ኤርምያስ 29:1-32

  • ኤርምያስ በግዞት ወደ ባቢሎን ለተወሰዱት ሰዎች የጻፈው ደብዳቤ (1-23)

    • እስራኤላውያን ከ70 ዓመት በኋላ ይመለሳሉ (10)

  • ለሸማያህ የተላለፈ መልእክት (24-32)

29  ነቢዩ ኤርምያስ፣ በግዞት ከተወሰዱት ሰዎች መካከል በሕይወት ለቀሩት ሽማግሌዎች፣ ለካህናቱ፣ ለነቢያቱና ናቡከደነጾር ከኢየሩሳሌም ወደ ባቢሎን በግዞት ለወሰደው ሕዝብ ሁሉ ከኢየሩሳሌም የላከው ደብዳቤ ቃል ይህ ነው፦  ይህም የሆነው ንጉሥ ኢኮንያን፣+ የንጉሡ እናት፣*+ ባለሥልጣናቱ፣ የይሁዳና የኢየሩሳሌም መኳንንት፣ የእጅ ጥበብ ባለሙያዎቹና አንጥረኞቹ* ከኢየሩሳሌም ከሄዱ በኋላ ነው።+  ደብዳቤውን የላከው፣ የይሁዳ ንጉሥ ሴዴቅያስ+ ወደ ባቢሎን ይኸውም የባቢሎን ንጉሥ ወደሆነው ወደ ናቡከደነጾር በላካቸው በሳፋን+ ልጅ በኤልዓሳና በኬልቅያስ ልጅ በገማርያህ እጅ ነው። ደብዳቤውም እንዲህ የሚል ነበር፦  “የእስራኤል አምላክ፣ የሠራዊት ጌታ ይሖዋ ከኢየሩሳሌም ወደ ባቢሎን በግዞት እንዲወሰዱ ላደረጋቸው ለተማረኩት ሕዝብ ሁሉ እንዲህ ይላል፦  ‘ቤት ሠርታችሁ በዚያ ኑሩ። አትክልት ተክላችሁ ፍሬውን ብሉ።  ሚስት አግብታችሁ ወንዶችና ሴቶች ልጆች ውለዱ፤ እነሱም ወንዶችና ሴቶች ልጆች እንዲወልዱ፣ ወንዶች ልጆቻችሁንና ሴቶች ልጆቻችሁን ዳሩ። በዚያም ቁጥራችሁ ይብዛ እንጂ አይነስ።  በግዞት ተወስዳችሁ እንድትኖሩባት ላደረግኳት ከተማም ሰላምን ፈልጉ፤ ስለ እሷም ወደ ይሖዋ ጸልዩ፤ እሷ ሰላም ከሰፈነባት እናንተም በሰላም ትኖራላችሁና።+  የእስራኤል አምላክ፣ የሠራዊት ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላልና፦ “በመካከላችሁ ያሉት ነቢያትና ሟርተኞች አያታሏችሁ፤+ የሚያልሙትንም ሕልም አትስሙ።  ‘በስሜ የሚተነብዩላችሁ ሐሰት ነውና። እኔ አልላክኋቸውም’+ ይላል ይሖዋ።”’” 10  “ይሖዋ እንዲህ ይላልና፦ ‘በባቢሎን የምትኖሩበት 70 ዓመት ሲፈጸም ትኩረቴን ወደ እናንተ አዞራለሁ፤+ ወደዚህም ስፍራ መልሼ በማምጣት፣ የገባሁትን ቃል እፈጽማለሁ።’+ 11  “‘ለእናንተ የማስበውን ሐሳብ በሚገባ አውቀዋለሁና’ ይላል ይሖዋ፤ ‘ለእናንተ የማስበው ጥፋትን ሳይሆን ሰላምን+ እንዲሁም የተሻለ ሕይወትንና ተስፋን ነው።+ 12  እናንተም ትጠሩኛላችሁ፤ ወደ እኔም ቀርባችሁ ትጸልያላችሁ፤ እኔም እሰማችኋለሁ።’+ 13  “‘እኔን ትሻላችሁ፤ በሙሉ ልባችሁ ስለምትፈልጉኝ ታገኙኛላችሁ።+ 14  እኔም እገኝላችኋለሁ’+ ይላል ይሖዋ። ‘በምርኮ የተወሰዱትን ወገኖቻችሁን እሰበስባለሁ፤ እናንተን ከበተንኩባቸው ብሔራትና ቦታዎች ሁሉ እሰበስባችኋለሁ’+ ይላል ይሖዋ። ‘በግዞት እንድትወሰዱ ባደረግኩ ጊዜ ትታችሁት ወደሄዳችሁት ቦታ መልሼ አመጣችኋለሁ።’+ 15  “እናንተ ግን ‘ይሖዋ በባቢሎን ነቢያት አስነስቶልናል’ ብላችኋል። 16  “ይሖዋ በዳዊት ዙፋን ላይ ለተቀመጠው ንጉሥና+ በዚህች ከተማ ውስጥ ለሚኖረው ሕዝብ ሁሉ ይኸውም ከእናንተ ጋር በግዞት ላልተወሰዱት ወንድሞቻችሁ እንዲህ ይላልና፦ 17  ‘የሠራዊት ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ “እነሆ፣ በእነሱ ላይ ሰይፍን፣ ረሃብንና ቸነፈርን* እሰዳለሁ፤+ በጣም መጥፎ ከመሆናቸው የተነሳ ሊበሉ እንደማይችሉ የበሰበሱ* በለሶች አደርጋቸዋለሁ።”’