ዘፀአት 2:1-25

  • ሙሴ ተወለደ (1-4)

  • የፈርዖን ሴት ልጅ ሙሴን አሳደገችው (5-10)

  • ሙሴ ወደ ምድያም ሸሸ፤ ሲፓራን አገባ (11-22)

  • አምላክ የእስራኤላውያንን ጩኸት ሰማ (23-25)

2  በዚያን ጊዜ ከሌዊ ነገድ የሆነ አንድ ሰው የሌዊን ልጅ አገባ።+  ሴቲቱም ፀንሳ ወንድ ልጅ ወለደች። ልጁም በጣም የሚያምር መሆኑን ስታይ ለሦስት ወር ደብቃ አቆየችው።+  ከዚያ በላይ ደብቃ ልታቆየው እንደማትችል+ ስታውቅ ግን የደንገል ቅርጫት* ወስዳ ቅርጫቱን በቅጥራንና በዝፍት ለቀለቀችው፤ ከዚያም ልጁን በቅርጫቱ ውስጥ አድርጋ በአባይ ወንዝ ዳር በሚገኘው ቄጠማ መሃል አስቀመጠችው።  እህቱ+ ግን የሕፃኑ መጨረሻ ምን እንደሚሆን ለማወቅ ራቅ ብላ ቆማ ሁኔታውን ትከታተል ነበር።  በዚህ ጊዜ የፈርዖን ሴት ልጅ ገላዋን ልትታጠብ ወደ አባይ ወረደች፤ ደንገጡሮቿም በአባይ ወንዝ ዳር ዳር ይሄዱ ነበር። እሷም በቄጠማው መሃል ቅርጫቱን አየች። ወዲያውኑም ቅርጫቱን እንድታመጣላት ባሪያዋን ላከቻት።+  ቅርጫቱንም ስትከፍት ሕፃኑን አየችው፤ ሕፃኑም እያለቀሰ ነበር። እሷም “ይህ ልጅ ከዕብራውያን ልጆች አንዱ ነው” አለች፤ ያም ሆኖ ለሕፃኑ አዘነችለት።  ከዚያም የሕፃኑ እህት የፈርዖንን ልጅ “ከዕብራውያን ሴቶች መካከል ልጁን እያጠባች የምታሳድግልሽ ሞግዚት ልጥራልሽ?” አለቻት።  የፈርዖንም ልጅ “አዎ፣ ሂጂ!” አለቻት። ልጅቷም ወዲያውኑ ሄዳ የሕፃኑን እናት+ ጠራቻት።  የፈርዖን ልጅም ሴትየዋን “ይህን ሕፃን ወስደሽ እያጠባሽ አሳድጊልኝ፤ እኔም እከፍልሻለሁ” አለቻት። በመሆኑም ሴትየዋ ልጁን ወስዳ እያጠባች ታሳድገው ጀመር። 10  ልጁም ባደገ ጊዜ አምጥታ ለፈርዖን ልጅ ሰጠቻት፤ እሱም ልጇ ሆነ።+ እሷም “ከውኃ ውስጥ አውጥቼዋለሁ” በማለት ስሙን ሙሴ* አለችው።+ 11  ሙሴ በጎለመሰ ጊዜ* ወንድሞቹ የተጫነባቸውን ሸክም+ ለማየት ወደ እነሱ ወጣ፤ ከዚያም ከወንድሞቹ አንዱ የሆነውን ዕብራዊ አንድ ግብፃዊ ሲደበድበው አየ። 12  በመሆኑም ወዲያና ወዲህ ተመልክቶ ማንም አለመኖሩን ካረጋገጠ በኋላ ግብፃዊውን ገድሎ አሸዋ ውስጥ ደበቀው።+ 13  ሆኖም በማግስቱ ሲወጣ ሁለት ዕብራውያን እርስ በርሳቸው ሲጣሉ ተመለከተ። እሱም ጥፋተኛውን “የገዛ ወገንህን የምትመታው ለምንድን ነው?” አለው።