ኢዮብ 8:1-22

  • የበልዳዶስ የመጀመሪያ ዙር ንግግር (1-22)

    • የኢዮብ ልጆች ኃጢአት ሠርተው ሊሆን እንደሚችል ጠቆመ (4)

    • ‘ንጹሕ ብትሆን ኖሮ አምላክ ይጠብቅህ ነበር’ (6)

    • ኢዮብ አምላክ የለሽ እንደሆነ ጠቆመ (13)

8  ከዚያም ሹሃዊው+ በልዳዶስ+ እንዲህ ሲል መለሰ፦   “እንዲህ የምትናገረው እስከ መቼ ነው?+ ከአፍህ የሚወጣው ቃል ብርቱ ነፋስ ነው!   አምላክ ፍትሕን ያዛባል?ወይስ ሁሉን ቻይ የሆነው አምላክ ጽድቅን ያጣምማል?   ልጆችህ በእሱ ላይ ኃጢአት ሠርተው ከሆነ፣ለፈጸሙት ዓመፅ እንዲቀጡ አድርጓል፤*   አንተ ግን ወደ አምላክ ዞር ብትል፣+ሁሉን ቻይ የሆነው አምላክ ሞገስ እንዲያሳይህ ብትማጸን፣   በእርግጥ ንጹሕና ቅን ብትሆን፣+እሱ ትኩረት ይሰጥሃል፤*ወደ ትክክለኛ ቦታህም ይመልስሃል።   ጅማሬህ አነስተኛ ቢሆንም፣የወደፊት ሕይወትህ ታላቅ ይሆናል።+   እስቲ የቀድሞውን ትውልድ ጠይቅ፤አባቶቻቸው ለተገነዘቧቸው ነገሮችም ትኩረት ስጥ።+   እኛ የተወለድነው ገና ትናንት ስለሆነ የምናውቀው ነገር የለም፤ምክንያቱም በምድር ላይ ዘመናችን እንደ ጥላ ነው። 10  እነሱ አያስተምሩህም?ደግሞስ የሚያውቁትን ነገር* አይነግሩህም? 11  ደንገል ረግረጋማ ባልሆነ ስፍራ ያድጋል? ሸምበቆስ ውኃ በሌለበት ቦታ ያድጋል? 12  ገና ሳያብብና ሳይቆረጥ፣ከሌላው ተክል ሁሉ በፊት ይደርቃል። 13  አምላክን የሚረሱ ሰዎች ሁሉ መጨረሻቸው እንደዚህ ነው፤*አምላክ የለሽ የሆነ* ሰው ተስፋ ይጨልማልና፤ 14  የሚመካበት ነገር ከንቱ ነው፤የሚታመንበትም ነገር ከሸረሪት ድር* የማይሻል ነው። 15  እሱ ቤቱን ይደገፈዋል፤ ሆኖም ቤቱ ጸንቶ አይቆምም፤አጥብቆ ሊይዘው ይሞክራል፤ ሆኖም አይጸናም። 16  እሱ በፀሐይ ብርሃን እንደሚያድግ እርጥበት ያለው ተክል ነው፤ቅርንጫፎቹም በአትክልት ስፍራው ውስጥ ይንሰራፋሉ።+ 17  ሥሩም በድንጋይ ክምር ውስጥ ይጠላለፋል፤በድንጋዮቹ መካከል ቤት ይፈልጋል።* 18  ሆኖም ከስፍራው በሚነቀልበት* ጊዜ፣ያ ስፍራ ‘ፈጽሞ አይቼህ አላውቅም’ ብሎ ይክደዋል።+ 19  አዎ፣ በዚህ ሁኔታ ይጠፋል፤*+ከዚያም ሌሎች ከአፈሩ ውስጥ ይበቅላሉ። 20  በእርግጥም አምላክ ንጹሕ አቋማቸውን* የሚጠብቁትን አይጥልም፤ክፉ ሰዎችንም አይረዳም፤* 21  በመጨረሻም አፍህን በሳቅ፣ከንፈሮችህንም በእልልታ ይሞላል። 22  የሚጠሉህ ኀፍረት ይከናነባሉ፤የክፉዎችም ድንኳን ይጠፋል።”

የግርጌ ማስታወሻ

ቃል በቃል “ወደ ዓመፃቸው እጅ ልኳቸዋል።”
ወይም “እሱ ስለ አንተ ይነሳል።”
ቃል በቃል “ከልባቸውም ቃል አውጥተው።”
ቃል በቃል “መንገዶቻቸው እንደዚህ ናቸው።”
ወይም “የከሃዲ።”
ቃል በቃል “ቤት።”
ወይም “የድንጋይ ቤት ይመለከታል።”
ወይም “በሚዋጥበት።”
ወይም “መንገዱ በዚህ ሁኔታ ያከትማል።”
ኢዮብ 2:9 ላይ የሚገኘውን የግርጌ ማስታወሻ ተመልከት።
ቃል በቃል “(የክፉ ሰዎችን) እጅ አይዝም።”