ዘኁልቁ 29:1-40

  • የተለያዩ መባዎች የሚቀርቡበት መንገድ (1-40)

    • መለከት የሚነፋበት ቀን (1-6)

    • የስርየት ቀን (7-11)

    • የዳስ በዓል (12-38)

29  “‘በሰባተኛው ወር ከወሩም በመጀመሪያው ቀን ቅዱስ ጉባኤ አድርጉ። ምንም ዓይነት ከባድ ሥራ መሥራት የለባችሁም።+ ይህም መለከት የምትነፉበት ቀን ነው።+  እናንተም አንድ ወይፈን፣ አንድ አውራ በግ እንዲሁም እያንዳንዳቸው አንድ ዓመት የሆናቸው ሰባት ተባዕት የበግ ጠቦቶች ይሖዋን ደስ የሚያሰኝ* መዓዛ ያለው የሚቃጠል መባ አድርጋችሁ ታቀርባላችሁ፤ ሁሉም እንከን የሌለባቸው መሆን ይኖርባቸዋል፤  ከእነዚህም ጋር ለወይፈኑ ሦስት አሥረኛ የኢፍ መስፈሪያ፣ ለአውራው በግ ደግሞ ሁለት አሥረኛ መስፈሪያ በዘይት የተለወሰ የላመ ዱቄት የእህል መባ አድርጋችሁ ታቀርባላችሁ፤  ለሰባቱ ተባዕት የበግ ጠቦቶች ለእያንዳንዳቸው አንድ አሥረኛ መስፈሪያ በዘይት የተለወሰ የላመ ዱቄት ታቀርባላችሁ፤  እንዲሁም ለእናንተ ማስተሰረያ እንዲሆን አንድ ተባዕት የፍየል ጠቦት የኃጢአት መባ አድርጋችሁ ታቀርባላችሁ።  ይህም በተለመደው አሠራር መሠረት ከሚቀርቡት ከወርሃዊው የሚቃጠል መባና አብሮት ከሚቀርበው የእህል መባ፣+ ከዘወትሩ የሚቃጠል መባና አብሮት ከሚቀርበው የእህል መባ+ እንዲሁም ከመጠጥ መባዎቻቸው+ በተጨማሪ ደስ የሚያሰኝ* መዓዛ ያለው ለይሖዋ በእሳት የሚቀርብ መባ ነው።  “‘በዚሁ በሰባተኛው ወር በአሥረኛው ቀን ቅዱስ ጉባኤ አድርጉ፤+ ራሳችሁን አጎሳቁሉ።* ምንም ዓይነት ሥራ አትሥሩ።+  አንድ ወይፈን፣ አንድ አውራ በግ እንዲሁም እያንዳንዳቸው አንድ ዓመት የሆናቸው ሰባት ተባዕት የበግ ጠቦቶች ደስ የሚያሰኝ* መዓዛ ያለው ለይሖዋ የሚቃጠል መባ አድርጋችሁ ታቀርባላችሁ፤ ሁሉም እንከን የሌለባቸው መሆን ይኖርባቸዋል።+  ከእነዚህም ጋር ለወይፈኑ ሦስት አሥረኛ መስፈሪያ፣ ለአውራው በግ ደግሞ ሁለት አሥረኛ መስፈሪያ በዘይት የተለወሰ የላመ ዱቄት የእህል መባ አድርጋችሁ ታቀርባላችሁ፤ 10  እንዲሁም ለሰባቱ ተባዕት የበግ ጠቦቶች ለእያንዳንዳቸው አንድ አሥረኛ መስፈሪያ በዘይት የተለወሰ የላመ ዱቄት ታቀርባላችሁ፤ 11  ለማስተሰረያ ከሚሆነው የኃጢአት መባ፣+ ከዘወትሩ የሚቃጠል መባና አብሮት ከሚቀርበው የእህል መባ እንዲሁም ከመጠጥ መባዎቻቸው በተጨማሪ አንድ የፍየል ጠቦት የኃጢአት መባ አድርጋችሁ ታቀርባላችሁ። 12  “‘በሰባተኛው ወር በ15ኛው ቀን ቅዱስ ጉባኤ አድርጉ። ምንም ዓይነት ከባድ ሥራ አትሥሩ፤ ለሰባት ቀንም ለይሖዋ በዓል አክብሩ።+ 13  እንዲሁም 13 ወይፈኖች፣ 2 አውራ በጎችና እያንዳንዳቸው አንድ ዓመት የሆናቸው 14 ተባዕት የበግ ጠቦቶች የሚቃጠል መባ+ ይኸውም ይሖዋን ደስ የሚያሰኝ* መዓዛ ያለው በእሳት የሚቀርብ መባ አድርጋችሁ አቅርቡ፤ ሁሉም እንከን የሌለባቸው መሆን ይኖርባቸዋል።