ኢዮብ 10:1-22

  • ኢዮብ መልስ መስጠቱን ቀጠለ (1-22)

    • ‘አምላክ ከእኔ ጋር የሚሟገተው ለምንድን ነው?’ (2)

    • ሟች የሆነው ኢዮብ ራሱን ከአምላክ ጋር አነጻጸረ (4-12)

    • ‘ትንሽ ፋታ ላግኝ’ (20)

10  “ሕይወቴን ተጸየፍኳት።*+ አንዳች ሳላስቀር ብሶቴን አሰማለሁ። በታላቅ ምሬት* እናገራለሁ!   አምላክን እንዲህ እለዋለሁ፦ ‘በደለኛ ነህ አትበለኝ። ከእኔ ጋር የምትሟገተው ለምን እንደሆነ ንገረኝ።   በክፉዎች ዕቅድ ደስ እየተሰኘህ፣የእጆችህን ሥራ መጨቆንህና መናቅህምን ይጠቅምሃል?+   ዓይንህ የሥጋ ለባሽ ዓይን ነው?ወይስ የምታየው ሟች የሆነ ሰው በሚያይበት መንገድ ነው?   ዘመንህ እንደ ሟች ሰዎች ዘመን ነው?ወይስ ዕድሜህ እንደ ሰው ዘመን ነው?+   ታዲያ በደልን የምትፈላልግብኝ፣ኃጢአቴንስ የምትከታተለው ለምንድን ነው?+   በደለኛ እንዳልሆንኩ ታውቃለህ፤+ደግሞም ማንም ከእጅህ ሊያስጥለኝ አይችልም።+   የገዛ እጆችህ ቀረጹኝ፤ ደግሞም ሠሩኝ፤+አሁን ግን ሙሉ በሙሉ ልታጠፋኝ ነው።   ከሸክላ እንደሠራኸኝ እባክህ አስታውስ፤+አሁን ግን ወደ አፈር ትመልሰኛለህ።+ 10  እንደ ወተት አላፈሰስከኝም?እንደ እርጎስ አላረጋኸኝም? 11  ቆዳና ሥጋ አለበስከኝ፤በአጥንትና በጅማት አያይዘህ ሠራኸኝ።+ 12  ሕይወት ሰጠኸኝ፤ ታማኝ ፍቅርም አሳየኸኝ፤መንፈሴን* በእንክብካቤ ጠበቅክ።+ 13  ሆኖም እነዚህን ነገሮች በስውር ለማድረግ አሰብክ።* እነዚህ ነገሮች ከአንተ እንደመጡ አውቃለሁ። 14  ኃጢአት ብሠራ ትመለከተኛለህ፤+ከበደሌም ነፃ አታደርገኝም። 15  በደለኛ ከሆንኩ ወዮልኝ! ንጹሕ ብሆንም እንኳ ራሴን ቀና ማድረግ አልችልም፤+ውርደትና ጉስቁልና በዝቶብኛልና።+ 16  ራሴን ቀና ባደርግ እንደ አንበሳ ታድነኛለህ፤+ዳግመኛም በእኔ ላይ ኃይልህን ታሳያለህ። 17  አዳዲስ ምሥክሮችን በእኔ ላይ ታቆማለህ፤ቁጣህንም በእኔ ላይ ታበዛለህ፤በመከራ ላይ መከራ ተደራርቦብኛል። 18  ታዲያ ከማህፀን ለምን አወጣኸኝ?+ ምነው የሰው ዓይን ሳያየኝ በሞትኩ ኖሮ! 19  እንዳልተፈጠርኩ በሆንኩ ነበር!በቀጥታ ከማህፀን ወደ መቃብር በተወሰድኩ ነበር!’ 20  የሕይወት ዘመኔ ጥቂት አይደለም?+ እስቲ ተወት ያድርገኝ፤ትንሽ ፋታ እንዳገኝ* ዓይኑን ከእኔ ላይ ያንሳ፤+ 21  ወደማልመለስበት ስፍራ፣+ወደ ድቅድቅ ጨለማ* ምድር በቅርቡ እሄዳለሁ፤+ 22  በጨለማ ወደተዋጠ፣ ፅልማሞት ወዳጠላበትናዝብርቅ ወደሰፈነበት፣ብርሃኑ እንኳ እንደ ጨለማ ወደሆነበት ምድር እሄዳለሁ።”

የግርጌ ማስታወሻ

ወይም “ነፍሴ ተጸየፈቻት።”
ወይም “በነፍሴ ምሬት።”
ወይም “እስትንፋሴን፤ ሕይወቴን።”
ቃል በቃል “ደግሞም እነዚህን ነገሮች በልብህ ውስጥ ሰወርክ።”
ወይም “ትንሽ እንድጽናና።”
ወይም “ጨለማና የሞት ጥላ ወዳለበት።”