ዘፀአት 17:1-16

  • በኮሬብ ውኃ ባለማግኘታቸው አማረሩ (1-4)

  • ከዓለት ውኃ ፈለቀ (5-7)

  • ከአማሌቃውያን ጋር ተዋግተው አሸነፉ (8-16)

17  መላው የእስራኤል ማኅበረሰብም ከሲን ምድረ በዳ+ ተነስቶ ይሖዋ ባዘዘው መሠረት+ ከቦታ ወደ ቦታ ሲጓዝ ከቆየ በኋላ በረፊዲም+ ሰፈረ። ሆኖም ሕዝቡ የሚጠጣው ውኃ አልነበረም።  በመሆኑም ሕዝቡ “የሚጠጣ ውኃ ስጠን” በማለት ከሙሴ ጋር ይጣላ ጀመር።+ ሙሴ ግን “ከእኔ ጋር የምትጣሉት ለምንድን ነው? ይሖዋንስ ለምን ትፈታተኑታላችሁ?”+ አላቸው።  ሆኖም ሕዝቡ ውኃ በጣም ተጠምቶ ስለነበር “እኛና ልጆቻችን እንዲሁም ከብቶቻችን በውኃ ጥም እንድናልቅ ከግብፅ ያወጣኸን ለምንድን ነው?” በማለት በሙሴ ላይ ማጉረምረሙን ቀጠለ።+  በመጨረሻም ሙሴ “ይህን ሕዝብ ምን ባደርገው ይሻለኛል? ትንሽ ቆይተው እኮ ይወግሩኛል!” በማለት ወደ ይሖዋ ጮኸ።  ከዚያም ይሖዋ ሙሴን እንዲህ አለው፦ “ከእስራኤል ሽማግሌዎች መካከል የተወሰኑትን ምረጥና የአባይን ወንዝ የመታህበትን በትር+ ይዘህ ከሕዝቡ ፊት ፊት ሂድ። በትሩን በእጅህ ይዘህ ሂድ።  እኔም በዚያ በኮሬብ በሚገኘው ዓለት ላይ ፊትህ እቆማለሁ። አንተም ዓለቱን ትመታዋለህ፤ ውኃም ከውስጡ ይፈልቃል፤ ሕዝቡም ይጠጣሉ።”+ ሙሴም የእስራኤል ሽማግሌዎች እያዩ እንደተባለው አደረገ።  እሱም እስራኤላውያን ስለተጣሉትና “ለመሆኑ ይሖዋ በመካከላችን አለ ወይስ የለም?” በማለት ይሖዋን ስለተፈታተኑት+ የቦታውን ስም ማሳህ*+ እና መሪባ*+ አለው።  ከዚያም አማሌቃውያን+ መጥተው በረፊዲም እስራኤላውያንን ወጉ።+  በዚህ ጊዜ ሙሴ ኢያሱን+ እንዲህ አለው፦ “ሰዎች ምረጥልንና ከአማሌቃውያን ጋር ለመዋጋት ውጣ። እኔም በነገው ዕለት የእውነተኛውን አምላክ በትር በእጄ ይዤ በኮረብታው አናት ላይ እቆማለሁ።” 10  ከዚያም ኢያሱ ልክ ሙሴ እንዳለው አደረገ፤+ ከአማሌቃውያንም ጋር ተዋጋ። ሙሴ፣ አሮንና ሁርም+ ወደ ኮረብታው አናት ወጡ። 11  ሙሴ እጆቹን ወደ ላይ አንስቶ በሚቆይበት ጊዜ ሁሉ እስራኤላውያን ያይሉ፣ እጆቹን በሚያወርድበት ጊዜ ግን አማሌቃውያን ያይሉ ነበር። 12  የሙሴ እጆች በዛሉ ጊዜ ድንጋይ ወስደው ከሥሩ አስቀመጡለት፤ እሱም በድንጋዩ ላይ ተቀመጠ። ከዚያም አሮንና ሁር አንዱ በአንደኛው በኩል፣ ሌላው ደግሞ በሌላኛው በኩል ሆነው እጆቹን ደገፉለት፤ በመሆኑም ፀሐይ እስከምትጠልቅበት ጊዜ ድረስ እጆቹ ባሉበት ጸኑ። 13  በዚህ መንገድ ኢያሱ አማሌቅንና ሕዝቦቹን በሰይፍ ድል አደረገ።+ 14  ይሖዋም ሙሴን እንዲህ አለው፦ “መታሰቢያ* እንዲሆን ይህን በመጽሐፍ ጻፈው፤ ለኢያሱም ‘የአማሌቅን መታሰቢያ ከሰማይ በታች ሙሉ በሙሉ ጠራርጌ አጠፋለሁ’+ በማለት ይህን ደግመህ ንገረው።” 15  ከዚያም ሙሴ መሠዊያ ሠርቶ ስሙን ‘ይሖዋ ንሲ’* ብሎ ሰየመው፤ 16  እንዲህም ያለው “እጁ በያህ+ ዙፋን ላይ ስለተነሳ ይሖዋ ከአማሌቅ ጋር ከትውልድ እስከ ትውልድ ይዋጋል”+ በማለት ነው።

የግርጌ ማስታወሻ

“ፈተና፤ ፈታኝ ሁኔታ” የሚል ትርጉም አለው።
“ጠብ” የሚል ትርጉም አለው።
ወይም “ማስታወሻ።”
“ይሖዋ አርማዬ ነው” የሚል ትርጉም አለው።