ዘሌዋውያን 22:1-33

  • የካህናቱ የመንጻት ሥርዓትና ቅዱስ ከሆኑት ነገሮች መብላት (1-16)

  • ተቀባይነት የሚያገኙት እንከን የሌለባቸው መባዎች ብቻ ናቸው (17-33)

22  በተጨማሪም ይሖዋ ሙሴን እንዲህ አለው፦  “ለአሮንና ለወንዶች ልጆቹ፣ እስራኤላውያን የሚያመጧቸውን ቅዱስ ነገሮች የሚይዙበትን መንገድ በተመለከተ ጥንቃቄ እንዲያደርጉና* ለእኔ የተቀደሱ አድርገው በለዩአቸው ነገሮች+ ቅዱስ ስሜን እንዳያረክሱ+ ንገራቸው። እኔ ይሖዋ ነኝ።  እንዲህ በላቸው፦ ‘በትውልዶቻችሁ ሁሉ ከልጆቻችሁ መካከል ረክሶ እያለ እስራኤላውያን ለይሖዋ የተቀደሱ አድርገው ወደለዩአቸው ቅዱስ ነገሮች የሚቀርብ ሰው ካለ ያ ሰው* ከፊቴ እንዲጠፋ ይደረግ።+ እኔ ይሖዋ ነኝ።  ከአሮን ልጆች መካከል የሥጋ ደዌ+ ያለበት ወይም ፈሳሽ የሚወጣው+ ማንኛውም ሰው ንጹሕ እስኪሆን ድረስ+ ቅዱስ ከሆኑት ነገሮች መብላት የለበትም፤ የሞተን ሰው* በመንካት የረከሰን ሰው+ የነካ ወይም ከሰውነቱ የዘር ፈሳሽ የሚወጣው+  አሊያም ርኩስ የሆነን የሚርመሰመስ ፍጡር የነካ+ ወይም ደግሞ ሊያረክሰው በሚችል በማንኛውም ዓይነት ነገር የረከሰን ሰው የነካ+ ሰው ከእነዚህ ነገሮች አይብላ።  እንደነዚህ ያሉ ነገሮችን የነካ ማንኛውም ሰው* እስከ ማታ ድረስ ርኩስ ይሆናል፤ ገላውንም በውኃ እስካልታጠበ+ ድረስ ቅዱስ ከሆኑት ነገሮች መብላት አይችልም።  ፀሐይ በምትጠልቅበት ጊዜ ንጹሕ ይሆናል፤ ከዚያ በኋላ ቅዱስ ከሆኑት ነገሮች መብላት ይችላል፤ ምክንያቱም ይህ ምግቡ ነው።+  በተጨማሪም እንዳይረክስ ሞቶ የተገኘን ወይም አውሬ የቦጫጨቀውን የማንኛውንም እንስሳ ሥጋ መብላት የለበትም።+ እኔ ይሖዋ ነኝ።  “‘ለእኔ የገቡትን ግዴታ ባለመጠበቅ በራሳቸው ላይ ኃጢአት እንዳያመጡና በዚህም የተነሳ ቅዱስ የሆነውን ነገር በማርከስ እንዳይሞቱ የገቡትን ግዴታ መጠበቅ አለባቸው። የምቀድሳቸው እኔ ይሖዋ ነኝ። 10  “‘ያልተፈቀደለት ማንኛውም ሰው* ቅዱስ የሆነውን የትኛውንም ነገር መብላት የለበትም።+ ካህኑ ቤት በእንግድነት ያረፈ ሰው ወይም ቅጥር ሠራተኛ ቅዱስ ከሆነው ነገር መብላት የለበትም። 11  ሆኖም አንድ ካህን በገዛ ገንዘቡ አንድ ሰው* ቢገዛ ያ ሰው ከምግቡ መካፈል ይችላል። በቤቱ የተወለዱ ባሪያዎችም ከእሱ ምግብ መካፈል ይችላሉ።+ 12  የአንድ ካህን ሴት ልጅ፣ ካህን ያልሆነን ሰው ብታገባ* በመዋጮ ከተሰጡት ቅዱስ የሆኑ ነገሮች መብላት አትችልም። 13  ይሁንና የአንድ ካህን ሴት ልጅ፣ ባሏ ቢሞት ወይም ብትፋታና ልጅ ባይኖራት እንደ ወጣትነቷም ጊዜ ወደ አባቷ ቤት ብትመለስ ከአባቷ ምግብ መብላት ትችላለች፤+ ያልተፈቀደለት ማንኛውም ሰው* ግን ከዚያ መብላት የለበትም። 14  “‘አንድ ሰው ቅዱስ ከሆነው ነገር ባለማወቅ ቢበላ የቅዱሱን ነገር ዋጋ አንድ አምስተኛ በመጨመር ቅዱስ የሆነውን መባ ለካህኑ ይስጥ።+ 15  ካህናቱ፣ እስራኤላውያን ለይሖዋ መዋጮ አድርገው የሰጧቸውን ቅዱስ ነገሮች ማርከስ+ 16  እንዲሁም ሕዝቡ ያመጣቸውን ቅዱስ ነገሮች እንዲበላና ቅጣት የሚያስከትል በደል እንዲፈጽም ማድረግ የለባቸውም፤ ምክንያቱም የምቀድሳቸው እኔ ይሖዋ ነኝ።’” 