ኢያሱ 7:1-26

  • እስራኤላውያን ጋይ ላይ ድል ተመቱ (1-5)

  • ኢያሱ ያቀረበው ጸሎት (6-9)

  • እስራኤላውያንን ለሽንፈት የዳረጋቸው ኃጢአት (10-15)

  • አካን ተጋለጠ፤ በድንጋይም ተወገረ (16-26)

7  ይሁን እንጂ ከይሁዳ ነገድ የሆነው የዛራ ልጅ፣ የዛብዲ ልጅ፣ የካርሚ ልጅ አካን+ ለጥፋት ከተለየው ነገር ላይ በመውሰዱ እስራኤላውያን ለጥፋት ከተለየው ነገር ጋር በተያያዘ ታማኝነት የጎደለው ድርጊት ፈጸሙ።+ በዚህም የተነሳ የይሖዋ ቁጣ በእስራኤላውያን ላይ ነደደ።+  ከዚያም ኢያሱ “ወጥታችሁ ምድሪቱን ሰልሉ” በማለት ከቤቴል+ በስተ ምሥራቅ በቤትአዌን አቅራቢያ ወደምትገኘው ወደ ጋይ+ ሰዎችን ላከ። በመሆኑም ሰዎቹ ወጥተው ጋይን ሰለሉ።  ሰዎቹም ወደ ኢያሱ ተመልሰው እንዲህ አሉት፦ “ሕዝቡ ሁሉ መውጣት አያስፈልገውም። ጋይን ድል ለማድረግ ሁለት ሺህ ወይም ሦስት ሺህ ገደማ የሚሆኑ ሰዎች ብቻ ይበቃሉ። ነዋሪዎቿ ጥቂት ስለሆኑ መላው ሕዝብ እንዲሄድ በማድረግ ሕዝቡን አታድክም።”  በመሆኑም 3,000 ገደማ የሚሆኑ ሰዎች ወደዚያ ወጡ፤ ይሁን እንጂ ከጋይ ሰዎች ፊት ለመሸሽ ተገደዱ።+  የጋይ ሰዎችም 36 ሰዎችን ገደሉ፤ ከከተማዋ በር አንስቶ እስከ ሸባሪም* ድረስ በማሳደድ ቁልቁለቱ ላይ መቷቸው። በዚህም የተነሳ የሕዝቡ ልብ ቀለጠ፤ እንደ ውኃም ፈሰሰ።  በዚህ ጊዜ ኢያሱ ልብሱን ቀደደ፤ እስከ ምሽትም ድረስ በይሖዋ ታቦት ፊት በግንባሩ መሬት ላይ ተደፋ፤ እሱም ሆነ የእስራኤል ሽማግሌዎች እንዲሁ አደረጉ፤ በራሳቸውም ላይ አቧራ ይበትኑ ነበር።  ኢያሱም እንዲህ አለ፦ “ወዮ! ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ፤ ይህን ሁሉ ሕዝብ ዮርዳኖስን አሻግረህ እዚህ ድረስ ያመጣኸው ለአሞራውያን አሳልፈህ በመስጠት እንድንጠፋ ለማድረግ ነው? እዚያው በዮርዳኖስ ማዶ* አርፈን ብንቀመጥ ይሻለን ነበር!  አቤቱ ይሖዋ ሆይ ይቅር በለኝ፣ እንግዲህ እስራኤል ከጠላቶቹ ፊት እንዲህ የሚሸሽ* ከሆነ ምን ማለት እችላለሁ?  ከነአናውያንና የምድሪቱ ነዋሪዎች በሙሉ ይህን ሲሰሙ መጥተው ይከቡንና ስማችንን ከምድር ገጽ ያጠፉታል፤ ታዲያ አንተ ለታላቁ ስምህ ስትል ምን ታደርግ ይሆን?”+ 10  ይሖዋም ለኢያሱ እንዲህ ሲል መለሰለት፦ “ተነስ! በግንባርህ የተደፋኸው ለምንድን ነው? 11  እስራኤላውያን ኃጢአት ሠርተዋል። እንዲጠብቁት ያዘዝኳቸውን ቃል ኪዳኔን አፍርሰዋል።+ ለጥፋት ከተለየው ነገር ላይም ሰርቀው+ ወስደዋል፤+ ከራሳቸው ዕቃዎችም ጋር በመቀላቀል ደብቀው አስቀምጠውታል።+ 12  ስለዚህ እስራኤላውያን ጠላቶቻቸውን መቋቋም አይችሉም። ዞረውም ከጠላቶቻቸው ፊት ይሸሻሉ፤ ምክንያቱም እነሱ ራሳቸው ለጥፋት የተለዩ ሆነዋል። ለጥፋት የተለየውን ነገር ከመካከላችሁ ካላስወገዳችሁ በስተቀር ከእንግዲህ እኔ ከእናንተ ጋር አልሆንም።+ 13  ተነስና ሕዝቡን ቀድስ!+ እንዲህም በላቸው፦ ‘ለነገ ራሳችሁን ቀድሱ፤ ምክንያቱም የእስራኤል አምላክ ይሖዋ እንዲህ ብሏል፦ “እስራኤል ሆይ፣ በመካከልህ ለጥፋት የተለየ ነገር አለ። ለጥፋት የተለየውን ነገር ከመካከልህ ካላስወገድክ ጠላቶችህን መቋቋም አትችልም። 