ነህምያ 13:1-31

  • ነህምያ ያካሄደው ተጨማሪ ተሃድሶ (1-31)

    • አንድ አሥረኛውን አስገቡ (10-13)

    • ሰንበትን አታርክሱ (15-22)

    • ባዕዳን ሴቶችን በማግባታቸው ተወገዙ (23-28)

13  በዚያን ቀን ሕዝቡ እየሰማ የሙሴ መጽሐፍ ይነበብ ነበር፤+ በዚህ ጊዜ አሞናዊ ወይም ሞዓባዊ+ የሆነ ማንኛውም ሰው ወደ እውነተኛው አምላክ ጉባኤ ፈጽሞ መግባት እንደሌለበት የሚገልጽ ሐሳብ ተጽፎ ተገኘ፤+  ይህም የሆነው ለእስራኤላውያን ምግብና ውኃ በመስጠት ፋንታ እነሱን እንዲረግምላቸው በለዓምን ቀጥረው ስለነበር ነው።+ ይሁንና አምላካችን እርግማኑን ወደ በረከት ለወጠው።+  እነሱም ይህን ሕግ እንደሰሙ የባዕድ አገር ሰዎችን ሁሉ* ከእስራኤላውያን መለየት ጀመሩ።+  ይህ ከመሆኑ ቀደም ብሎ የአምላካችን ቤት* ግምጃ ቤቶች*+ ኃላፊ፣ የጦብያ+ ዘመድ የሆነው ካህኑ ኤልያሺብ+ ነበር።  እሱም ቀደም ሲል የእህል መባውን፣ ነጩን ዕጣን፣ ዕቃዎቹን እንዲሁም ለሌዋውያኑ፣+ ለዘማሪዎቹና ለበር ጠባቂዎቹ እንዲሰጥ የታዘዘውን የእህሉን፣ የአዲሱን የወይን ጠጅና የዘይቱን+ አንድ አሥረኛ* እንዲሁም ለካህናቱ የሚዋጣውን መዋጮ+ ያስቀምጡበት የነበረውን ቦታ ትልቅ ግምጃ ቤት* አድርጎ አዘጋጀለት።  ይህ ሁሉ ሲሆን እኔ በኢየሩሳሌም አልነበርኩም፤ ምክንያቱም የባቢሎን ንጉሥ አርጤክስስ+ በነገሠ በ32ኛው ዓመት+ ወደ ንጉሡ ሄጄ ነበር፤ ከተወሰነ ጊዜ በኋላም ንጉሡን ፈቃድ እንዲሰጠኝ ጠየቅኩ።  ከዚያም ወደ ኢየሩሳሌም ስመጣ ኤልያሺብ+ በእውነተኛው አምላክ ቤት ግቢ ውስጥ ለጦብያ+ ግምጃ ቤት በማዘጋጀት የፈጸመውን መጥፎ ድርጊት አስተዋልኩ።  እኔም በዚህ በጣም አዘንኩ፤ በመሆኑም የጦብያን የቤት ዕቃዎች በሙሉ ከግምጃ ቤቱ* አውጥቼ ወረወርኳቸው።  ከዚያም ትእዛዝ ሰጠሁ፤ እነሱም ግምጃ ቤቶቹን አጸዱ፤* እኔም የእውነተኛውን አምላክ ቤት+ ዕቃዎች ከእህሉ መባና ከነጩ ዕጣን+ ጋር እዚያው መልሼ አስቀመጥኩ። 10  በተጨማሪም ሌዋውያኑ የሚገባቸው ድርሻ+ ስለማይሰጣቸው+ ሥራውን ያከናውኑ የነበሩት ሌዋውያንም ሆኑ ዘማሪዎች እያንዳንዳቸው ወደየእርሻቸው መሄዳቸውን ተረዳሁ።+ 11  እኔም የበታች ገዢዎቹን+ “ለመሆኑ የእውነተኛው አምላክ ቤት እንዲህ ቸል የተባለው ለምንድን ነው?” በማለት ገሠጽኳቸው።+ ከዚያም ሁሉንም አንድ ላይ ከሰበሰብኳቸው በኋላ ወደየሥራ ምድባቸው እንዲመለሱ አደረግኩ። 