ዘዳግም 11:1-32

  • የይሖዋን ታላቅነት አይተሃል (1-7)

  • ተስፋይቱ ምድር (8-12)

  • ታዛዥነት የሚያስገኘው በረከት (13-17)

  • የአምላክ ቃል በልብህ ላይ ይታተም (18-25)

  • “በረከትና እርግማን” (26-32)

11  “አንተም አምላክህን ይሖዋን ውደድ፤+ ለእሱ ያለብህንም ግዴታ ምንጊዜም ተወጣ፤ እንዲሁም ደንቦቹን፣ ድንጋጌዎቹንና ትእዛዛቱን ሁልጊዜ ጠብቅ።  ዛሬ እየተናገርኩ ያለሁት ለእናንተ እንጂ የአምላካችሁን የይሖዋን ተግሣጽ፣+ የእሱን ታላቅነት፣+ የእሱን ብርቱ እጅና+ የተዘረጋ ክንድ ላላወቁት ወይም ላላዩት ለልጆቻችሁ እንዳልሆነ ታውቃላችሁ።  እነሱ በግብፅ ይኸውም በግብፁ ንጉሥ በፈርዖን ፊትና በመላው ምድሩ ላይ ያሳየውን ተአምራዊ ምልክትም ሆነ ያደረገውን ነገር አልተመለከቱም፤+  ወይም እናንተን እያሳደዱ ሳሉ በቀይ ባሕር ውስጥ በሰጠሙት በግብፅ ሠራዊት፣ በፈርዖን ፈረሶችና የጦር ሠረገሎች ላይ ያደረገውን አላዩም፤ ይሖዋም ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ* አጠፋቸው።+  እናንተ እዚህ ቦታ እስክትደርሱ ድረስ በምድረ በዳ ያደረገላችሁን ነገር አልተመለከቱም፤  ወይም ደግሞ የሮቤል ልጅ የኤልያብ ልጆች የሆኑትን ዳታንን እና አቤሮንን፣ ቤተሰቦቻቸውን፣ ድንኳኖቻቸውንና ከእነሱ ጋር ያበረውን ማንኛውንም ሕያው ፍጡር እስራኤላውያን ሁሉ እያዩ ምድር ተከፍታ በዋጠቻቸው ጊዜ በእነሱ ላይ ያደረገውን ነገር አልተመለከቱም።+  እናንተ፣ ይሖዋ ያደረጋቸውን ታላላቅ ሥራዎች በሙሉ በገዛ ዓይናችሁ አይታችኋል።  “ብርታት እንድታገኙና ወደምትወርሷት ምድር ተሻግራችሁ እንድትገቡ ዛሬ የምሰጣችሁን ትእዛዛት በሙሉ ጠብቁ፤  ይሖዋ ለአባቶቻችሁና ለዘሮቻቸው ለመስጠት በማለላቸው+ ወተትና ማር በምታፈሰው ምድር+ ላይ ዕድሜያችሁ እንዲረዝም+ እነዚህን ትእዛዛት በሙሉ ጠብቁ። 10  “የምትወርሳት ምድር ዘር ትዘራባት እንዲሁም ልክ እንደ አትክልት ስፍራ በእግርህ* በመስኖ ታጠጣት እንደነበረችው እንደወጣህባት እንደ ግብፅ ምድር አይደለችም። 11  ከዚህ ይልቅ ተሻግራችሁ የምትወርሷት ምድር ተራሮችና ሸለቋማ ሜዳዎች ያሉባት ምድር ናት።+ የሰማይን ዝናብ የምትጠጣ ምድር ናት፤+ 12  አምላክህ ይሖዋ የሚንከባከባት ምድር ናት። የአምላክህም የይሖዋ ዓይን ከዓመቱ መጀመሪያ እስከ መጨረሻው ድረስ ዘወትር በእሷ ላይ ነው። 13  “እኔ ዛሬ የማዛችሁን ትእዛዛቴን በትጋት ብትፈጽሙ፣ አምላካችሁን ይሖዋን ብትወዱት እንዲሁም በሙሉ ልባችሁና በሙሉ ነፍሳችሁ* ብታገለግሉት፣+ 14  እኔ ደግሞ ለምድራችሁ በወቅቱ ዝናብን ይኸውም የፊተኛውንና የኋለኛውን ዝናብ እሰጣለሁ፤ አንተም እህልህን፣ አዲስ የወይን ጠጅህንና ዘይትህን ትሰበስባለህ።+ 15  ለእንስሶችህም በሜዳህ ላይ ዕፀዋት አበቅልልሃለሁ፤ አንተም በልተህ ትጠግባለህ።+ 16  ልባችሁ እንዳይታለልና ዞር ብላችሁ ሌሎች አማልክትን እንዳታመልኩ እንዲሁም እንዳትሰግዱላቸው ተጠንቀቁ።