ዘዳግም 12:1-32

  • አምላክ በሚመርጠው ስፍራ የሚቀርብ አምልኮ (1-14)

  • ሥጋ እንዲበሉ ቢፈቀድላቸውም ደም እንዳይበሉ ታዘዋል (15-28)

  • በሌሎች አማልክት እንዳትጠመድ ተጠንቀቅ (29-32)

12  “የአባቶቻችሁ አምላክ ይሖዋ እንድትወርሷት በሚሰጣችሁ ምድር ላይ በሕይወት በምትኖሩበት ዘመን ሁሉ በጥንቃቄ ልትፈጽሟቸው የሚገቡ ሥርዓቶችና ድንጋጌዎች እነዚህ ናቸው።  ከምድራቸው የምታስለቅቋቸው ብሔራት አማልክታቸውን ያመልኩባቸው የነበሩትን ቦታዎች በሙሉ፣ በረጃጅም ተራሮችም ሆነ በኮረብቶች ላይ ወይም በተንዠረገጉ ዛፎች ሥር ያሉትን ስፍራዎች ሙሉ በሙሉ አጥፉ።+  መሠዊያዎቻቸውን አፈራርሱ፤ የማምለኪያ ዓምዶቻቸውን አድቅቁ፤+ የማምለኪያ ግንዶቻቸውንም* በእሳት አቃጥሉ፤ የአማልክታቸውን የተቀረጹ ምስሎች ሰባብራችሁ ጣሉ፤+ ስማቸውንም ከዚያ ስፍራ ሙሉ በሙሉ ደምስሱ።+  “እነሱ አማልክታቸውን በሚያመልኩበት መንገድ አምላካችሁን ይሖዋን አታምልኩ።+  ከዚህ ይልቅ በነገዶቻችሁ ሁሉ መካከል ስሙን ሊያጸናበትና ማደሪያ ስፍራው ሊያደርገው በሚመርጠው በማንኛውም ቦታ አምላካችሁን ይሖዋን ፈልጉ፤ ወደዚያም ስፍራ ሂዱ።+  የሚቃጠሉ መባዎቻችሁን፣+ መሥዋዕቶቻችሁን፣ አሥራቶቻችሁን፣+ ከእጃችሁ የሚዋጣውን መዋጮ፣+ የስእለት መባዎቻችሁን፣ የፈቃደኝነት መባዎቻችሁን+ እንዲሁም የከብታችሁንና የመንጋችሁን በኩራት+ የምትወስዱት ወደዚያ ስፍራ ነው።  እናንተም ሆናችሁ ቤተሰቦቻችሁ በዚያ በአምላካችሁ በይሖዋ ፊት ብሉ፤+ አምላካችሁ ይሖዋ ስለባረካችሁ በሥራችሁ ሁሉ ተደሰቱ።+  “ዛሬ እዚህ እያደረግን እንዳለነው እያንዳንዳችሁ በራሳችሁ አመለካከት ትክክል መስሎ የታያችሁን ማድረግ የለባችሁም፤  ምክንያቱም አሁን ይህን የምታደርጉት ወደምታርፉበት ቦታና+ አምላካችሁ ይሖዋ ወደሚሰጣችሁ ርስት ገና ስላልገባችሁ ነው። 10  ዮርዳኖስን በምትሻገሩበትና+ አምላካችሁ ይሖዋ ርስት አድርጎ በሚሰጣችሁ ምድር ላይ በምትኖሩበት ጊዜ በዙሪያችሁ ካሉ ጠላቶቻችሁ ሁሉ ያሳርፋችኋል፤ እናንተም ያለስጋት ትቀመጣላችሁ።+ 11  የማዛችሁንም ነገር በሙሉ ይኸውም የሚቃጠሉ መባዎቻችሁን፣ መሥዋዕቶቻችሁን፣ አሥራቶቻችሁን፣+ የእጃችሁን መዋጮና ለይሖዋ የተሳላችሁትን ማንኛውንም የስእለት መባ አምላካችሁ ይሖዋ ለስሙ ማደሪያ እንዲሆን ወደሚመርጠው ስፍራ ታመጣላችሁ።