ዘፍጥረት 13:1-18

  • አብራም ወደ ከነአን ተመለሰ (1-4)

  • አብራምና ሎጥ ተለያዩ (5-13)

  • አምላክ ለአብራም በድጋሚ ተስፋ ሰጠው (14-18)

13  ከዚያም አብራም ሚስቱንና ያለውን ንብረት ሁሉ ይዞ ከሎጥ ጋር በመሆን ከግብፅ ወጥቶ ወደ ኔጌብ ሄደ።+  አብራም በከብት፣ በብርና በወርቅ እጅግ በልጽጎ ነበር።+  እሱም ከኔጌብ ተነስቶ ወደ ቤቴል በሚጓዝበት ጊዜ ድንኳኑን ተክሎበት ወደነበረው በቤቴልና በጋይ+ መካከል ወደሚገኘው ስፍራ እስኪደርስ ድረስ በየቦታው ይሰፍር ነበር፤  ይህም ቀደም ሲል መሠዊያ ሠርቶበት የነበረው ስፍራ ነው። በዚያም አብራም የይሖዋን ስም ጠራ።  ከአብራም ጋር ይጓዝ የነበረው ሎጥም በጎች፣ ከብቶችና ድንኳኖች ነበሩት።  በመሆኑም ሁሉም አንድ ላይ ለመኖር ምድሪቱ አልበቃቻቸውም፤ ንብረታቸው በጣም እየበዛ ስለመጣ አብረው መኖር አልቻሉም።  በዚህም ምክንያት በአብራም እረኞችና በሎጥ እረኞች መካከል ጠብ ተነሳ። (በወቅቱ ከነአናውያንና ፈሪዛውያን በምድሪቱ ይኖሩ ነበር።)+  ስለዚህ አብራም ሎጥን+ እንዲህ አለው፦ “እባክህ በእኔና በአንተ እንዲሁም በእኔ እረኞችና በአንተ እረኞች መካከል ምንም ዓይነት ጠብ አይኑር፤ እኛ እኮ ወንድማማቾች ነን።  ምድሪቱ ሁሉ በእጅህ አይደለችም? እባክህ ከእኔ ተለይ። አንተ ወደ ግራ ብትሄድ እኔ ወደ ቀኝ እሄዳለሁ፤ አንተ ወደ ቀኝ ብትሄድ ደግሞ እኔ ወደ ግራ እሄዳለሁ።” 10  ሎጥም ዓይኑን አቅንቶ መላውን የዮርዳኖስ አውራጃ እስከ ዞአር+ ድረስ ተመለከተ፤+ (ይሖዋ ሰዶምንና ገሞራን ከማጥፋቱ በፊት) አካባቢው ልክ እንደ ይሖዋ የአትክልት ስፍራ፣+ ልክ እንደ ግብፅ ምድር ውኃ የጠገበ ነበር። 11  ከዚያም ሎጥ መላውን የዮርዳኖስ አውራጃ ለራሱ መረጠ፤ ሎጥም ወደ ምሥራቅ ሄዶ ሰፈረ። በዚህ መንገድ አንዳቸው ከሌላው ተለዩ። 12  አብራም በከነአን ምድር ኖረ፤ ሎጥ ግን በአውራጃው በሚገኙ ከተሞች አቅራቢያ ኖረ።+ በመጨረሻም በሰዶም አቅራቢያ ድንኳን ተከለ። 13  የሰዶም ሰዎች በይሖዋ ፊት ከባድ ኃጢአት የሚፈጽሙ ክፉ ሰዎች ነበሩ።+ 14  ሎጥ ከአብራም ከተለየ በኋላ ይሖዋ አብራምን እንዲህ አለው፦ “እባክህ ካለህበት ቦታ ሆነህ ዓይንህን አቅንተህ ወደ ሰሜን፣ ወደ ደቡብ፣ ወደ ምሥራቅና ወደ ምዕራብ ተመልከት፤ 15  ምክንያቱም የምታየውን ምድር ሁሉ ለአንተና ለዘርህ ለዘለቄታው ርስት አድርጌ እሰጣለሁ።+ 16  ዘርህን እንደ ምድር አፈር አበዛዋለሁ፤ ማንም ሰው የምድርን አፈር መቁጠር ከቻለ የአንተም ዘር ሊቆጠር ይችላል።+ 17  ተነሳ፣ ይህችን ምድር ልሰጥህ ስለሆነ በምድሪቱ ስፋትና ርዝመት ሂድ።” 18  በመሆኑም አብራም ሄደ፤ በድንኳን መኖሩንም ቀጠለ። ከጊዜ በኋላም በኬብሮን+ ወደሚገኙት የማምሬ+ ትላልቅ ዛፎች መጥቶ መኖር ጀመረ፤ በዚያም ለይሖዋ መሠዊያ ሠራ።+

የግርጌ ማስታወሻ