ዘፀአት 28:1-43

  • የካህናቱ አልባሳት (1-5)

  • ኤፉዱ (6-14)

  • የደረት ኪሱ (15-30)

    • ኡሪሙና ቱሚሙ (30)

  • እጅጌ የሌለው ቀሚስ (31-35)

  • ጥምጥሙና በጥምጥሙ ላይ የሚደረገው ጠፍጣፋ ወርቅ (36-39)

  • ሌሎች የካህናት አልባሳት (40-43)

28  “አንተም ለእኔ ካህን ሆኖ እንዲያገለግለኝ+ ወንድምህን አሮንን ከወንዶች ልጆቹ ጋር ከእስራኤላውያን መካከል ለይተህ ትጠራዋለህ፤ አሮንን+ እንዲሁም የአሮንን ወንዶች ልጆች+ ናዳብን፣ አቢሁን፣+ አልዓዛርንና ኢታምርን+ ትጠራቸዋለህ።  ለወንድምህ ለአሮንም ክብርና ውበት የሚያጎናጽፉትን ቅዱስ ልብሶች ትሠራለታለህ።+  የጥበብ መንፈስ የሞላሁባቸውን ጥሩ ችሎታ* ያላቸውን ሰዎች+ ሁሉ አንተ ራስህ ታናግራቸዋለህ፤ እነሱም አሮን ለእኔ ካህን ሆኖ እንዲያገለግለኝ እሱን ለመቀደስ ልብሶቹን ይሠሩለታል።  “የሚሠሯቸው ልብሶችም እነዚህ ናቸው፦ የደረት ኪስ፣+ ኤፉድ፣+ እጅጌ የሌለው ቀሚስ፣+ በካሬ ንድፍ የተሸመነ ረጅም ቀሚስ፣ ጥምጥምና+ መቀነት፤+ ወንድምህ አሮንና ወንዶች ልጆቹ ካህን ሆነው እንዲያገለግሉኝ እነዚህን ቅዱስ ልብሶች ይሠሩላቸዋል።  እነዚህ የእጅ ጥበብ ባለሙያዎች ወርቁን፣ ሰማያዊውን ክር፣ ሐምራዊውን ሱፍ፣ ደማቁን ቀይ ማግና ጥሩውን በፍታ ተጠቅመው ይሠሯቸዋል።  “ከወርቅ፣ ከሰማያዊ ክር፣ ከሐምራዊ ሱፍ፣ ከደማቅ ቀይ ማግና በቀጭኑ ከተፈተለ ጥሩ በፍታ ኤፉዱን ያዘጋጃሉ፤ ኤፉዱም ጥልፍ የተጠለፈበት ይሁን።+  ኤፉዱ በሁለቱ የላይኛው ጫፎቹ ላይ የተያያዙ ሁለት የትከሻ ጥብጣቦች ይኖሩታል።  ኤፉዱ ወዲያ ወዲህ እንዳይንቀሳቀስ ለማሰር የሚያገለግለው ከኤፉዱ ጋር የተያያዘው በሽመና የተሠራው መቀነት+ ልክ እንደ ኤፉዱ ከወርቅ፣ ከሰማያዊ ክር፣ ከሐምራዊ ሱፍ፣ ከደማቅ ቀይ ማግና በቀጭኑ ከተፈተለ ጥሩ በፍታ የተሠራ መሆን ይኖርበታል።  “ሁለት የኦኒክስ ድንጋዮችን+ ወስደህ የእስራኤልን ወንዶች ልጆች ስሞች+ ትቀርጽባቸዋለህ፤ 10  በትውልዳቸው ቅደም ተከተል መሠረት የስድስቱን ስሞች በአንዱ ድንጋይ ላይ፣ የቀሩትን የስድስቱን ስሞች ደግሞ በሌላኛው ድንጋይ ላይ ትቀርጻለህ። 11  አንድ ቅርጽ አውጪ በድንጋይ ላይ ማኅተም እንደሚቀርጽ ሁሉ የእስራኤልን ወንዶች ልጆች ስሞች በሁለቱ ድንጋዮች ላይ ይቀርጽባቸዋል።+ ከዚያም በወርቅ አቃፊዎች ውስጥ እንዲቀመጡ ታደርጋለህ። 12  ለእስራኤል ልጆች እንደ መታሰቢያ ድንጋዮች ሆነው እንዲያገለግሉ ሁለቱን ድንጋዮች በኤፉዱ የትከሻ ጥብጣቦች ላይ ታስቀምጣቸዋለህ፤+ አሮንም እንደ መታሰቢያ ሆነው እንዲያገለግሉ ስሞቻቸውን በሁለቱ የትከሻ ጥብጣቦች ላይ በይሖዋ ፊት ይሸከማል። 