17  ይሖዋም ሙሴን እንዲህ አለው፦ 18  “ለአሮን፣ ለወንዶች ልጆቹና ለእስራኤላውያን በሙሉ እንዲህ ብለህ ንገራቸው፦ ‘ስእለቱን ለመፈጸም ወይም የፈቃደኝነት መባ ለማቅረብ+ ሲል የሚቃጠል መባውን ለይሖዋ የሚያቀርብ አንድ እስራኤላዊ ወይም በእስራኤል ውስጥ የሚኖር አንድ የባዕድ አገር ሰው+ 19  ተቀባይነት እንዲያገኝ ከፈለገ መሥዋዕቱ ከመንጋው፣ ከጠቦቶቹ ወይም ከፍየሎቹ መካከል የተወሰደ እንከን የሌለበት ተባዕት+ መሆን ይኖርበታል። 20  ተቀባይነት ስለማያስገኝላችሁ እንከን ያለበትን ማንኛውንም ነገር አታቅርቡ።+ 21  “‘አንድ ሰው ስእለቱን ለመፈጸም ወይም የፈቃደኝነት መባ ለመስጠት ሲል ለይሖዋ የኅብረት መሥዋዕት+ ቢያቀርብ መሥዋዕቱ ተቀባይነት እንዲያገኝ ከከብቶቹ ወይም ከመንጋው መካከል እንከን የሌለበትን ማቅረብ ይኖርበታል። ምንም ዓይነት እንከን ሊኖርበት አይገባም። 22  መባ ሆኖ የሚቀርበው እንስሳ ዕውር ወይም ሰባራ አሊያም ቆራጣ ወይም ደግሞ ኪንታሮት አሊያም እከክ ወይም ጭርት ያለበት መሆን የለበትም፤ እንዲህ ያለውን እንስሳ ለይሖዋ ማቅረብ የለባችሁም ወይም እንዲህ ያለውን መባ ለይሖዋ በመሠዊያው ላይ ማቅረብ የለባችሁም። 23  አንዱ እግሩ የረዘመን ወይም ያጠረን በሬ ወይም በግ የፈቃደኝነት መባ አድርጋችሁ ማቅረብ ትችላላችሁ፤ የስእለት መባ አድርጋችሁ ብታቀርቡት ግን ተቀባይነት አይኖረውም። 24  የዘር ፍሬው ጉዳት የደረሰበትን ወይም የተቀጠቀጠን አሊያም ተሰንጥቆ የወጣን ወይም የተቆረጠን እንስሳ ለይሖዋ ማቅረብ የለባችሁም፤ በምድራችሁ እነዚህን የመሰሉ እንስሳትን ማቅረብ አይኖርባችሁም። 25  እነዚህ ጉድለትና እንከን ስላለባቸው ከመካከላቸው የትኛውንም ከባዕድ ሰው እጅ በመቀበል የአምላካችሁ ምግብ አድርጋችሁ ማቅረብ የለባችሁም። ተቀባይነት አያገኙላችሁም።’” 26  በተጨማሪም ይሖዋ ሙሴን እንዲህ አለው፦ 27  “ጥጃ ወይም የበግ ግልገል አሊያም የፍየል ግልገል በሚወለድበት ጊዜ ለሰባት ቀን ከእናቱ ጋር ይቆይ፤+ ከስምንተኛው ቀን አንስቶ ግን መባ ይኸውም ለይሖዋ በእሳት የሚቀርብ መባ ሆኖ ቢቀርብ ተቀባይነት ይኖረዋል። 28  ላምን ከጥጃዋ ወይም በግን ከግልገሏ ጋር በአንድ ቀን አትረዱ።+ 29  “ለይሖዋ የምሥጋና መሥዋዕት+ የምትሠዉ ከሆነ ተቀባይነት በሚያስገኝላችሁ መንገድ ልትሠዉት ይገባል። 30  መሥዋዕቱ በዚያው ዕለት መበላት ይኖርበታል። ከእሱም ላይ ምንም አስተርፋችሁ አታሳድሩ።+ እኔ ይሖዋ ነኝ። 31  “እናንተም ትእዛዛቴን ጠብቁ፤ እንዲሁም ፈጽሟቸው።+ እኔ ይሖዋ ነኝ። 32  ቅዱሱን ስሜን አታርክሱ፤+ እኔ በእስራኤላውያን መካከል ልቀደስ ይገባኛል።+ የምቀድሳችሁ እኔ ይሖዋ ነኝ፤+ 33  አምላክ መሆኔን ለእናንተ ለማሳየት ከግብፅ ምድር ያወጣኋችሁ እኔ ነኝ።+ እኔ ይሖዋ ነኝ።”

የግርጌ ማስታወሻ

ቃል በቃል “እስራኤላውያን ከሚያመጧቸው ቅዱስ ነገሮች ራሳቸውን እንዲለዩና።”
ወይም “ነፍስ።”
ወይም “ነፍስ።”
ወይም “ነፍስ።”
ቃል በቃል “ባዕድ ሰው።” ከአሮን ወገን ያልሆነን ሰው ያመለክታል።
ወይም “ነፍስ።”
ወይም “ባዕድ ሰው ብታገባ።”
ቃል በቃል “ባዕድ ሰው።” ከአሮን ወገን ያልሆነን ሰው ያመለክታል።