ዘዳግም 33:1-29

  • ሙሴ የእስራኤልን ነገዶች ባረከ (1-29)

    • የይሖዋ ‘ዘላለማዊ ክንዶች’ (27)

33  የእውነተኛው አምላክ ሰው ሙሴ ከመሞቱ በፊት እስራኤላውያንን የባረካቸው በረከት ይህ ነው።+  እንዲህ አለ፦ “ይሖዋ ከሲና መጣ፤+ከሴይርም ሆኖ አበራባቸው። ከፋራን ተራራማ አካባቢዎችም በክብር አበራ፤+ከእሱም ጋር አእላፋት ቅዱሳን* ነበሩ፤+በቀኙም ተዋጊዎቹ አሉ።+   እሱ ሕዝቡን ይወዳል፤+ቅዱስ የሆነው ሕዝብ ሁሉ እጅህ ውስጥ ነው።+ እነሱም እግርህ ሥር ተቀምጠዋል፤+ቃልህንም ይሰማሉ።+   (ሙሴ ትእዛዝን ይኸውም ሕግን ሰጠን፤+ይህም ለያዕቆብ ጉባኤ እንደ ርስት ነው።)+   የሕዝቡ መሪዎች ከመላው የእስራኤል ነገድ ጋር+አንድ ላይ በተሰበሰቡ ጊዜ፣+አምላክ በየሹሩን*+ ላይ ንጉሥ ሆነ።   ሮቤል በሕይወት ይኑር፣ አይሙት፤+የወገኖቹም ቁጥር አይቀንስ።”+   ይሁዳንም እንዲህ ሲል ባረከው፦+ “ይሖዋ ሆይ፣ የይሁዳን ድምፅ ስማ፤+ወደ ሕዝቦቹም መልሰህ አምጣው። እጆቹ የእሱ ለሆነው ይከላከላሉ፤*አንተም ጠላቶቹን እንዲዋጋ እርዳው።”+   ስለ ሌዊም እንዲህ አለ፦+ “የአንተ* ቱሚምና ኡሪም+ ለአንተ ታማኝ ለሆነ፣+በማሳህ ለፈተንከው ሰው ይሆናል፤+ በመሪባ ውኃዎች አጠገብ ተጣላኸው፤+   ሰውየው አባቱንና እናቱን በተመለከተ ‘ስለ እነሱ ግድ የለኝም’ አለ። ሌላው ቀርቶ ወንድሞቹን እንኳ አልተቀበለም፤+የገዛ ልጆቹንም ችላ አለ። ቃልህን ታዘዋልና፤ቃል ኪዳንህንም ጠብቀዋል።+ 10  ለያዕቆብ ድንጋጌህን፣+ለእስራኤልም ሕግህን ያስተምሩ።+ ደስ የሚያሰኝ መዓዛ እንዲሸትህ ዕጣን ያቅርቡልህ፤+በመሠዊያህም ላይ ሙሉ በሙሉ የሚቀርብ መባ ይሠዉልህ።+ 11  ይሖዋ ሆይ፣ ጉልበቱን ባርክለት፤በእጆቹም ሥራ ደስ ይበልህ። እሱን የሚጠሉት ዳግመኛ እንዳያንሰራሩበእሱ ላይ የሚነሱትን እግራቸውን* አድቅቅ።” 12  ስለ ቢንያም እንዲህ አለ፦+ “ይሖዋ የወደደው ያለስጋት አብሮት ይኑር፤ቀኑን ሙሉ ይከልለዋልና፤በትከሻዎቹም መካከል ይኖራል።” 13  ስለ ዮሴፍ እንዲህ አለ፦+ “ይሖዋ ከሰማይ በሚወርዱ ምርጥ ነገሮች፣በጤዛና ከታች በሚመነጩ ውኃዎች+ምድሩን ይባርክ፤+ 14  እንዲሁም ፀሐይ በምታስገኛቸው ምርጥ ነገሮች፣በየወሩ በሚገኝ ምርጥ ፍሬ፣+ 15  ጥንታዊ ከሆኑ ተራሮች* በሚገኙ ምርጥ ነገሮች፣+ጸንተው ከሚኖሩት ኮረብቶች በሚገኙ ምርጥ ነገሮች፣ 16  ከምድር በሚገኙ ምርጥ ነገሮችና ምድርን በሞሉ ምርጥ ነገሮች፣+በቁጥቋጦው ውስጥ በተገለጠው በእሱ ሞገስ ይባርክ።+ እነዚህ ሁሉ በዮሴፍ ራስ ላይ፣ከወንድሞቹ መካከል ተነጥሎ በወጣው አናት ላይ ይውረዱ።