+ 12  እናንተ፣ ወንዶች ልጆቻችሁ፣ ሴቶች ልጆቻችሁ፣ ወንድ ባሪያዎቻችሁ፣ ሴት ባሪያዎቻችሁ እንዲሁም በከተሞቻችሁ* ውስጥ የሚኖር ሌዋዊ በአምላካችሁ በይሖዋ ፊት ትደሰታላችሁ፤+ ምክንያቱም ሌዋዊው በእናንተ መካከል ድርሻም ሆነ ውርሻ አልተሰጠውም።+ 13  የሚቃጠሉ መባዎችህን በፈለግከው በየትኛውም ቦታ እንዳታቀርብ ተጠንቀቅ።+ 14  ከዚህ ይልቅ የሚቃጠሉ መባዎችህን ይሖዋ በሚመርጠው የነገዶችህ ይዞታ በሆነው ቦታ ብቻ አቅርብ፤ በዚያም እኔ የማዝህን ነገር ሁሉ አድርግ።+ 15  “አምላክህ ይሖዋ በሰጠህ በረከት መጠን በከተሞችህ ሁሉ* አንተን ባሰኘህ* በማንኛውም ጊዜ እንስሳትን አርደህ ሥጋ መብላት ትችላለህ።+ የሜዳ ፍየልና ርኤም* እንደምትበላ ሁሉ ንጹሕ ያልሆነው ሰውም ሆነ ንጹሕ የሆነው ሰው ሊበላው ይችላል። 16  ደሙን ግን እንዳትበሉ፤+ ከዚህ ይልቅ እንደ ውኃ መሬት ላይ አፍሱት።+ 17  የእህልህን፣ የአዲሱን የወይን ጠጅህንና የዘይትህን አንድ አሥረኛ፣ የከብትህንና የመንጋህን በኩር፣+ የምትሳለውን ማንኛውንም የስእለት መባ፣ የፈቃደኝነት መባዎችህን ወይም የእጅህን መዋጮ በከተሞችህ* ውስጥ እንድትበላ አይፈቀድልህም። 18  እነዚህንም አንተ፣ ወንድ ልጅህ፣ ሴት ልጅህ፣ ወንድ አገልጋይህ፣ ሴት አገልጋይህ እንዲሁም በከተሞችህ* የሚኖሩ ሌዋውያን አምላክህ ይሖዋ በሚመርጠው ስፍራ+ በአምላክህ በይሖዋ ፊት ትበሏቸዋላችሁ፤ አንተም በሥራህ ሁሉ በአምላክህ በይሖዋ ፊት ትደሰታለህ። 19  በምድርህ ላይ በሕይወት እስካለህ ድረስ ሌዋውያንን ቸል እንዳትል ተጠንቀቅ።+ 20  “አምላክህ ይሖዋ ቃል በገባልህ መሠረት+ ግዛትህን በሚያሰፋልህ ጊዜ+ ሥጋ መብላት ፈልገህ* ‘ሥጋ አማረኝ’ ብትል ባሰኘህ* ጊዜ ሁሉ ሥጋ ብላ።+ 21  አምላክህ ይሖዋ ስሙ እንዲኖርበት የሚመርጠው ስፍራ+ አንተ ካለህበት የራቀ ከሆነ ይሖዋ ከሰጠህ ከከብትህ ወይም ከመንጋህ መካከል እኔ ባዘዝኩህ መሠረት አርደህ ባሰኘህ* ጊዜ ሁሉ በከተሞችህ* ውስጥ ብላ። 22  የሜዳ ፍየልንና ርኤምን እንደምትበላው ሁሉ ይህንም ልትበላው ትችላለህ፤+ ንጹሕ ያልሆነው ሰውም ሆነ ንጹሕ የሆነው ሰው ሊበላው ይችላል። 