12  የይሁዳ ሰዎችም ሁሉ የእህሉን፣ የአዲሱን የወይን ጠጅና የዘይቱን አንድ አሥረኛ+ ወደ ግምጃ ቤቶቹ አስገቡ።+ 13  ከዚያም ካህኑን ሸሌምያህን፣ የቅዱሳን መጻሕፍት ገልባጭ* የሆነውን ሳዶቅን እንዲሁም ከሌዋውያን መካከል ፐዳያህን በግምጃ ቤቶቹ ላይ ኃላፊዎች አደረግኳቸው፤ የማታንያህ ልጅ፣ የዛኩር ልጅ ሃናን ደግሞ የእነሱ ረዳት ነበር፤ እነዚህ ሰዎች እምነት የሚጣልባቸው ነበሩ። ለወንድሞቻቸው የማከፋፈሉ ኃላፊነት የእነሱ ነበር። 14  አምላኬ ሆይ፣ ስለዚህ ነገር አስበኝ፤+ ለአምላኬ ቤትና በዚያ ለሚከናወነው አገልግሎት* ስል የፈጸምኩትን ታማኝ ፍቅር የተንጸባረቀበት ተግባር አትርሳ።+ 15  በእነዚያ ቀናት በይሁዳ በሰንበት ቀን በመጭመቂያ ውስጥ ወይን የሚረግጡና+ እህል አምጥተው በአህያ ላይ የሚጭኑ እንዲሁም የወይን ጠጅ፣ የወይን ዘለላ፣ በለስና የተለያዩ ነገሮችን ጭነው በሰንበት ቀን ወደ ኢየሩሳሌም የሚያመጡ ሰዎችን አየሁ።+ በመሆኑም በዚያን ቀን ሸቀጣ ሸቀጦችን እንዳይሸጡ አስጠነቀቅኳቸው።* 16  በከተማዋ የሚኖሩ የጢሮስ ሰዎችም ዓሣና የተለያዩ ሸቀጣ ሸቀጦችን እያመጡ በኢየሩሳሌም ለሚኖሩ የይሁዳ ሰዎች በሰንበት ቀን ይሸጡ ነበር።+ 17  ስለሆነም በይሁዳ ያሉትን የተከበሩ ሰዎች እንዲህ በማለት ገሠጽኳቸው፦ “ሰንበትን በማርከስ የምትፈጽሙት ይህ መጥፎ ድርጊት ምንድን ነው? 18  አምላካችን በእኛም ሆነ በዚህች ከተማ ላይ ይህን ሁሉ መከራ ያመጣው አባቶቻችሁ እንዲህ ዓይነት ድርጊት በመፈጸማቸው አይደለም? አሁንም እናንተ ሰንበትን በማርከስ በእስራኤል ላይ የሚነደውን ቁጣ እያባባሳችሁ ነው።”+ 19  በመሆኑም በሰንበት ዋዜማ የምሽቱ ጥላ በኢየሩሳሌም በሮች ላይ ማረፍ ሲጀምር በሮቹ እንዲዘጉ ትእዛዝ ሰጠሁ። ሰንበት እስኪያልፍም ድረስ እንዳይከፍቷቸው ነገርኳቸው፤ በሰንበት ቀን ምንም ዓይነት ጭነት እንዳይገባም ከአገልጋዮቼ የተወሰኑትን በበሮቹ ላይ አቆምኩ። 20  ስለዚህ የተለያዩ ሸቀጣ ሸቀጦችን የሚነግዱትና የሚሸጡት ሰዎች ከአንዴም ሁለቴ ከኢየሩሳሌም ውጭ አደሩ። 21  ከዚያም እኔ “ቅጥሩ አጠገብ የምታድሩት ለምንድን ነው? ዳግመኛ እንዲህ የምታደርጉ ከሆነ የኃይል እርምጃ እወስድባችኋለሁ” በማለት አስጠነቀቅኳቸው። ከዚያን ጊዜ ወዲህ በሰንበት መጥተው አያውቁም። 22  ለሌዋውያኑም የሰንበት ቀን ምንጊዜም የተቀደሰ እንዲሆን ዘወትር ራሳቸውን እንዲያነጹና መጥተው በሮቹን እንዲጠብቁ ነገርኳቸው።