 24  ይኸውም ከአይሁዳውያን ብቻ ሳይሆን ከአሕዛብም+ በጠራን በእኛ ላይ ታላቅ ክብሩን ለመግለጥ ቢሆንስ? 25  ይህም በሆሴዕ መጽሐፍ ላይ እንዲህ ብሎ እንደተናገረው ነው፦ “ሕዝቤ ያልሆኑትን+ ‘ሕዝቤ’ ብዬ፣ ያልተወደደችውንም ‘የተወደደች’+ ብዬ እጠራለሁ፤ 26  ‘ሕዝቤ አይደላችሁም’ ተብሎ በተነገራቸው ስፍራም በዚያ ‘የሕያው አምላክ ልጆች’ ተብለው ይጠራሉ።”+ 27  ከዚህም በተጨማሪ ኢሳይያስ ስለ እስራኤል እንዲህ ሲል ድምፁን ከፍ አድርጎ ይናገራል፦ “የእስራኤል ልጆች ቁጥር እንደ ባሕር አሸዋ ቢሆንም እንኳ የሚድኑት ቀሪዎች ብቻ ናቸው።+ 28  ይሖዋ* በምድር የሚኖሩትን ይፋረዳልና፤ ይህን ደግሞ ሳይዘገይ* ይፈጽመዋል።”+ 29  ደግሞም ኢሳይያስ አስቀድሞ እንደተናገረው “የሠራዊት ጌታ ይሖዋ* ዘር ባያስቀርልን ኖሮ እንደ ሰዶም በሆን፣ ገሞራንም በመሰልን ነበር።”+ 30  እንግዲህ ምን እንበል? አሕዛብ ጽድቅን ባይከታተሉም እንኳ ጽድቅን ይኸውም በእምነት አማካኝነት የሚገኘውን ጽድቅ አገኙ፤+ 31  ሆኖም እስራኤል የጽድቅን ሕግ ቢከታተልም ግቡ ላይ አልደረሰም፤ ይኸውም ሕጉን አልፈጸመም። 32  ይህ የሆነው ለምንድን ነው? በእምነት ሳይሆን በሥራ የሚገኝ እንደሆነ አድርገው ስለተከታተሉት ነው። ስለዚህ “በማሰናከያ ድንጋይ” ተሰናከሉ፤+ 33  ይህም “እነሆ፣ በጽዮን የሚያደናቅፍ ድንጋይና የሚያሰናክል ዓለት አኖራለሁ፤+ በእሱ ላይ እምነት የሚጥል ግን አያፍርም”+ ተብሎ እንደተጻፈው ነው።

የግርጌ ማስታወሻ

ቃል በቃል “በተመኘ ወይም በሮጠ።”
ወይም “በሰዎች ላይ ለምን ስህተት ይፈላልጋል?”
ከተጨማሪው መረጃ ላይ ሀ5ን ተመልከት።
ወይም “በፍጥነት።”
ከተጨማሪው መረጃ ላይ ሀ5ን ተመልከት።