ዘፀአት 5:1-23

  • ሙሴና አሮን ፈርዖን ፊት ቀረቡ (1-5)

  • እስራኤላውያን የሚደርስባቸው ጭቆና እየባሰ ሄደ (6-18)

  • እስራኤላውያን ሙሴንና አሮንን አማረሩ (19-23)

5  ከዚያ በኋላ ሙሴና አሮን ወደ ፈርዖን ገብተው እንዲህ አሉት፦ “የእስራኤል አምላክ ይሖዋ ‘በምድረ በዳ በዓል እንዲያከብርልኝ ሕዝቤን ልቀቅ’ ይላል።”  ፈርዖን ግን እንዲህ አለ፦ “የእሱን ቃል ሰምቼ እስራኤልን የምለቀው ለመሆኑ ይሖዋ ማነው?+ እኔ ይሖዋ የምትሉትን ፈጽሞ አላውቅም፤ እስራኤልንም አለቅም።”+  ሆኖም እነሱ እንዲህ አሉት፦ “የዕብራውያን አምላክ አነጋግሮን ነበር። በመሆኑም እባክህ የሦስት ቀን መንገድ ወደ ምድረ በዳ ተጉዘን ለአምላካችን ለይሖዋ መሥዋዕት ማቅረብ እንፈልጋለን፤+ ካልሆነ ግን በበሽታ ወይም በሰይፍ ይጨርሰናል።”  የግብፅም ንጉሥ “ሙሴና አሮን፣ ሕዝቡን ሥራ የምታስፈቱት ለምንድን ነው? አርፋችሁ ወደ ጉልበት ሥራችሁ ተመለሱ!” አላቸው።+  ፈርዖንም በመቀጠል “የምድሩ ሕዝብ ምን ያህል ብዙ እንደሆነ ተመልከት፤ አንተ ደግሞ ሥራ ልታስፈታቸው ነው” አለ።  ፈርዖንም በዚያኑ ዕለት የሥራ ኃላፊዎቹንና አሠሪዎቹን እንዲህ ሲል አዘዛቸው፦  “ከአሁን በኋላ ለጡብ መሥሪያ የሚሆን ጭድ ለሕዝቡ እንዳትሰጡ።+ ራሳቸው ሄደው ጭድ ይሰብስቡ።  ሆኖም በፊት ይሠሩት የነበረውን ያህል ጡብ ሠርተው እንዲያስረክቡ አድርጉ። ዘና እያሉ ስለሆነ* ማስረከብ ከሚጠበቅባቸው ጡብ ምንም እንዳትቀንሱላቸው። ‘መሄድ እንፈልጋለን፤ ሄደን ለአምላካችን መሥዋዕት ማቅረብ እንፈልጋለን!’ እያሉ የሚጮኹት ለዚህ ነው።  ለሐሰት ወሬ ጆሯቸውን እንዳይሰጡ ሥራውን አክብዱባቸው፤ እንዲሁም ፋታ አሳጧቸው።” 10  ስለዚህ የሥራ ኃላፊዎቹና+ አሠሪዎቹ ወጥተው ለሕዝቡ እንዲህ አሉ፦ “ፈርዖን እንዲህ ይላል፦ ‘ከእንግዲህ ጭድ አላቀርብላችሁም። 11  ራሳችሁ ሄዳችሁ ከየትም ፈልጋችሁ ጭድ አምጡ፤ ሥራችሁ ግን በምንም ዓይነት አይቀነስም።’” 12  ከዚያም ሕዝቡ እንደ ጭድ ሆኖ የሚያገለግለውን የእህል ቆረን* ለመሰብሰብ በመላው የግብፅ ምድር ተሰማራ። 13  የሥራ ኃላፊዎቹም “እያንዳንዳችሁ ጭድ ይቀርብላችሁ በነበረበት ጊዜ ታደርጉት እንደነበረው ሁሉ አሁንም በየዕለቱ የሚጠበቅባችሁን ሥራ ሠርታችሁ ማጠናቀቅ አለባችሁ” እያሉ ያስገድዷቸው ነበር። 