ዘፀአት 7:1-25

  • ይሖዋ ሙሴን አበረታታው (1-7)

  • የአሮን በትር ትልቅ እባብ ሆነ (8-13)

  • የመጀመሪያው መቅሰፍት፦ ውኃው ወደ ደም ተለወጠ (14-25)

7  ይሖዋም ሙሴን እንዲህ አለው፦ “እንግዲህ አንተን ለፈርዖን እንደ አምላክ አድርጌሃለሁ፤* የገዛ ወንድምህ አሮን ደግሞ የአንተ ነቢይ ይሆናል።+  አንተም የማዝህን ሁሉ ደግመህ ትናገራለህ፤ ወንድምህ አሮንም ለፈርዖን ይነግረዋል፤ እሱም እስራኤላውያንን ከምድሩ እንዲወጡ ይለቃቸዋል።  እኔ ደግሞ የፈርዖን ልብ እንዲደነድን እፈቅዳለሁ፤+ በግብፅ ምድርም ምልክቶቼንና ተአምራቴን አበዛለሁ።+  ፈርዖን ግን አይሰማችሁም፤ እኔም በግብፅ ምድር ላይ እጄን አሳርፋለሁ፤ ሠራዊቴን ይኸውም ሕዝቤ የሆኑትን እስራኤላውያንን በታላቅ ፍርድ ከግብፅ ምድር አወጣቸዋለሁ።+  በግብፅ ላይ እጄን ስዘረጋና እስራኤላውያንን ከመካከላቸው ሳወጣ ግብፃውያን እኔ ይሖዋ መሆኔን በእርግጥ ያውቃሉ።”+  ሙሴና አሮን ይሖዋ እንዳዘዛቸው አደረጉ፤ ልክ እንደተባሉት አደረጉ።  ከፈርዖን ጋር በተነጋገሩበት ጊዜ ሙሴ የ80 ዓመት ሰው፣ አሮን ደግሞ የ83 ዓመት ሰው ነበር።+  በዚህ ጊዜ ይሖዋ ሙሴንና አሮንን እንዲህ አላቸው፦  “ምናልባት ፈርዖን ‘እስቲ ተአምር አሳዩ’ ቢላችሁ አሮንን ‘በትርህን ወስደህ በፈርዖን ፊት ጣለው’ በለው። በትሩም ትልቅ እባብ ይሆናል።”+ 10  ስለሆነም ሙሴና አሮን ወደ ፈርዖን ገብተው ልክ ይሖዋ እንዳዘዛቸው አደረጉ። አሮንም በትሩን በፈርዖንና በአገልጋዮቹ ፊት ጣለው፤ በትሩም ትልቅ እባብ ሆነ። 11  ይሁንና ፈርዖን ጠቢባኑንና መተተኞቹን ጠራ፤ አስማት የሚሠሩ የግብፅ ካህናትም+ በአስማታቸው* ተመሳሳይ ነገር አደረጉ።+ 12  እያንዳንዳቸውም በትራቸውን ጣሉ፤ በትሮቹም ትላልቅ እባቦች ሆኑ፤ ይሁን እንጂ የአሮን በትር የእነሱን በትሮች ዋጠ። 13  ያም ሆኖ የፈርዖን ልብ ደነደነ፤+ ልክ ይሖዋ እንዳለውም ያሉትን ነገር አልሰማቸውም። 14  ከዚያም ይሖዋ ሙሴን እንዲህ አለው፦ “የፈርዖን ልብ ደንድኗል።+ እሱም ሕዝቡን ለመልቀቅ እንቢተኛ ሆኗል። 15  በማለዳ ወደ ፈርዖን ሂድ። እሱም ወደ ውኃው ይወርዳል! አንተም እሱን ለማግኘት በአባይ ወንዝ ዳር ቁም፤ ወደ እባብ ተለውጦ የነበረውንም በትር በእጅህ ያዝ።+ 16  እንዲህም በለው፦ ‘የዕብራውያን አምላክ ይሖዋ ወደ አንተ ልኮኛል፤+ እሱም “በምድረ በዳ እንዲያገለግለኝ ሕዝቤን ልቀቅ” ብሎሃል፤ ይኸው አንተ ግን እስካሁን ድረስ አልታዘዝክም። 17  እንግዲህ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ “እኔ ይሖዋ እንደሆንኩ በዚህ ታውቃለህ።+ ይኸው በበትሬ በአባይ ወንዝ ውስጥ ያለውን ውኃ እመታለሁ፤ ውኃውም ወደ ደም ይለወጣል። 18  በአባይ ውስጥ ያሉት ዓሣዎች ይሞታሉ፤ አባይም ይከረፋል፤ ግብፃውያንም ከአባይ ወንዝ ውኃ መጠጣት አይችሉም።”’” 19  ከዚያም ይሖዋ ሙሴን እንዲህ አለው፦ “አሮንን እንዲህ በለው፦ ‘የግብፅ ውኃዎች ይኸውም ወንዞቿ፣ የመስኖ ቦዮቿ፣* ረግረጋማ ቦታዎቿና+ የተጠራቀሙት ውኃዎቿ ሁሉ ወደ ደም እንዲለወጡ በትርህን ወስደህ በእነሱ ላይ እጅህን ዘርጋ።’+ በመላው የግብፅ ምድር ላይ ሌላው ቀርቶ ከእንጨትና ከድንጋይ በተሠሩ ዕቃዎች ውስጥ ደም ይሆናል።” 20  ሙሴና አሮን ወዲያውኑ ልክ ይሖዋ እንዳዘዛቸው አደረጉ። እሱም ፈርዖንና አገልጋዮቹ እያዩ በትሩን አንስቶ በአባይ ወንዝ ውስጥ ያለውን ውኃ መታ፤ በወንዙ ውስጥ የነበረውም ውኃ በሙሉ ወደ ደም ተለወጠ።+ 21  በወንዙ ውስጥ የነበሩት ዓሣዎች ሞቱ፤+ ወንዙም መከርፋት ጀመረ፤ ግብፃውያንም ከአባይ ወንዝ ውኃ መጠጣት አልቻሉም፤+ በመላው የግብፅ ምድር ላይም ደም ነበር። 22  ይሁንና አስማት የሚሠሩ የግብፅ ካህናትም በሚስጥራዊ ጥበባቸው ተመሳሳይ ነገር አደረጉ፤+ በመሆኑም የፈርዖን ልብ ደነደነ፤ ልክ ይሖዋ እንዳለውም እነሱን ለመስማት እንቢተኛ ሆነ።+ 23  ከዚያም ፈርዖን ተመልሶ ወደ ቤቱ ሄደ፤ ይህን ከቁም ነገር አልቆጠረውም። 24  ግብፃውያን ሁሉ ከአባይ ወንዝ ውኃ መጠጣት ስላልቻሉ የሚጠጣ ውኃ ለማግኘት የአባይን ዳርቻ ተከትለው ጉድጓዶችን ይቆፍሩ ነበር። 25  ይሖዋ አባይን ከመታ ሰባት ቀን አለፈ።

የግርጌ ማስታወሻ

ቃል በቃል “አምላክ አድርጌሃለሁ።”
ወይም “በአስማታዊ ጥበባቸው።”
ከአባይ ወንዝ የሚወጡ ቦዮችን ያመለክታል።