13  አንተም የወርቅ አቃፊዎችን 14  እንዲሁም እንደ ገመድ የተገመዱ ሁለት ሰንሰለቶችን ከንጹሕ ወርቅ ትሠራለህ፤+ የተገመዱትንም ሰንሰለቶች ከአቃፊዎቹ ጋር አያይዛቸው።+ 15  “የፍርዱን የደረት ኪስ የጥልፍ ባለሙያ እንዲሠራው ታደርጋለህ።+ የደረት ኪሱ ልክ እንደ ኤፉዱ ከወርቅ፣ ከሰማያዊ ክር፣ ከሐምራዊ ሱፍ፣ ከደማቅ ቀይ ማግና በቀጭኑ ከተፈተለ ጥሩ በፍታ መሠራት ይኖርበታል።+ 16  ለሁለት በሚታጠፍበትም ጊዜ ቁመቱ አንድ ስንዝር፣* ወርዱ ደግሞ አንድ ስንዝር የሆነ ካሬ ይሁን። 17  የከበሩ ድንጋዮችን* በአራት ረድፍ በማቀፊያ ውስጥ ታደርግበታለህ። በመጀመሪያው ረድፍ ሩቢ፣ ቶጳዝዮንና መረግድ ይደርደር። 18  በሁለተኛው ረድፍ በሉር፣ ሰንፔርና ኢያስጲድ ይደርደር። 19  በሦስተኛው ረድፍ ለሼም፣ አካትምና አሜቴስጢኖስ ይደርደር። 20  በአራተኛውም ረድፍ ክርስቲሎቤ፣ ኦኒክስና ጄድ ይደርደር። በወርቅ አቃፊዎችም ውስጥ ይቀመጡ። 21  ድንጋዮቹም የእስራኤልን ወንዶች ልጆች ስሞች ማለትም 12ቱን በየስማቸው የሚወክሉ ይሆናሉ። ለ12ቱም ነገዶች ልክ ማኅተም በሚቀረጽበት መንገድ ለእያንዳንዳቸው በየስማቸው ይቀረጽላቸው። 22  “በደረት ኪሱም ላይ ከንጹሕ ወርቅ እንደተሠሩ ገመዶች የተጎነጎኑ ሰንሰለቶችን ትሠራለህ።+ 23  ለደረት ኪሱም ሁለት የወርቅ ቀለበቶችን ሠርተህ ሁለቱን ቀለበቶች ከሁለቱ የደረት ኪሱ ጫፎች ጋር ታያይዛቸዋለህ። 24  ሁለቱን የወርቅ ገመዶችም በደረት ኪሱ ዳርና ዳር ባሉት ጫፎች ላይ በሚገኙት በሁለቱ ቀለበቶች ውስጥ ታስገባቸዋለህ። 25  የሁለቱን ገመዶች ሁለት ጫፎች በሁለቱ አቃፊዎች ውስጥ ታስገባለህ፤ እነሱንም ከኤፉዱ የትከሻ ጥብጣቦች ጋር በፊት በኩል ታያይዛቸዋለህ። 26  ሁለት የወርቅ ቀለበቶችንም ሠርተህ በኤፉዱ በኩል በሚውለው በደረት ኪሱ ውስጠኛ ጠርዝ ላይ ባሉት ሁለት ጫፎች ላይ ታደርጋቸዋለህ።+ 27  ሁለት ተጨማሪ የወርቅ ቀለበቶችንም ሠርተህ በኤፉዱ በፊት በኩል ከሁለቱ የትከሻ ጥብጣቦች በታች ኤፉዱ በተጋጠመበት ቦታ አካባቢ፣ በሽመና ከተሠራው የኤፉዱ መቀነት በላይ አድርጋቸው።+ 28  የደረት ኪሱ ከቦታው እንዳይንቀሳቀስ የደረት ኪሱ ቀለበቶች ከኤፉዱ ቀለበቶች ጋር በሰማያዊ ገመድ መያያዝ ይኖርባቸዋል። ይህም የደረት ኪሱ ከመቀነቱ በላይ ከኤፉዱ ላይ ሳይንቀሳቀስ እንዲቀመጥ ያደርገዋል። 29  “አሮን ወደ ቅድስቱ በሚገባበት ጊዜ በይሖዋ ፊት ቋሚ መታሰቢያ እንዲሆን በልቡ ላይ በሚገኘው የፍርድ የደረት ኪስ የእስራኤልን ልጆች ስሞች ይሸከም። 30  ኡሪሙንና ቱሚሙን*+ በፍርድ የደረት ኪሱ ውስጥ ታስቀምጣቸዋለህ፤ አሮን በይሖዋ ፊት ለመቅረብ በሚገባበት ጊዜ በልቡ ላይ መሆን አለባቸው፤ አሮን በይሖዋ ፊት በሚቀርብበት ጊዜ ለእስራኤላውያን ፍርድ መስጫውን ዘወትር በልቡ ላይ ይሸከም። 