ዘዳግም 31:1-30

  • ሙሴ ሊሞት ሲቃረብ (1-8)

  • ሕጉን በሕዝብ ፊት ስለ ማንበብ የተሰጠ መመሪያ (9-13)

  • ኢያሱ በሙሴ እግር ተተካ (14, 15)

  • እስራኤላውያን እንደሚያምፁ ትንቢት ተነገረ (16-30)

    • እስራኤላውያን ሊማሩት የሚገባቸው መዝሙር (19, 22, 30)

31  ከዚያም ሙሴ ወጥቶ እነዚህን ቃላት ለመላው እስራኤል ተናገረ፤  እንዲህም አላቸው፦ “እንግዲህ እኔ አሁን 120 ዓመት ሆኖኛል።+ ይሖዋ ‘የዮርዳኖስን ወንዝ አትሻገርም’+ ስላለኝ ከእንግዲህ ልመራችሁ* አልችልም።  ከፊትህ የሚሻገረው አምላክህ ይሖዋ ነው፤ እሱ ራሱም እነዚህን ብሔራት ከፊትህ ያጠፋቸዋል፤ አንተም ታባርራቸዋለህ።+ ልክ ይሖዋ በተናገረውም መሠረት እየመራ የሚያሻግርህ ኢያሱ ነው።+  ይሖዋ የአሞራውያንን ነገሥታት ሲሖንን+ እና ኦግን+ እንዲሁም ምድራቸውን ባጠፋ ጊዜ በእነሱ ላይ እንዳደረገው ሁሉ በእነዚህም ብሔራት ላይ እንዲሁ ያደርግባቸዋል።+  ይሖዋ እነሱን ድል ያደርግላችኋል፤ እናንተም እኔ በሰጠኋችሁ ትእዛዝ ሁሉ መሠረት ታደርጉባቸዋላችሁ።+  ደፋርና ብርቱ ሁኑ።+ ከእናንተ ጋር የሚሄደው አምላካችሁ ይሖዋ ስለሆነ አትፍሯቸው ወይም በፊታቸው አትሸበሩ።+ እሱ አይጥላችሁም ወይም አይተዋችሁም።”+  ከዚያም ሙሴ ኢያሱን ጠርቶ በመላው እስራኤል ፊት እንዲህ አለው፦ “ደፋርና ብርቱ ሁን፤+ ምክንያቱም ይህን ሕዝብ ይሖዋ ለአባቶቻቸው ሊሰጣቸው ወደማለላቸው ምድር የምታስገባው አንተ ነህ፤ ደግሞም ይህን ምድር ርስት አድርገህ ትሰጣቸዋለህ።+  በፊትህ የሚሄደው ይሖዋ ነው፤ እሱ ምንጊዜም ከአንተ ጋር ይሆናል።+ አይጥልህም ወይም አይተውህም። አትፍራ ወይም አትሸበር።”+  ከዚያም ሙሴ ይህን ሕግ ጽፎ+ የይሖዋን የቃል ኪዳን ታቦት ለሚሸከሙት ሌዋውያን ካህናትና ለእስራኤል ሽማግሌዎች በሙሉ ሰጣቸው። 10  ሙሴ እንዲህ ሲል አዘዛቸው፦ “በየሰባት ዓመቱ መጨረሻ፣ በዓመቱ ውስጥ ዕዳ በሚሰረዝበት+ በተወሰነው ጊዜ ላይ ማለትም የዳስ* በዓል+ ሲከበር 11  መላው እስራኤል አምላክህ ይሖዋ በሚመርጠው ስፍራ በፊቱ በሚሰበሰብበት+ ጊዜ ይህን ሕግ እስራኤላውያን በሙሉ እንዲሰሙት አንብብላቸው።+ 12  ስለ አምላካችሁ ስለ ይሖዋ ይሰሙና ይማሩ እንዲሁም እሱን ይፈሩ ዘንድ ብሎም የዚህን ሕግ ቃላት በሙሉ በጥንቃቄ እንዲፈጽሙ ሕዝቡን ማለትም ወንዶችን፣ ሴቶችን፣ ልጆችንና* በከተሞችህ ውስጥ* የሚኖረውን የባዕድ አገር ሰው ሰብስብ።+ 13  ከዚያም ይህን ሕግ የማያውቁት ልጆቻቸው ይሰማሉ፤+ እንዲሁም ዮርዳኖስን ተሻግራችሁ በምትወርሷት ምድር ላይ በምትኖሩበት ዘመን ሁሉ አምላካችሁን ይሖዋን መፍራት ይማራሉ።”+ 14  ይሖዋም ሙሴን እንዲህ አለው፦ “እንግዲህ የምትሞትበት ጊዜ ቀርቧል።+ ኢያሱን ጥራውና መሪ አድርጌ እንድሾመው በመገናኛ ድንኳኑ ተገኙ።”*+ በመሆኑም ሙሴና ኢያሱ ሄደው በመገናኛ ድንኳኑ ተገኙ። 15  ከዚያም ይሖዋ በደመና ዓምድ ውስጥ ሆኖ በድንኳኑ ላይ ተገለጠ፤ የደመናውም ዓምድ በድንኳኑ መግቢያ ላይ ቆመ።+ 16  ይሖዋም ሙሴን እንዲህ አለው፦ “እንግዲህ አንተ መሞትህ ነው፤* ይህም ሕዝብ በሚሄድበት ምድር በዙሪያው ካሉ ባዕዳን አማልክት ጋር መንፈሳዊ ምንዝር ይፈጽማል።