23  ብቻ ደሙን እንዳትበሉ ተጠንቀቁ፤+ ምክንያቱም ደም ሕይወት* ነው፤+ ሕይወትን* ደግሞ ከሥጋ ጋር መብላት የለብህም። 24  ደሙን ፈጽሞ እንዳትበላ። ከዚህ ይልቅ እንደ ውኃ መሬት ላይ አፍስሰው።+ 25  ደሙን አትብላ፤ ምክንያቱም እንዲህ ስታደርግ በይሖዋ ፊት ትክክል የሆነውን ነገር ትፈጽማለህ፤ ይህን የምታደርገው ለአንተም ሆነ ከአንተ በኋላ ለሚመጡት ልጆችህ መልካም እንዲሆንላችሁ ነው። 26  ይሖዋ ወደሚመርጠው ስፍራ ስትመጣ የአንተ የሆኑትን ቅዱስ ነገሮችና የስእለት መባዎችህን ብቻ መያዝ ይኖርብሃል። 27  የሚቃጠሉ መባዎችህን፣ ሥጋውንና ደሙን+ በአምላክህ በይሖዋ መሠዊያ ላይ ታቀርባለህ፤ የመሥዋዕቶችህም ደም በአምላክህ በይሖዋ መሠዊያ ላይ መፍሰስ ይኖርበታል፤+ ሥጋውን ግን መብላት ትችላለህ። 28  “እኔ የማዝህን እነዚህን ቃላት በሙሉ በጥንቃቄ ፈጽም፤ ምክንያቱም እንዲህ ስታደርግ በአምላክህ በይሖዋ ፊት መልካምና ትክክል የሆነውን ትፈጽማለህ፤ ይህን የምታደርገው ለአንተም ሆነ ከአንተ በኋላ ለሚመጡት ልጆችህ ምንጊዜም መልካም እንዲሆንላችሁ ነው። 29  “ከምድራቸው የምታስለቅቃቸውን ብሔራት አምላክህ ይሖዋ ሲያጠፋቸውና+ በምድራቸው ላይ ስትኖር 30  እነሱ ከጠፉ በኋላ በእነሱ እንዳትጠመድ ተጠንቀቅ። ‘እነዚህ ብሔራት አማልክታቸውን ያመልኩ የነበረው እንዴት ነው? ቆይ እኔም እንደ እነሱ አደርጋለሁ’ ብለህ ስለ አማልክታቸው አትጠይቅ።+ 31  አንተ በአምላክህ በይሖዋ ላይ ይህን ማድረግ የለብህም፤ ምክንያቱም እነሱ ይሖዋ የሚጠላውን አስጸያፊ ነገር ሁሉ ለአማልክታቸው ያደርጋሉ፤ ሌላው ቀርቶ ወንዶችና ሴቶች ልጆቻቸውን ለአማልክታቸው በእሳት ያቃጥላሉ።+ 32  እናንተ እኔ የማዛችሁን እያንዳንዱን ነገር በጥንቃቄ ፈጽሙ።+ በእሱ ላይ ምንም አትጨምሩ፤ ከእሱም ላይ ምንም አትቀንሱ።+

የግርጌ ማስታወሻ

ቃል በቃል “በደጆቻችሁ።”
ቅርንጫፍ የሚመስሉ ቀንዶች ያሉት አጥቢ እንስሳ፤ ከአጋዘን ጋር ይመሳሰላል።
ወይም “ነፍስህ ባሰኛት።”
ቃል በቃል “በደጆችህ ሁሉ ውስጥ።”
ቃል በቃል “በደጆችህ።”
ቃል በቃል “በደጆችህ።”
ወይም “ነፍስህ ሥጋ መብላት ፈልጋ።”
ወይም “ነፍስህ ባሰኛት።”
ወይም “ነፍስህ ባሰኛት።”
ቃል በቃል “በደጆችህ።”
ወይም “ነፍስ።”
ወይም “ነፍስን።”