አሞጽ 7:1-17

  • የእስራኤል ጥፋት እንደቀረበ የሚያሳዩ ራእዮች (1-9)

    • አንበጦች (1-3)፣ እሳት (4-6)፣ ቱምቢ (7-9)

  • አሞጽ መተንበዩን እንዲያቆም ተነገረው (10-17)

7  ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ ይህን አሳየኝ፦ እነሆ በኋለኛው ወቅት የተዘራው እህል* መብቀል በጀመረበት ጊዜ እሱ የአንበጣ መንጋ ሰደደ። ይህም የንጉሡ ድርሻ የሆነው ሣር ታጭዶ ሲያበቃ በኋለኛው ወቅት የበቀለ እህል ነበር።  የአንበጣው መንጋ በምድሪቱ ላይ የበቀለውን ተክል ሁሉ በልቶ በጨረሰ ጊዜ እንዲህ አልኩ፦ “ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ ሆይ፣ እባክህ ይቅር በል!+ ያዕቆብ ይህን እንዴት ሊቋቋም ይችላል? እሱ አቅመ ቢስ ነውና!”+  በመሆኑም ይሖዋ ጉዳዩን በድጋሚ አጤነ።*+ ይሖዋም “ይህ አይፈጸምም” አለ።  ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ ይህን አሳየኝ፦ እነሆ ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ በእሳት እንደሚቀጣ ተናገረ። እሳቱም የተንጣለለውን ጥልቅ ውኃ በላ፤ ደግሞም የተወሰነውን የምድሪቱን ክፍል በላ።  በዚህ ጊዜ እንዲህ አልኩ፦ “ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ ሆይ፣ እባክህ ይህ ነገር እንዲደርስ አታድርግ።+ ያዕቆብ ይህን እንዴት ሊቋቋም ይችላል? እሱ አቅመ ቢስ ነውና!”+  በመሆኑም ይሖዋ ጉዳዩን በድጋሚ አጤነ።*+ ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋም “ይህም ቢሆን አይፈጸምም” አለ።  እሱም ይህን አሳየኝ፦ እነሆ ይሖዋ በቱምቢ በተሠራ ቅጥር ላይ ቆሞ ነበር፤ በእጁም ቱምቢ ይዞ ነበር።  ከዚያም ይሖዋ “አሞጽ፣ ምን ይታይሃል?” አለኝ። እኔም “ቱምቢ” አልኩ። ይሖዋም እንዲህ አለኝ፦ “እነሆ፣ በሕዝቤ በእስራኤል መካከል ቱምቢ እዘረጋለሁ። ከእንግዲህ ወዲህ ይቅርታ አላደርግላቸውም።+  የይስሐቅ ከፍ ያሉ የማምለኪያ ቦታዎች+ ይወድማሉ፤ የእስራኤልም መቅደሶች ይፈራርሳሉ፤+ ደግሞም በኢዮርብዓም* ቤት ላይ ሰይፍ ይዤ እመጣለሁ።”+ 10  የቤቴል ካህን የሆነው አሜስያስ+ ለእስራኤል ንጉሥ ለኢዮርብዓም+ ይህን መልእክት ላከ፦ “አሞጽ በእስራኤል ቤት መካከል በአንተ ላይ እያሴረ ነው።+ ምድሪቱ የእሱን ቃል ሁሉ መታገሥ አትችልም።+ 11  አሞጽ እንዲህ ይላልና፦ ‘ኢዮርብዓም በሰይፍ ይገደላል፤ እስራኤልም ያላንዳች ጥርጥር ከምድሩ ተፈናቅሎ በግዞት ይወሰዳል።’”+ 12  ከዚያም አሜስያስ አሞጽን እንዲህ አለው፦ “አንተ ባለ ራእይ፣ ሂድ፤ ወደ ይሁዳም ምድር ሽሽ፤ ቀለብህን ከዚያ አግኝ፤ በዚያም ትንቢት ተናገር።+ 13  ከእንግዲህ ወዲያ ግን በቤቴል ትንቢት አትናገር፤+ ቤቴል የንጉሥ መቅደስና+ የመንግሥት መኖሪያ ናትና።” 14  በዚህ ጊዜ አሞጽ ለአሜስያስ እንዲህ ሲል መለሰ፦ “እኔ ነቢይ ወይም የነቢይ ልጅ አይደለሁም፤ ከዚህ ይልቅ እረኛና+ የሾላ ዛፎች የምንከባከብ* ሰው ነኝ። 15  ይሖዋ ግን ከመንጋ ጠባቂነት ወሰደኝ፤ ይሖዋም ‘ሂድና ለሕዝቤ ለእስራኤል ትንቢት ተናገር’ አለኝ።+ 16  እንግዲህ የይሖዋን ቃል ስማ፦ ‘አንተ “በእስራኤል ላይ ትንቢት አትናገር፤+ በይስሐቅም ቤት ላይ አትስበክ”+ እያልክ ነው። 17  በመሆኑም ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ “ሚስትህ በከተማዋ ውስጥ ዝሙት አዳሪ ትሆናለች፤ ወንዶችና ሴቶች ልጆችህ ደግሞ በሰይፍ ይወድቃሉ። ምድርህም በገመድ እየተለካ ይከፋፈላል፤ አንተ ራስህም በረከሰ ምድር ትሞታለህ፤ እስራኤልም ያላንዳች ጥርጥር ከምድሩ ተፈናቅሎ በግዞት ይወሰዳል።”’”+

የግርጌ ማስታወሻ

በጥርና በየካቲት የሚዘራውን እህል ያመለክታል።
ወይም “በዚህ ተጸጸተ።”
ወይም “በዚህ ተጸጸተ።”
እዚህ ላይ የተጠቀሰው የዮአስ (የኢዮዓስ) ልጅ የሆነው ዳግማዊ ኢዮርብዓም ነው። አሞጽ 1:1ን ተመልከት።
ወይም “የሾላ ፍሬዎችን የምወጋ።”