+ እኔንም ይተዉኛል፤+ ከእነሱም ጋር የገባሁትን ቃል ኪዳን ያፈርሳሉ።+ 17  በዚያን ጊዜ ቁጣዬ በእነሱ ላይ ይነዳል፤+ እኔም እተዋቸዋለሁ፤+ ሙሉ በሙሉ እስኪደመሰሱም ድረስ ፊቴን ከእነሱ እሰውራለሁ።+ ከዚያም ብዙ መከራና ችግር ይደርስባቸዋል፤+ እነሱም ‘ይህ ሁሉ መከራ የደረሰብን አምላካችን በመካከላችን ስለሌለ አይደል?’+ ይላሉ። 18  ሆኖም ወደ ሌሎች አማልክት ዞር በማለት ከፈጸሙት መጥፎ ድርጊት ሁሉ የተነሳ በዚያ ቀን ፊቴን ከእነሱ እሰውራለሁ።+ 19  “እንግዲህ አሁን ይህን መዝሙር ለራሳችሁ ጻፉ፤+ ለእስራኤላውያንም አስተምሯቸው።+ ይህ መዝሙር በእስራኤል ሕዝብ ላይ ምሥክሬ ሆኖ ያገለግል ዘንድ እንዲማሩት አድርጉ።*+ 20  ምክንያቱም ለአባቶቻቸው ወደማልኩላቸው+ ወተትና ማር ወደምታፈሰው ምድር+ በማስገባቸው ጊዜ በልተው ሲጠግቡና ሲበለጽጉ*+ ወደ ሌሎች አማልክት ዞር ይላሉ፤ እንዲሁም እነሱን ያገለግላሉ፤ እኔንም ይንቁኛል፤ ቃል ኪዳኔንም ያፈርሳሉ።+ 21  ብዙ መከራና ችግር በሚደርስባቸው ጊዜ+ ይህ መዝሙር ምሥክር ይሆንባቸዋል፤ (ምክንያቱም ዘሮቻቸው ይህን መዝሙር ሊዘነጉት አይገባም፤) እኔ እንደሆነ ወደማልኩላቸው ምድር ገና ሳላስገባቸው ምን ዓይነት ዝንባሌ እንዳዳበሩ አውቄአለሁ።”+ 22  ስለዚህ ሙሴ ይህን መዝሙር በዚያን ቀን ጻፈው፤ እስራኤላውያንንም አስተማራቸው። 23  እሱም* የነዌን ልጅ ኢያሱን ሾመው፤+ እንዲህም አለው፦ “ደፋርና ብርቱ ሁን፤+ ምክንያቱም እስራኤላውያንን ወደማልኩላቸው ምድር የምታስገባቸው አንተ ነህ፤+ እኔም ምንጊዜም ከአንተ ጋር እሆናለሁ።” 24  ሙሴም የዚህን ሕግ ቃላት በሙሉ በመጽሐፍ ላይ ጽፎ+ እንደጨረሰ 25  የይሖዋን የቃል ኪዳን ታቦት የሚሸከሙትን ሌዋውያኑን እንዲህ ሲል አዘዛቸው፦ 26  “ይህን የሕግ መጽሐፍ+ ወስዳችሁ በአምላካችሁ በይሖዋ የቃል ኪዳን ታቦት+ አጠገብ አስቀምጡት፤ ይህም በዚያ በእናንተ ላይ ምሥክር ሆኖ ያገለግላል። 27  ምክንያቱም እናንተ ዓመፀኛና+ ግትር*+ መሆናችሁን በሚገባ አውቃለሁ። እኔ ዛሬ ከእናንተ ጋር በሕይወት እያለሁ በይሖዋ ላይ እንዲህ ካመፃችሁ ከሞትኩ በኋላማ ምን ያህል ታምፁ! 28  የነገዶቻችሁን ሽማግሌዎችና አለቆቻችሁን በሙሉ ሰብስቡልኝ፤ እኔም ጆሯቸው እየሰማ እነዚህን ቃላት ልናገር፤ ሰማይንና ምድርንም በእነሱ ላይ ምሥክሮች አድርጌ ልጥራ።+ 29  ምክንያቱም እኔ ከሞትኩ በኋላ ክፉ ድርጊት እንደምትፈጽሙና ካዘዝኳችሁ መንገድ ዞር እንደምትሉ በሚገባ አውቃለሁ።+ በይሖዋም ፊት መጥፎ የሆነውን ነገር ስለምትፈጽሙና በእጆቻችሁ ሥራ ስለምታስቆጡት ወደፊት መከራ ይደርስባችኋል።”+ 30  ከዚያም ሙሴ መላው የእስራኤል ጉባኤ እየሰማ የዚህን መዝሙር ቃላት ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ እንዲህ ሲል ተናገረ፦+

የግርጌ ማስታወሻ

ቃል በቃል “ልወጣና ልገባ።”
ወይም “የጊዜያዊ መጠለያ።”
ቃል በቃል “ሕፃናትንና።”
ቃል በቃል “በደጆችህ ውስጥ።”
ወይም “ቦታችሁን ያዙ።”
ቃል በቃል “ከአባቶችህ ጋር ትተኛለህ።”
ቃል በቃል “በአፋቸው ውስጥ አድርጉት።”
ቃል በቃል “ሲወፍሩ።”
አምላክን እንደሚያመለክት ከሁኔታው መረዳት ይቻላል።
ቃል በቃል “አንገተ ደንዳና።”