ዘፀአት 35:1-35

  • ሰንበትን አስመልክቶ የተሰጠ መመሪያ (1-3)

  • ለማደሪያ ድንኳኑ የሚሰጥ መዋጮ (4-29)

  • ባስልኤልና ኤልያብ በመንፈስ ተሞሉ (30-35)

35  በኋላም ሙሴ የእስራኤልን ማኅበረሰብ ሁሉ አንድ ላይ ሰብስቦ እንዲህ አላቸው፦ “ይሖዋ እንድትፈጽሟቸው ያዘዛችሁ ነገሮች እነዚህ ናቸው፦+  ስድስት ቀን ሥራ ይሠራል፤ ሰባተኛው ቀን ግን ለእናንተ የተቀደሰ ይሆናል፤ ለይሖዋም ሙሉ በሙሉ የሚታረፍበት ሰንበት ይሆናል።+ በዚህ ቀን ሥራ የሚሠራ ማንም ሰው ይገደላል።+  በምትኖሩበት በየትኛውም ቦታ በሰንበት ቀን እሳት አታቀጣጥሉ።”  ከዚያም ሙሴ ለእስራኤል ማኅበረሰብ ሁሉ እንዲህ አለ፦ “ይሖዋ እንዲህ ሲል አዟል፦  ‘ካላችሁ ነገር ለይሖዋ መዋጮ አምጡ።+ ልቡ ያነሳሳው+ ማንኛውም ሰው የሚከተሉትን ነገሮች ለይሖዋ መዋጮ አድርጎ ያምጣ፦ ወርቅ፣ ብር፣ መዳብ፣  ሰማያዊ ክር፣ ሐምራዊ ሱፍ፣ ደማቅ ቀይ ማግ፣ ጥሩ በፍታ፣ የፍየል ፀጉር፣+  ቀይ ቀለም የተነከረ የአውራ በግ ቆዳ፣ የአቆስጣ ቆዳ፣ የግራር እንጨት፣  ለመብራት የሚሆን ዘይት፣ ለቅብዓት ዘይትና ጥሩ መዓዛ ላለው ዕጣን የሚሆን የበለሳን ዘይት፣+  በኤፉዱና በደረት ኪሱ+ ላይ የሚቀመጡ የኦኒክስ ድንጋዮችና+ ሌሎች ድንጋዮች። 10  “‘በመካከላችሁ ያሉ ጥሩ ችሎታ* ያላቸው+ ሰዎች ሁሉ መጥተው ይሖዋ ያዘዘውን ነገር ሁሉ ይሥሩ፤ 11  እነዚህም የማደሪያ ድንኳኑ ከተለያየ ቁሳቁሱና ከመደረቢያው ጋር፣ ማያያዣዎቹ፣ አራት ማዕዘን ቋሚዎቹ፣ አግዳሚ እንጨቶቹ፣ ዓምዶቹ፣ መሰኪያዎቹ፣ 12  ታቦቱና+ መሎጊያዎቹ፣+ መክደኛው፣+ ለመከለያ የሚሆነው መጋረጃ፣+ 13  ጠረጴዛው+ እንዲሁም መሎጊያዎቹና ዕቃዎቹ በሙሉ፣ ገጸ ኅብስቱ፣+ 14  የመብራት መቅረዙና+ ዕቃዎቹ፣ መብራቶቹ፣ ለመብራቱ የሚሆነው ዘይት፣+ 15  የዕጣን መሠዊያውና+ መሎጊያዎቹ፣ የቅብዓት ዘይቱና ጥሩ መዓዛ ያለው ዕጣን፣+ ለማደሪያ ድንኳኑ መግቢያ የሚሆነው መከለያ፣* 16  የሚቃጠል መባ የሚቀርብበት መሠዊያ+ እንዲሁም የመዳብ ፍርግርጉ፣ መሎጊያዎቹና ዕቃዎቹ በሙሉ፣ ገንዳውና ማስቀመጫው፣+ 17  የግቢው መጋረጃ+ እንዲሁም ቋሚዎቹና መሰኪያዎቹ፣ ለግቢው መግቢያ የሚሆነው መከለያ፣* 18  የማደሪያ ድንኳኑ ካስማዎችና የግቢው ካስማዎች እንዲሁም ገመዶቻቸው፣+ 19  በመቅደሱ ለማገልገል የሚለበሱት በጥሩ ሁኔታ የተሸመኑት ልብሶች፣+ የካህኑ የአሮን ቅዱስ ልብሶች+ እንዲሁም ወንዶች ልጆቹ ካህናት ሆነው ሲያገለግሉ የሚለብሷቸው ልብሶች ናቸው።’” 20  ከዚያም የእስራኤል ማኅበረሰብ በሙሉ ከሙሴ ፊት ሄደ። 21  ከዚያም ልባቸው የገፋፋቸውና+ መንፈሳቸው ያነሳሳቸው ሁሉ መጥተው ለመገናኛ ድንኳኑ ሥራና በዚያ ለሚከናወነው ማንኛውም አገልግሎት እንዲሁም ለቅዱሶቹ ልብሶች እንዲሆን መዋጮአቸውን ለይሖዋ አመጡ። 