+ 17  ግርማው እንደ በኩር በሬ ነው፤ቀንዶቹም የዱር በሬ ቀንድ ናቸው። በእነሱም ሰዎችን፣ሕዝቦችን ሁሉ እስከ ምድር ዳርቻ ይገፋል።* እነሱ የኤፍሬም አሥር ሺዎች ናቸው፤+የምናሴም ሺዎች ናቸው።” 18  ስለ ዛብሎን እንዲህ አለ፦+ “ዛብሎን ሆይ፣ በመውጣትህ ደስ ይበልህ፤አንተም ይሳኮር፣ በድንኳኖችህ ውስጥ ደስ ይበልህ።+ 19  ሰዎችን ወደ ተራራው ይጠራሉ። በዚያም የጽድቅ መሥዋዕቶችን ያቀርባሉ። ምክንያቱም በባሕሮች ውስጥ ካለው የተትረፈረፈ ሀብት፣በአሸዋም ውስጥ ተሰውሮ ከተከማቸው ነገር* ዝቀው ያወጣሉ።” 20  ስለ ጋድ እንዲህ አለ፦+ “የጋድን ድንበሮች የሚያሰፋ የተባረከ ነው።+ በዚያ እንደ አንበሳ ይተኛል፤ክንድን፣ አዎ አናትን ለመዘነጣጠል ተዘጋጅቶ ይጠብቃል። 21  የመጀመሪያውን መርጦ ለራሱ ይወስዳል፤+በዚያ የሕግ ሰጪው ድርሻ ተለይቶ ተቀምጧልና።+ የሕዝቡ መሪዎች አንድ ላይ ይሰበሰባሉ። የይሖዋን ጽድቅና ድንጋጌዎች፣በእስራኤል ያስፈጽማል።” 22  ስለ ዳን እንዲህ አለ፦+ “ዳን የአንበሳ ደቦል ነው።+ ከባሳን ዘሎ ይወጣል።”+ 23  ስለ ንፍታሌም እንዲህ አለ፦+ “ንፍታሌም በይሖዋ ሞገስ ረክቷል፤በእሱም በረከት ተሞልቷል። ምዕራቡንና ደቡቡን ውረስ።” 24  ስለ አሴር እንዲህ አለ፦+ “አሴር በልጆች የተባረከ ነው። በወንድሞቹ ፊት ሞገስ ያግኝ፤እግሩንም ዘይት ውስጥ ይንከር።* 25  የበርህ መቀርቀሪያ ብረትና መዳብ ናቸው፤+በዘመንህ ሁሉ ያለስጋት ትኖራለህ።* 26  አንተን ለመርዳት በሰማይ ውስጥ የሚጋልብ፣በግርማው በደመና ላይ የሚገሰግስ፣+እንደ እውነተኛው የየሹሩን+ አምላክ ያለ ማንም የለም።+ 27  አምላክ ከጥንት ጀምሮ መሸሸጊያ ነው፤+ዘላለማዊ ክንዶቹ ከበታችህ ናቸው።+ ጠላትን ከፊትህ ያባርራል፤+እንዲሁም ‘አጥፋቸው!’ ይላል።+ 28  እህልና አዲስ የወይን ጠጅ ባለበት ምድር፣+ሰማያቱ ጠል በሚያንጠባጥቡበት+እስራኤል ያለስጋት ይቀመጣል፤የያዕቆብም ምንጭ የተገለለ ይሆናል። 29  እስራኤል ሆይ፣ ደስተኛ ነህ!+ የይሖዋን ማዳን ያየ፣+እንደ አንተ ያለ ሕዝብ ማን አለ?+እሱ የሚከልል ጋሻህና+ታላቅ ሰይፍህ ነው፤ ጠላቶችህ በፊትህ ይንቀጠቀጣሉ፤+አንተም በጀርባቸው* ላይ ትራመዳለህ።”

የግርጌ ማስታወሻ

ወይም “በአሥር ሺዎች የሚቆጠሩ ቅዱሳን።”
“ቅን የሆነው” የሚል ትርጉም ያለው ሲሆን ለእስራኤል የተሰጠ የማዕረግ ስም ነው።
ወይም “ይታገላሉ።”
እዚህ ጥቅስ ላይ ያሉት “የአንተ” እና “ለአንተ” የሚሉት ቃላት አምላክን ያመለክታሉ።
ወይም “ወገባቸውን።”
“ከምሥራቅ ተራሮች” ማለትም ሊሆን ይችላል።
ወይም “ይወጋል።”
ወይም “የከበረ ሀብት።”
ወይም “ይታጠብ።”
ቃል በቃል “ብርታትህም እንደ ዘመንህ ይሆናል።”
“በከፍታ ቦታዎቻቸው” ማለትም ሊሆን ይችላል።