+ 14  ከእነዚህም ጋር ለ13ቱ ወይፈኖች ለእያንዳንዳቸው ሦስት አሥረኛ መስፈሪያ፣ ለ2ቱ አውራ በጎች ደግሞ ለእያንዳንዳቸው ሁለት አሥረኛ መስፈሪያ በዘይት የተለወሰ የላመ ዱቄት የእህል መባ አድርጋችሁ አቅርቡ፤ 15  እንዲሁም ለ14ቱ ተባዕት የበግ ጠቦቶች ለእያንዳንዳቸው አንድ አሥረኛ መስፈሪያ በዘይት የተለወሰ የላመ ዱቄት አቅርቡ፤ 16  ከዘወትሩ የሚቃጠል መባ እንዲሁም አብሮት ከሚቀርበው የእህል መባና የመጠጥ መባ በተጨማሪ አንድ የፍየል ጠቦት የኃጢአት መባ አድርጋችሁ አቅርቡ።+ 17  “‘በሁለተኛው ቀን 12 ወይፈኖች፣ 2 አውራ በጎች እንዲሁም እያንዳንዳቸው አንድ ዓመት የሆናቸው 14 ተባዕት የበግ ጠቦቶች አቅርቡ፤ ሁሉም እንከን የሌለባቸው መሆን ይኖርባቸዋል፤+ 18  ለወይፈኖቹ፣ ለአውራ በጎቹና ለተባዕት የበግ ጠቦቶቹ በተለመደው አሠራር መሠረት በቁጥራቸው ልክ የእህል መባቸውንና የመጠጥ መባዎቻቸውን አቅርቡ፤ 19  ከዘወትሩ የሚቃጠል መባና አብሮት ከሚቀርበው የእህል መባ እንዲሁም ከመጠጥ መባዎቻቸው በተጨማሪ አንድ የፍየል ጠቦት የኃጢአት መባ አድርጋችሁ አቅርቡ።+ 20  “‘በሦስተኛው ቀን 11 ወይፈኖች፣ 2 አውራ በጎች እንዲሁም እያንዳንዳቸው አንድ ዓመት የሆናቸው 14 ተባዕት የበግ ጠቦቶች አቅርቡ፤ ሁሉም እንከን የሌለባቸው መሆን ይኖርባቸዋል፤+ 21  ለወይፈኖቹ፣ ለአውራ በጎቹና ለተባዕት የበግ ጠቦቶቹ በተለመደው አሠራር መሠረት በቁጥራቸው ልክ የእህል መባቸውንና የመጠጥ መባዎቻቸውን አቅርቡ፤ 22  ከዘወትሩ የሚቃጠል መባ እንዲሁም አብሮት ከሚቀርበው የእህል መባና የመጠጥ መባ በተጨማሪ አንድ ፍየል የኃጢአት መባ አድርጋችሁ አቅርቡ።+ 23  “‘በአራተኛው ቀን 10 ወይፈኖች፣ 2 አውራ በጎች እንዲሁም እያንዳንዳቸው አንድ ዓመት የሆናቸው 14 ተባዕት የበግ ጠቦቶች አቅርቡ፤ ሁሉም እንከን የሌለባቸው መሆን ይኖርባቸዋል፤+ 24  ለወይፈኖቹ፣ ለአውራ በጎቹና ለተባዕት የበግ ጠቦቶቹ በተለመደው አሠራር መሠረት በቁጥራቸው ልክ የእህል መባቸውንና የመጠጥ መባዎቻቸውን አቅርቡ፤ 25  ከዘወትሩ የሚቃጠል መባ እንዲሁም አብሮት ከሚቀርበው የእህል መባና የመጠጥ መባ በተጨማሪ አንድ የፍየል ጠቦት የኃጢአት መባ አድርጋችሁ አቅርቡ።+ 26  “‘በአምስተኛው ቀን 9 ወይፈኖች፣ 2 አውራ በጎች እንዲሁም እያንዳንዳቸው አንድ ዓመት የሆናቸው 14 ተባዕት የበግ ጠቦቶች አቅርቡ፤ ሁሉም እንከን የሌለባቸው መሆን ይኖርባቸዋል፤+ 27  ለወይፈኖቹ፣ ለአውራ በጎቹና ለተባዕት የበግ ጠቦቶቹ በተለመደው አሠራር መሠረት በቁጥራቸው ልክ የእህል መባቸውንና የመጠጥ መባዎቻቸውን አቅርቡ፤ 28  ከዘወትሩ የሚቃጠል መባ እንዲሁም አብሮት ከሚቀርበው የእህል መባና የመጠጥ መባ በተጨማሪ አንድ ፍየል የኃጢአት መባ አድርጋችሁ አቅርቡ።