22  ፈቃደኛ ልብ ያላቸው ሁሉ፣ ወንዶችም ሆኑ ሴቶች የደረት ጌጥ፣ የጆሮ ጌጥ፣ ቀለበትና ሌላ ጌጣጌጥ እንዲሁም ሁሉንም ዓይነት ከወርቅ የተሠራ ጌጣጌጥ ይዘው ይመጡ ነበር። ሁሉም የወርቅ መባዎቻቸውን* ለይሖዋ አቀረቡ።+ 23  ደግሞም ሰማያዊ ክር፣ ሐምራዊ ሱፍ፣ ደማቅ ቀይ ማግ፣ ጥሩ በፍታ፣ የፍየል ፀጉር፣ ቀይ ቀለም የተነከረ የአውራ በግ ቆዳ እንዲሁም የአቆስጣ ቆዳ ያላቸው ሁሉ እነዚህን አመጡ። 24  ብርና መዳብ የሚያዋጡ ሁሉ ለይሖዋ የሚሆነውን መዋጮ አመጡ፤ ለመገናኛው ድንኳን ሥራ የሚውል የግራር እንጨት ያላቸውም ሁሉ ይህን አመጡ። 25  ጥሩ ችሎታ ያላቸው ሴቶችም+ ሁሉ በእጃቸው ይፈትሉ ነበር፤ እነሱም የሚከተሉትን ነገሮች ፈትለው አመጡ፦ ሰማያዊ ክር፣ ሐምራዊ ሱፍ፣ ደማቅ ቀይ ማግ እንዲሁም ጥሩ በፍታ። 26  ጥሩ ችሎታ ያላቸው ልባቸው ያነሳሳቸው ሴቶች ሁሉ የፍየል ፀጉሩን ይፈትሉ ነበር። 27  አለቆቹም በኤፉዱና በደረት ኪሱ+ ላይ የሚቀመጡ የኦኒክስ ድንጋዮችንና ሌሎች ድንጋዮችን፣ 28  የበለሳን ዘይቱን እንዲሁም ለመብራት፣ ለቅብዓት ዘይቱና+ ጥሩ መዓዛ ላለው ዕጣን+ የሚሆነውን ዘይት አመጡ። 29  ልባቸው ያነሳሳቸው ወንዶችና ሴቶች በሙሉ ይሖዋ በሙሴ አማካኝነት እንዲከናወን ላዘዘው ሥራ የሚውሉ ነገሮችን አመጡ፤ እስራኤላውያኑ ይህን በፈቃደኝነት የሚቀርብ መባ አድርገው ለይሖዋ አመጡ።+ 30  ከዚያም ሙሴ እስራኤላውያንን እንዲህ አላቸው፦ “እንደምታዩት ይሖዋ ከይሁዳ ነገድ የሆነው የሁር ልጅ ዖሪ+ የወለደውን ባስልኤልን መርጦታል። 31  ደግሞም በማንኛውም ዓይነት የእጅ ሙያ ማስተዋል፣ ጥበብና እውቀት በመስጠት በአምላክ መንፈስ ሞልቶታል። 32  ይኸውም የተለያዩ ንድፎችን እንዲያወጣ እንዲሁም በወርቅ፣ በብርና በመዳብ የተለያዩ ነገሮችን እንዲሠራ፣ 33  ፈርጥ የሚሆኑትን ድንጋዮች እንዲቀርጽና በቦታቸው እንዲያስቀምጥ እንዲሁም ድንቅ የሆኑ ልዩ ልዩ የእንጨት ቁሳቁሶችን እንዲሠራ ነው። 34  አምላክም ለእሱና ከዳን ነገድ ለሆነው ለአሂሳማክ ልጅ ለኤልያብ+ ሌሎችን የማስተማር ችሎታ ሰጥቷቸዋል። 35  የእጅ ጥበብ ባለሙያ፣ የጥልፍ ባለሙያ እንዲሁም በሰማያዊ ክር፣ በሐምራዊ ሱፍ፣ በደማቅ ቀይ ማግና በጥሩ በፍታ የሚሸምን የጥበብ ባለሙያ ብሎም የሽመና ባለሙያ የሚያከናውኗቸውን ሥራዎች በሙሉ እንዲሠሩ ጥሩ ችሎታ* ሰጥቷቸዋል።+ እነዚህ ሰዎች ሁሉንም ዓይነት ሥራዎች የሚሠሩና ሁሉንም ዓይነት ንድፎች የሚያወጡ ነበሩ።

የግርጌ ማስታወሻ

ቃል በቃል “ጥበበኛ ልብ።”
ወይም “መጋረጃ።”
ወይም “መጋረጃ።”
ወይም “የሚወዘወዙ መባዎቻቸውን።”
ቃል በቃል “ጥበበኛ ልብ።”