ለቲቶ የተጻፈ ደብዳቤ 2:1-15

  • ለወጣቶችና ለአረጋውያን የተሰጠ ትክክለኛ ትምህርት (1-15)

    • ፈሪሃ አምላክ ከጎደለው አኗኗር መራቅ (12)

    • ለመልካም ሥራ መቅናት (14)

2  አንተ ግን ምንጊዜም ከትክክለኛ* ትምህርት ጋር የሚስማማ ነገር ተናገር።+  አረጋውያን ወንዶች በልማዶቻቸው ረገድ ልከኞች፣ ቁም ነገረኞች፣ ጤናማ አስተሳሰብ ያላቸው እንዲሁም በእምነት፣ በፍቅርና በጽናት ጤናሞች ይሁኑ።  በተመሳሳይም አረጋውያን ሴቶች ለቅዱሳን ሰዎች የሚገባ ባሕርይ ያላቸው፣ ስም የማያጠፉ፣ ለብዙ ወይን ጠጅ የማይገዙ እንዲሁም ጥሩ የሆነውን ነገር የሚያስተምሩ ይሁኑ፤  ይህም ወጣት ሴቶችን በመምከር* ባሎቻቸውን የሚወዱ፣ ልጆቻቸውን የሚወዱ፣  ጤናማ አስተሳሰብ ያላቸው፣ ንጹሐን፣ በቤት ውስጥ የሚሠሩ፣* ጥሩዎችና ለባሎቻቸው የሚገዙ+ እንዲሆኑ ለማድረግ ያስችላቸዋል፤ ይህም የአምላክ ቃል እንዳይሰደብ ነው።  በተመሳሳይም ወጣት ወንዶች ጤናማ አስተሳሰብ እንዲኖራቸው አሳስባቸው፤+  በማንኛውም ሁኔታ መልካም ሥራ በመሥራት አርዓያ መሆንህን አሳይ። ንጹሕ የሆነውን ነገር* በቁም ነገር አስተምር፤+  ደግሞም ሊነቀፍ የማይችል ጤናማ* አነጋገር በመጠቀም አስተምር፤+ ይኸውም ተቃዋሚዎች ስለ እኛ የሚናገሩት መጥፎ ነገር አጥተው እንዲያፍሩ ነው።+  ባሪያዎች ጌቶቻቸውን ለማስደሰት ጥረት በማድረግ በሁሉም ነገር ይገዙላቸው፤+ የአጸፋ ቃልም አይመልሱላቸው፤ 10  ደግሞም ሊሰርቋቸው አይገባም፤+ ከዚህ ይልቅ አዳኛችን የሆነው አምላክ ትምህርት በሁሉም መንገድ ውበት እንዲጎናጸፍ ያደርጉ ዘንድ ሙሉ በሙሉ እምነት የሚጣልባቸው ይሁኑ።+ 11  የአምላክ ጸጋ ተገልጧልና፤ ጸጋው ለሁሉም ዓይነት ሰዎች መዳን ያስገኛል።+ 12  ይህም ጸጋ ፈሪሃ አምላክ በጎደለው መንገድ መኖርና ዓለማዊ ምኞቶችን+ መከተል ትተን አሁን ባለው በዚህ ሥርዓት* ውስጥ ጤናማ አስተሳሰብ በመያዝ፣ በጽድቅና ለአምላክ በማደር እንድንኖር ያሠለጥነናል፤+ 13  በዚህ ሁኔታ አስደሳች የሆነውን ተስፋ+ እንዲሁም የታላቁን አምላክና የአዳኛችንን የኢየሱስ ክርስቶስን በክብር መገለጥ እንጠባበቃለን፤ 14  ክርስቶስ ከማንኛውም ዓይነት የዓመፅ ሕይወት እኛን ነፃ ለማውጣትና*+ ለመልካም ሥራ የሚቀና+ ልዩ ንብረቱ የሆነ ሕዝብ ለራሱ ለማንጻት ሕይወቱን ለእኛ ሰጥቷል።+ 15  እነዚህን ነገሮች፣ በሙሉ ሥልጣን መናገርህን፣ አጥብቀህ መምከርህንና* መውቀስህን ቀጥል።+ ማንም ሰው ፈጽሞ አይናቅህ።

የግርጌ ማስታወሻ

ወይም “ከጤናማ፤ ጠቃሚ ከሆነ።”
ወይም “ወደ ልቦናቸው እንዲመለሱ በመርዳት፤ በማሠልጠን።”
ወይም “ቤታቸውን የሚንከባከቡ።”
“በንጽሕና” ማለትም ሊሆን ይችላል።
ወይም “የሚያንጽ።”
ወይም “በዚህ ዘመን።” የቃላት መፍቻውን ተመልከት።
ቃል በቃል “ለመቤዠትና፤ ለመዋጀትና።”
ወይም “ማበረታታትህንና።”