+ 29  “‘በስድስተኛውም ቀን 8 ወይፈኖች፣ 2 አውራ በጎች እንዲሁም እያንዳንዳቸው አንድ ዓመት የሆናቸው 14 ተባዕት የበግ ጠቦቶች አቅርቡ፤ ሁሉም እንከን የሌለባቸው መሆን ይኖርባቸዋል፤+ 30  ለወይፈኖቹ፣ ለአውራ በጎቹና ለተባዕት የበግ ጠቦቶቹ በተለመደው አሠራር መሠረት በቁጥራቸው ልክ የእህል መባቸውንና የመጠጥ መባዎቻቸውን አቅርቡ፤ 31  ከዘወትሩ የሚቃጠል መባ እንዲሁም አብረውት ከሚቀርቡት የእህል መባና የመጠጥ መባዎች በተጨማሪ አንድ ፍየል የኃጢአት መባ አድርጋችሁ አቅርቡ።+ 32  “‘በሰባተኛው ቀን 7 ወይፈኖች፣ 2 አውራ በጎች እንዲሁም እያንዳንዳቸው አንድ ዓመት የሆናቸው 14 ተባዕት የበግ ጠቦቶች አቅርቡ፤ ሁሉም እንከን የሌለባቸው መሆን ይኖርባቸዋል፤+ 33  ለወይፈኖቹ፣ ለአውራ በጎቹና ለተባዕት የበግ ጠቦቶቹ በተለመደው አሠራር መሠረት በቁጥራቸው ልክ የእህል መባቸውንና የመጠጥ መባዎቻቸውን አቅርቡ፤ 34  ከዘወትሩ የሚቃጠል መባ እንዲሁም አብሮት ከሚቀርበው የእህል መባና የመጠጥ መባ በተጨማሪ አንድ ፍየል የኃጢአት መባ አድርጋችሁ አቅርቡ።+ 35  “‘በስምንተኛው ቀን የተቀደሰ ጉባኤ አድርጉ። ምንም ዓይነት ከባድ ሥራ መሥራት የለባችሁም።+ 36  አንድ ወይፈን፣ አንድ አውራ በግ እንዲሁም እያንዳንዳቸው አንድ ዓመት የሆናቸው ሰባት ተባዕት የበግ ጠቦቶች የሚቃጠል መባ ይኸውም ይሖዋን ደስ የሚያሰኝ* መዓዛ ያለው በእሳት የሚቀርብ መባ አድርጋችሁ ታቀርባላችሁ፤ ሁሉም እንከን የሌለባቸው መሆን ይኖርባቸዋል፤+ 37  ለወይፈኑ፣ ለአውራው በግና ለተባዕት የበግ ጠቦቶቹ በተለመደው አሠራር መሠረት በቁጥራቸው ልክ የእህል መባቸውንና የመጠጥ መባዎቻቸውን አቅርቡ፤ 38  ከዘወትሩ የሚቃጠል መባ እንዲሁም አብሮት ከሚቀርበው የእህል መባና የመጠጥ መባ በተጨማሪ አንድ ፍየል የኃጢአት መባ አድርጋችሁ አቅርቡ።+ 39  “‘እነዚህም የሚቃጠሉ መባዎች፣+ የእህል መባዎች፣+ የመጠጥ መባዎችና+ የኅብረት መሥዋዕቶች+ አድርጋችሁ ከምታቀርቧቸው የስእለት መባዎችና+ የፈቃደኝነት መባዎች+ በተጨማሪ በየወቅቱ በምታከብሯቸው በዓላት+ ላይ ለይሖዋ የምታቀርቧቸው ናቸው።’” 40  ሙሴም ይሖዋ ያዘዘውን ነገር በሙሉ ለእስራኤላውያን ነገራቸው።

የግርጌ ማስታወሻ

ወይም “የሚያረጋጋ፤ የሚያበርድ።” ቃል በቃል “እረፍት የሚሰጥ።”
ወይም “የሚያረጋጋ፤ የሚያበርድ።” ቃል በቃል “እረፍት የሚሰጥ።”
ወይም “ነፍሳችሁን አጎሳቁሉ።” “ራስን ማጎሳቆል” በአብዛኛው መጾምን ጨምሮ የራስን ፍላጎት ከመፈጸም መቆጠብን የሚያሳዩ የተለያዩ ድርጊቶችን ሊያመለክት ይችላል።
ወይም “የሚያረጋጋ፤ የሚያበርድ።” ቃል በቃል “እረፍት የሚሰጥ።”
ወይም “የሚያረጋጋ፤ የሚያበርድ።” ቃል በቃል “እረፍት የሚሰጥ።”
ወይም “የሚያረጋጋ፤ የሚያበርድ።” ቃል በቃል “እረፍት የሚሰጥ።”