+ አምላኬ ሆይ፣ ይህንም አስብልኝ፤ ማለቂያ ከሌለው ታማኝ ፍቅርህም የተነሳ እዘንልኝ።+ 23  በተጨማሪም በእነዚያ ቀናት አሽዶዳውያን፣+ አሞናውያንና ሞዓባውያን+ ሴቶችን ያገቡ* አይሁዳውያን መኖራቸውን አወቅኩ።+ 24  ከልጆቻቸው መካከል ግማሾቹ የአሽዶድን ቋንቋ ግማሾቹ ደግሞ ከተለያየ አገር የመጡትን ሰዎች ቋንቋ ይናገሩ የነበረ ቢሆንም ማንኛቸውም የአይሁዳውያንን ቋንቋ መናገር አይችሉም ነበር። 25  ስለሆነም ገሠጽኳቸው፤ እርግማንም አወረድኩባቸው፤ አንዳንዶቹንም መታኋቸው፤+ ፀጉራቸውንም ነጨሁ፤ እንዲሁም እንደሚከተለው በማለት በአምላክ አስማልኳቸው፦ “ሴቶች ልጆቻችሁን ለወንዶች ልጆቻቸው መስጠት የለባችሁም፤ ሴቶች ልጆቻቸውንም ለወንዶች ልጆቻችሁም ሆነ ለራሳችሁ መውሰድ የለባችሁም።+ 26  የእስራኤል ንጉሥ ሰለሞን ኃጢአት የሠራው በእነሱ ምክንያት አይደለም? በብዙ ብሔራት መካከል እንደ እሱ ያለ ንጉሥ አልነበረም፤+ ደግሞም በአምላኩ ዘንድ የተወደደ+ ስለነበር አምላክ በመላው እስራኤል ላይ ንጉሥ አደረገው። ይሁንና ባዕዳን ሚስቶች እሱን እንኳ ኃጢአት እንዲሠራ አደረጉት።+ 27  እናንተም ባዕዳን ሴቶችን በማግባት በአምላካችን ላይ ታማኝነት የጎደለው ተግባር ፈጸማችሁ፤ ታዲያ እንዲህ ያለውን ተሰምቶ የማያውቅ እጅግ መጥፎ ድርጊት እንዴት ትፈጽማላችሁ?”+ 28  ከሊቀ ካህናቱ ከኤልያሺብ+ ልጅ ከዮያዳ+ ወንዶች ልጆች መካከል አንዱ የሆሮናዊው የሳንባላጥ+ አማች ሆኖ ነበር። በመሆኑም ከአጠገቤ አባረርኩት። 29  አምላኬ ሆይ፣ ክህነቱን+ እንዲሁም ከካህናቱና ከሌዋውያኑ+ ጋር የተገባውን ቃል ኪዳን ስላረከሱ አትርሳቸው። 30  እኔም ርኩስ ከሆነ ከማንኛውም ባዕድ ነገር አነጻኋቸው፤ ለካህናቱና ለሌዋውያኑም ለእያንዳንዳቸው በየምድባቸው መሠረት ሥራ ሰጠኋቸው፤+ 31  እንዲሁም በተወሰነው ጊዜ መቅረብ ያለበትን እንጨትና+ መጀመሪያ የሚደርሰውን ፍሬ በተመለከተ ዝግጅት አደረግኩ። አምላኬ ሆይ፣ በመልካም አስበኝ።+

የግርጌ ማስታወሻ

ወይም “ድብልቅ ዘሮችን ሁሉ።”
ወይም “ቤተ መቅደስ።”
ወይም “መመገቢያ አዳራሾች።”
ወይም “መመገቢያ አዳራሽ።”
ወይም “አሥራት።”
ወይም “ከመመገቢያ አዳራሹ።”
ወይም “መመገቢያ አዳራሾቹን አጸዱ።”
ወይም “ጸሐፊ።”
ወይም “ቤቱን ለመጠበቅና ለመንከባከብ።”
“በመሆኑም ሸቀጣ ሸቀጦችን እንዳይሸጡ በዚያን ቀን አስጠነቀቅኳቸው” ማለትም ሊሆን ይችላል።
ወይም “ወደ ቤታቸው ያስገቡ።”