14  ማለዳ ላይ በነገድ በነገድ ሆናችሁ ትቀርባላችሁ፤ ይሖዋ የሚመርጠውም ነገድ+ ወደ ፊት ይቀርባል፤ ከዚያም በወገን በወገኑ ሆኖ ይቀርባል፤ ይሖዋ የሚመርጠውም ወገን ወደ ፊት ይቀርባል፤ ከዚያም በቤተሰብ በቤተሰብ ሆኖ ይቀርባል፤ ይሖዋ የሚመርጠውም ቤተሰብ ወደ ፊት ይቀርባል፤ ከዚያም በግለሰብ በግለሰብ ሆኖ ይቀርባል። 15  ለጥፋት የተለየውን ነገር ወስዶ የተገኘውም ሰው በእሳት ይቃጠላል፤+ እሱም ሆነ የእሱ የሆነው ሁሉ ይቃጠላሉ፤ ምክንያቱም ይህ ሰው የይሖዋን ቃል ኪዳን አፍርሷል፤+ እንዲሁም በእስራኤል ውስጥ አሳፋሪ ተግባር ፈጽሟል።”’” 16  ስለሆነም ኢያሱ በሚቀጥለው ቀን በማለዳ ተነስቶ እስራኤላውያን በነገድ በነገድ ሆነው ወደ ፊት እንዲቀርቡ አደረገ፤ የይሁዳም ነገድ ተመረጠ። 17  የይሁዳ ወገኖች ወደ ፊት እንዲቀርቡ አደረገ፤ ከመካከላቸውም የዛራውያን+ ወገን ተመረጠ፤ ከዚያም ከዛራውያን ወገን የሆኑት ሰዎች በግለሰብ ደረጃ ወደ ፊት እንዲቀርቡ አደረገ፤ ከዚያም ዛብዲ ተመረጠ። 18  በመጨረሻም የዛብዲ ቤተሰብ በግለሰብ በግለሰብ ሆኖ ወደ ፊት እንዲቀርብ አደረገ፤ ከዚያም ከይሁዳ ነገድ የዛራ ልጅ፣ የዛብዲ ልጅ፣ የካርሚ ልጅ አካን ተመረጠ።+ 19  ኢያሱም አካንን እንዲህ አለው፦ “ልጄ ሆይ፣ እባክህ የእስራኤልን አምላክ ይሖዋን አክብር፤ ለእሱም ተናዘዝ። እባክህ ያደረግከውን ንገረኝ። አትደብቀኝ።” 20  አካንም ለኢያሱ እንዲህ ሲል መለሰለት፦ “በእርግጥም በእስራኤል አምላክ በይሖዋ ላይ ኃጢአት የሠራሁት እኔ ነኝ፤ እንግዲህ ያደረግኩት ይህ ነው፦ 21  ከምርኮው መካከል ከሰናኦር+ የመጣ የሚያምር የክብር ልብስ፣ 200 ሰቅል* ብርና 50 ሰቅል የሚመዝን ጥፍጥፍ ወርቅ አይቼ ስለተመኘሁ ወሰድኳቸው። አሁንም ገንዘቡ ከታች ሆኖ ድንኳኔ ውስጥ መሬት ውስጥ ተቀብረው ይገኛሉ።” 22  ኢያሱም ወዲያውኑ መልእክተኞች ላከ፤ እነሱም ወደ ድንኳኑ እየሮጡ ሄዱ፤ ልብሱንም ድንኳኑ ውስጥ ተደብቆ አገኙት፤ ገንዘቡም ከልብሱ ሥር ነበር። 23  ከዚያም ከድንኳኑ አውጥተው ወደ ኢያሱና ወደ እስራኤላውያን ሁሉ አመጧቸው፤ በይሖዋም ፊት አስቀመጧቸው። 24  በኋላም ኢያሱና ከእሱ ጋር የነበሩት እስራኤላውያን በሙሉ የዛራን ልጅ አካንን፣+ ብሩን፣ የክብር ልብሱን፣ ጥፍጥፍ ወርቁን፣+ ወንዶች ልጆቹን፣ ሴቶች ልጆቹን፣ በሬውን፣ አህያውን፣ መንጋውን፣ ድንኳኑንና የእሱ የሆነውን ሁሉ ወደ አኮር ሸለቆ*+ አመጡ። 25  ኢያሱም አካንን “መዓት* ያመጣህብን ለምንድን ነው?+ ይሖዋም በዛሬው ዕለት መዓት ያመጣብሃል” አለው። ከዚያም እስራኤላውያን በሙሉ በድንጋይ ወገሩት፤+ በእሳትም አቃጠሏቸው።+ በዚህ መንገድ ሁሉንም በድንጋይ ወግረው ገደሏቸው። 26  በእሱም ላይ እስከ ዛሬ ድረስ የሚታየውን የድንጋይ ቁልል ከመሩበት። በዚህ ጊዜ የይሖዋ ታላቅ ቁጣ በረደ።+ የዚያ ቦታ ስም እስከ ዛሬ ድረስ የአኮር* ሸለቆ የሚባለው በዚህ የተነሳ ነው።

የግርጌ ማስታወሻ

“የድንጋይ ካባ” የሚል ትርጉም አለው።
በስተ ምሥራቅ ያለውን ያመለክታል።
ወይም “ለጠላቶቹ ጀርባውን የሚሰጥ።”
አንድ ሰቅል 11.4 ግራም ነው። ከተጨማሪው መረጃ ላይ ለ14ን ተመልከት።
ወይም “ረባዳማ ሜዳ።”
ወይም “ችግር፤ መጠላት።”
“መዓት፤ መጠላት” የሚል ትርጉም አለው።