+ 18  “‘በሰይፍ፣+ በረሃብና በቸነፈር አሳድዳቸዋለሁ፤ በምድር ላይ ላሉ መንግሥታትም ሁሉ መቀጣጫ አደርጋቸዋለሁ፤+ እነሱን በምበትንባቸው ብሔራት ሁሉ መካከልም ለእርግማን አሳልፌ እሰጣቸዋለሁ፤ ደግሞም መደነቂያ፣ ማፏጫና+ መሳለቂያ አደርጋቸዋለሁ፤+ 19  ምክንያቱም ደግሜ ደጋግሜ* በላክኋቸው አገልጋዮቼ ይኸውም በነቢያት አማካኝነት ያስተላለፍኩትን ቃል አልሰሙም’+ ይላል ይሖዋ። “‘ይሁንና እናንተም አልሰማችሁም’+ ይላል ይሖዋ። 20  “ስለዚህ ከኢየሩሳሌም ወደ ባቢሎን የሰደድኳችሁ እናንተ ግዞተኞች ሁሉ የይሖዋን ቃል ስሙ። 21  የእስራኤል አምላክ፣ የሠራዊት ጌታ ይሖዋ በስሜ የሐሰት ትንቢት ስለሚተነብዩላችሁ+ ስለ ቆላያህ ልጅ ስለ አክዓብና ስለ ማአሴያህ ልጅ ስለ ሴዴቅያስ እንዲህ ይላል፦ ‘እነሆ፣ በባቢሎን ንጉሥ በናቡከደነጾር* እጅ አሳልፌ እሰጣቸዋለሁ፤ እሱም በፊታችሁ ይገድላቸዋል። 22  በእነሱ ላይ የሚደርሰውንም ነገር በባቢሎን ያሉ የይሁዳ ግዞተኞች ሁሉ እንደ እርግማን ይጠቀሙበታል፤ “ይሖዋ፣ የባቢሎን ንጉሥ በእሳት እንደጠበሳቸው እንደ ሴዴቅያስና እንደ አክዓብ ያድርግህ!” ይላሉ፤ 23  ከባልንጀሮቻቸው ሚስቶች ጋር በማመንዘርና እኔ ያላዘዝኳቸውን ቃል በስሜ በሐሰት በመናገር+ በእስራኤል የሚያሳፍር ድርጊት ፈጽመዋልና።+ “‘“እኔ ይህን አውቃለሁ፤ ለዚህም ነገር ምሥክር ነኝ”+ ይላል ይሖዋ።’” 24  “ኔሄላማዊውን ሸማያህን+ እንዲህ ትለዋለህ፦ 25  ‘የእስራኤል አምላክ፣ የሠራዊት ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ “በኢየሩሳሌም ላሉት ሰዎች ሁሉና ለማአሴያህ ልጅ ለካህኑ ሶፎንያስ+ እንዲሁም ለካህናቱ ሁሉ፣ በገዛ ስምህ እንዲህ ብለህ ደብዳቤዎችን ልከሃልና፦ 26  ‘በይሖዋ ቤት የበላይ ተመልካች እንድትሆን፣ እንደ ነቢይ የሚያደርገውን ማንኛውንም ያበደ ሰው እንድትይዝ እንዲሁም በእግር ግንድ ብሎም በአንገትና በእጅ መጠረቂያ* እንድታስር ይሖዋ በካህኑ በዮዳሄ ምትክ ካህን አድርጎሃል፤+ 27  ታዲያ ነቢይ ነኝ የሚላችሁን የአናቶቱን+ ኤርምያስን ለምን አልገሠጽከውም?+ 28  በባቢሎን ላለነው ሰዎችም እንኳ ሳይቀር እንዲህ የሚል መልእክት ልኮብናል፦ “በግዞት የምትቆዩበት ጊዜ ረጅም ነው! ቤት ሠርታችሁ በዚያ ኑሩ። አትክልት ተክላችሁ ፍሬውን ብሉ፤+ . . .”’”’” 29  ካህኑ ሶፎንያስ+ ይህን ደብዳቤ ነቢዩ ኤርምያስ እየሰማ ባነበበ ጊዜ 30  የይሖዋ ቃል እንዲህ ሲል ወደ ኤርምያስ መጣ፦ 31  “በግዞት ወዳሉት ሁሉ እንዲህ የሚል መልእክት ላክ፦ ‘ይሖዋ ስለ ኔሄላማዊው ሸማያህ እንዲህ ይላል፦ “ሸማያህ እኔ ሳልከው ስለተነበየላችሁና በሐሰት እንድትታመኑ ለማድረግ ስለሞከረ፣+ 32  ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ ‘እነሆ፣ ትኩረቴን በኔሄላማዊው ሸማያህና በዘሮቹ ላይ አደርጋለሁ።’ በዚህ ሕዝብ መካከል የእሱ ዘር የሆነ አንድም ሰው አይተርፍም፤ ለሕዝቤ የማደርገውንም መልካም ነገር አያይም’ ይላል ይሖዋ፤ ‘በይሖዋ ላይ ዓመፅ አነሳስቷልና።’”’”

የግርጌ ማስታወሻ

“ምሽግ የሚገነቡት ሰዎች” ማለትም ሊሆን ይችላል።
ወይም “እመቤቲቱ።”
“የፈረጡ” ማለትም ሊሆን ይችላል።
ወይም “በሽታን።”
ቃል በቃል “በማለዳ እየተነሳሁ።”
ቃል በቃል “በናቡከደረጾር።” ናቡከደነጾር የሚለው ስም የሚጻፍበት ሌላው መንገድ ነው።
ወይም “በአንገት ማሠሪያ ሰንሰለት።”