14  በተጨማሪም የፈርዖን የሥራ ኃላፊዎች የሾሟቸው የእስራኤላውያን አሠሪዎች ተገረፉ።+ እነሱንም “ቀደም ሲል ሠርታችሁ ታስረክቡት የነበረውን ያህል ጡብ ሠርታችሁ ያላስረከባችሁት ለምንድን ነው? ትናንትም ሆነ ዛሬ እንዲህ አላደረጋችሁም” ብለው ጠየቋቸው። 15  በመሆኑም የእስራኤላውያን አሠሪዎች ወደ ፈርዖን ገብተው እንዲህ በማለት እሮሯቸውን አሰሙ፦ “በአገልጋዮችህ ላይ እንዲህ ያለ ድርጊት የምትፈጽመው ለምንድን ነው? 16  ለእኛ ለአገልጋዮችህ ምንም ጭድ አይሰጠንም፤ እነሱ ግን ‘ጡብ ሥሩ!’ ይሉናል። ጥፋቱ የገዛ ሰዎችህ ሆኖ ሳለ እኛ አገልጋዮችህ እንገረፋለን።” 17  እሱ ግን እንዲህ አላቸው፦ “እናንተ እኮ ተዝናንታችኋል፤* አዎ፣ ዘና እያላችሁ ነው!*+ ‘መሄድ እንፈልጋለን፤ ሄደን ለይሖዋ መሥዋዕት ማቅረብ እንፈልጋለን!’ የምትሉት ለዚህ ነው።+ 18  በሉ አሁን ወደ ሥራችሁ ተመለሱ! ምንም ጭድ አይቀርብላችሁም፤ ሆኖም የሚጠበቅባችሁን ያህል ጡብ መሥራት አለባችሁ።” 19  የእስራኤል አሠሪዎችም “በየዕለቱ ማስረከብ ከሚጠበቅባችሁ ጡብ ምንም ማጉደል የለባችሁም” የሚለውን ትእዛዝ ሲሰሙ ከባድ ችግር ውስጥ መውደቃቸውን ተረዱ። 20  እነሱም ፈርዖንን አነጋግረው ሲወጡ በዚያ ቆመው ይጠብቋቸው የነበሩትን ሙሴንና አሮንን አገኟቸው። 21  እነሱም እንዲህ አሏቸው፦ “በፈርዖንና በአገልጋዮቹ ፊት እንድንጠላ ስላደረጋችሁና* እንዲገድሉን በእጃቸው ሰይፍ ስለሰጣችኋቸው ይሖዋ ይይላችሁ፤ ደግሞም ይፍረድባችሁ።”+ 22  በዚህ ጊዜ ሙሴ ወደ ይሖዋ ተመልሶ እንዲህ አለው፦ “ይሖዋ ሆይ፣ ይህን ሕዝብ ለመከራ የዳረግከው ለምንድን ነው? እኔንስ የላክኸኝ ለምንድን ነው? 23  ፈርዖን በስምህ ለመናገር ወደ እሱ ከገባሁበት+ ጊዜ አንስቶ ይህን ሕዝብ ይበልጥ ማንገላታቱን ቀጥሏል፤+ አንተም ብትሆን ሕዝብህን አላዳንክም።”+

የግርጌ ማስታወሻ

ወይም “ሰነፎች ስለሆኑ።”
ጤፍ ወይም ስንዴ ከታጨደ በኋላ ማሳው ላይ የሚቀር አገዳ።
ወይም “ሰነፎች ናችሁ።”
ወይም “ሰነፎች ናችሁ።”
ወይም “በፈርዖንና በአገልጋዮቹ ፊት እንደ ግም ስላስቆጠራችሁንና።”