+ 14  በዚህ ጊዜ “አንተን በእኛ ላይ አለቃና ፈራጅ ማን አደረገህ? ግብፃዊውን እንደገደልከው እኔንም ልትገድለኝ ታስባለህ?” አለው።+ ሙሴም “ይህ ነገር ታውቋል ማለት ነው!” ብሎ በማሰብ ፈራ። 15  ከዚያም ፈርዖን ይህን ነገር ሰማ፤ ሙሴንም ሊገድለው ሞከረ፤ ይሁን እንጂ ሙሴ ከፈርዖን ሸሽቶ በምድያም+ ምድር ለመኖር ሄደ፤ እዚያም በአንድ የውኃ ጉድጓድ አጠገብ ተቀመጠ። 16  በምድያም የነበረው ካህን+ ሰባት ሴቶች ልጆች ነበሩት፤ እነሱም ውኃ ቀድተው ገንዳውን በመሙላት የአባታቸውን መንጋ ውኃ ለማጠጣት መጡ። 17  ሆኖም እንደወትሮው እረኞቹ መጥተው ሴቶቹን አባረሯቸው። በዚህ ጊዜ ሙሴ ተነስቶ ለሴቶቹ አገዘላቸው፤* መንጋቸውንም አጠጣላቸው። 18  ሴቶቹም ወደ ቤት፣ ወደ አባታቸው ወደ ረኡዔል*+ በተመለሱ ጊዜ አባታቸው “ዛሬ እንዴት ቶሎ መጣችሁ?” ሲል በመገረም ጠየቃቸው። 19  እነሱም “አንድ ግብፃዊ+ ከእረኞቹ እጅ አዳነን፤ እንዲያውም ውኃ ቀድቶ መንጋችንን አጠጣልን” አሉት። 20  እሱም ልጆቹን “ታዲያ ሰውየው የት አለ? ለምን ትታችሁት መጣችሁ? አብሮን ይበላ ዘንድ ጥሩት” አላቸው። 21  ከዚያ በኋላ ሙሴ ከሰውየው ጋር ለመኖር ተስማማ፤ ሰውየውም ልጁን ሲፓራን+ ለሙሴ ዳረለት። 22  እሷም ከጊዜ በኋላ ወንድ ልጅ ወለደች፤ ሙሴም “በባዕድ አገር የምኖር የባዕድ አገር ሰው ሆንኩ”+ በማለት ስሙን ጌርሳም*+ አለው። 23  ከረጅም ጊዜ* በኋላ የግብፁ ንጉሥ ሞተ፤+ እስራኤላውያን ግን ካሉበት የባርነት ሕይወት የተነሳ መቃተታቸውንና እሮሮ ማሰማታቸውን አላቆሙም ነበር፤ ከባርነት ሕይወታቸው የተነሳ እርዳታ ለማግኘት የሚያሰሙት ጩኸት ወደ እውነተኛው አምላክ ወጣ።+ 24  ከጊዜ በኋላም አምላክ በመቃተት የሚያሰሙትን ጩኸት አዳመጠ፤+ እንዲሁም ከአብርሃም፣ ከይስሐቅና ከያዕቆብ ጋር የገባውን ቃል ኪዳኑን አሰበ።+ 25  በመሆኑም አምላክ እስራኤላውያንን አየ፤ ያሉበትንም ሁኔታ ተመለከተ።

የግርጌ ማስታወሻ

ወይም “ሣጥን።”
“ከውኃ የወጣ” የሚል ትርጉም አለው፤ ይህም ከውኃ መዳንን ያመለክታል።
ወይም “ሙሴ በበረታ ጊዜ።”
ወይም “ተከላከለላቸው።”
ዮቶርን ያመለክታል።
“በዚያ የሚኖር የባዕድ አገር ሰው” የሚል ትርጉም አለው።
ቃል በቃል “ከብዙ ቀናት።”