31  “እጅጌ የሌለውን የኤፉዱን ቀሚስ ሙሉ በሙሉ ከሰማያዊ ክር ትሠራዋለህ።+ 32  ከላይ በኩል መሃል ላይ የአንገት ማስገቢያ ይኖረዋል። የአንገት ማስገቢያውም ዙሪያውን በሽመና ባለሙያ የተሠራ ቅምቅማት ይኑረው። የአንገት ማስገቢያውም እንዳይቀደድ እንደ ጥሩር አንገትጌ ሆኖ ይሠራ። 33  በታችኛው ጠርዝ ዙሪያ ከሰማያዊ ክር፣ ከሐምራዊ ሱፍና ከደማቅ ቀይ ማግ የተሠሩ ሮማኖችን አድርግ፤ በመሃል በመሃላቸውም የወርቅ ቃጭሎች አድርግ። 34  እጅጌ በሌለው ቀሚስ በታችኛው ጠርዝ ዙሪያ የወርቅ ቃጭል ከዚያም ሮማን፣ የወርቅ ቃጭል ከዚያም ሮማን እያፈራረቅክ አንጠልጥልበት። 35  አሮን በሚያገለግልበት ጊዜ ይህን ልብስ መልበስ አለበት፤ በይሖዋ ፊት ለመቅረብ ወደ መቅደሱ በሚገባበትና ከዚያ በሚወጣበት ጊዜ እንዳይሞት የቃጭሎቹ ድምፅ መሰማት አለበት።+ 36  “ከንጹሕ ወርቅም የሚያብረቀርቅ ጠፍጣፋ ወርቅ ሠርተህ ልክ ማኅተም በሚቀረጽበት መንገድ ‘ቅድስና የይሖዋ ነው’+ ብለህ ትቀርጽበታለህ። 37  እሱንም በሰማያዊ ገመድ በጥምጥሙ ላይ እሰረው፤+ በጥምጥሙ ላይ ከፊት በኩል ይሆናል። 38  በአሮን ግንባር ላይ ይሆናል፤ አሮንም አንድ ሰው ቅዱስ ከሆኑ ነገሮች ይኸውም እስራኤላውያን ቅዱስ ስጦታ አድርገው በሚያቀርቧቸው ጊዜ ከሚቀድሷቸው ነገሮች ጋር በተያያዘ ለሚፈጽመው ስህተት ተጠያቂ ይሆናል።+ በይሖዋም ፊት ተቀባይነት እንዲያገኙ ዘወትር በግንባሩ ላይ መሆን ይኖርበታል። 39  “ከጥሩ በፍታ ረጅም ቀሚስ በካሬ ንድፍ ትሸምንለታለህ፤ እንዲሁም ከጥሩ በፍታ ጥምጥም ትሠራለህ፤ በተጨማሪም በሽመና የተሠራ መቀነት ትሠራለህ።+ 40  “ለአሮን ወንዶች ልጆችም ክብርና ውበት የሚያጎናጽፏቸውን+ ረጃጅም ቀሚሶች፣ መቀነቶችና የራስ ቆቦች ትሠራላቸዋለህ።+ 41  ወንድምህን አሮንንና ወንዶች ልጆቹን ታለብሳቸዋለህ፤ እንዲሁም ትቀባቸዋለህ፣+ ትሾማቸዋለህ*+ ደግሞም ትቀድሳቸዋለህ፤ እነሱም ካህናት ሆነው ያገለግሉኛል። 42  እርቃናቸውን የሚሸፍኑበት የበፍታ ቁምጣም ትሠራላቸዋለህ።+ ቁምጣውም ከወገባቸው እስከ ጭናቸው የሚደርስ ይሆናል። 43  በደል እንዳይሆንባቸውና እንዳይሞቱ አሮንና ወንዶች ልጆቹ ወደ መገናኛ ድንኳኑ በሚገቡበት ጊዜ ወይም ቅዱስ በሆነው ስፍራ ለማገልገል ወደ መሠዊያው በሚቀርቡበት ጊዜ እነዚህን ልብሶች መልበስ አለባቸው። ይህ ለእሱም ሆነ ከእሱ በኋላ ለሚመጡት ዘሮቹ ዘላለማዊ ደንብ ነው።

የግርጌ ማስታወሻ

ቃል በቃል “ጥበበኛ ልብ።”
አንድ ስንዝር 22.2 ሴንቲ ሜትር ነው። ከተጨማሪው መረጃ ላይ ለ14ን ተመልከት።
ቃል በቃል “እጃቸውን ትሞላለህ።”