+ 17  አለዚያ የይሖዋ ቁጣ በእናንተ ላይ ይነድዳል፤ ዝናብ ዘንቦ ምድሪቱ ምርት እንዳትሰጥ ሰማያትን ይዘጋል፤+ እናንተም ይሖዋ ከሚሰጣችሁ መልካም ምድር ፈጥናችሁ ትጠፋላችሁ።+ 18  “እነዚህን ቃሎቼን በልባችሁና በነፍሳችሁ* ላይ አትሟቸው፤ በእጃችሁም ላይ እንደ ማስታወሻ እሰሯቸው፤ በግንባራችሁም ላይ* እንደታሰረ ነገር ይሁኑ።+ 19  በቤታችሁ ስትቀመጡ፣ በመንገድ ላይ ስትሄዱ፣ ስትተኙና ስትነሱ ስለ እነሱ በመናገር ለልጆቻችሁ አስተምሯቸው።+ 20  በቤታችሁ መቃኖችና በግቢያችሁ በሮች ላይ ጻፏቸው፤ 21  ይህን ካደረጋችሁ ሰማይ ከምድር በላይ እስካለ ድረስ ይሖዋ ለአባቶቻችሁ ለመስጠት በማለላቸው ምድር+ ላይ የእናንተም ሆነ የልጆቻችሁ ዕድሜ ይረዝማል።+ 22  “አምላካችሁን ይሖዋን እንድትወዱ፣+ በመንገዶቹ ሁሉ እንድትሄዱና ከእሱ ጋር እንድትጣበቁ የሰጠኋችሁን እነዚህን ሁሉ ትእዛዛት በጥብቅ ብትከተሉና ብትፈጽሟቸው+ 23  ይሖዋም እነዚህን ሁሉ ብሔራት ከፊታችሁ ያባርራቸዋል፤+ እናንተም ከእናንተ ይልቅ ታላቅ የሆኑትንና ብዙ ሕዝብ ያላቸውን ብሔራት ታስለቅቃላችሁ።+ 24  እግራችሁ የረገጠው ቦታ ሁሉ የእናንተ ይሆናል።+ ወሰናችሁም ከምድረ በዳው አንስቶ እስከ ሊባኖስ እንዲሁም ከወንዙ ይኸውም ከኤፍራጥስ ወንዝ አንስቶ በስተ ምዕራብ እስካለው ባሕር* ድረስ ይሆናል።+ 25  ማንም ሰው ሊቋቋማችሁ አይችልም።+ አምላካችሁ ይሖዋም ቃል በገባላችሁ መሠረት በምትረግጡት ምድር ሁሉ ላይ ሽብርና ፍርሃት ይለቃል።+ 26  “እንግዲህ ዛሬ ይህን በረከትና እርግማን በፊታችሁ አስቀምጫለሁ፦+ 27  እኔ ዛሬ የማዛችሁን የአምላካችሁን የይሖዋን ትእዛዛት ከፈጸማችሁ በረከቱን ታገኛላችሁ፤+ 28  የአምላካችሁን የይሖዋን ትእዛዛት ካልፈጸማችሁና እኔ ዛሬ እንድትከተሉት ከማዛችሁ መንገድ ዞር በማለት የማታውቋቸውን አማልክት ከተከተላችሁ ግን እርግማኑ ይደርስባችኋል።+ 29  “አምላካችሁ ይሖዋ ርስት አድርጋችሁ ወደምትወርሷት ምድር በሚያስገባችሁ ጊዜ በረከቱን በገሪዛን ተራራ ላይ እርግማኑን ደግሞ በኤባል ተራራ ላይ ታውጃላችሁ።*+ 30  እነዚህ ተራሮች የሚገኙት ከዮርዳኖስ በስተ ምዕራብ፣* በአረባ በሚኖሩት በከነአናውያን ምድር ከጊልጋል ትይዩ በሞሬ ትላልቅ ዛፎች አጠገብ አይደለም?+ 31  አሁን አምላካችሁ ይሖዋ የሚሰጣችሁን ምድር ገብታችሁ ለመውረስ ዮርዳኖስን ልትሻገሩ ነው።+ እንግዲህ ምድሪቱን ወርሳችሁ በእሷ ላይ ስትኖሩ 32  ዛሬ በፊታችሁ ያስቀመጥኳቸውን ሥርዓቶችና ድንጋጌዎች በሙሉ በጥንቃቄ ፈጽሙ።+

የግርጌ ማስታወሻ

ወይም “እስከዚህ ቀን ድረስ።”
ወይም “በእግርህ ታጠጣት።” በእግር ተጠቅሞ በውኃ ኃይል የሚሽከረከርን መንኮራኩር በማንቀሳቀስም ሆነ የውኃ መውረጃ ቦዮችን በመሥራትና በመክፈት ውኃ ማጠጣትን ያመለክታል።
ቃል በቃል “በዓይኖቻችሁም መካከል።”
ታላቁን ባሕር፣ ሜድትራንያንን ያመለክታል።
ወይም “ትሰጣላችሁ።”
ወይም “በፀሐይ መግቢያ።”