ዘፍጥረት 50:1-26

  • ዮሴፍ ያዕቆብን በከነአን ቀበረው (1-14)

  • ዮሴፍ ወንድሞቹን ይቅር እንዳላቸው በድጋሚ አረጋገጠላቸው (15-21)

  • ዮሴፍ የሚሞትበት ጊዜ ቀረበ (22-26)

    • ዮሴፍ አፅሙን አስመልክቶ የሰጠው ትእዛዝ (25)

50  ከዚያም ዮሴፍ አባቱ ላይ ተደፍቶ አለቀሰ፤+ አባቱንም ሳመው።  በኋላም ዮሴፍ መድኃኒት ቀማሚ የሆኑ አገልጋዮቹን የአባቱን አስከሬን መድኃኒት እንዲቀቡ+ አዘዛቸው። መድኃኒት ቀማሚዎቹም እስራኤልን መድኃኒት ቀቡት፤  ይህም 40 ቀን ሙሉ ፈጀባቸው፤ ምክንያቱም አስከሬን መድኃኒት መቀባት ይህን ያህል ጊዜ ይወስድ ነበር፤ ግብፃውያንም 70 ቀን አለቀሱለት።  የሐዘኑም ጊዜ ሲያበቃ ዮሴፍ የፈርዖንን ቤተ መንግሥት ባለሥልጣናት* እንዲህ አላቸው፦ “በፊታችሁ ሞገስ አግኝቼ ከሆነ እባካችሁ ለፈርዖን ይህን መልእክት ንገሩልኝ፦  ‘አባቴ “እንግዲህ እኔ የምሞትበት ጊዜ ቀርቧል።+ በመሆኑም በከነአን ምድር ባዘጋጀሁት+ የመቃብር ስፍራ ቅበረኝ”+ ሲል አስምሎኛል።+ ስለዚህ እባክህ ልውጣና አባቴን ልቅበር፤ ከዚያም እመለሳለሁ።’”  ፈርዖንም “እንግዲህ ባስማለህ መሠረት+ ሄደህ አባትህን ቅበር” አለው።  በመሆኑም ዮሴፍ አባቱን ለመቅበር ወጣ፤ ከእሱም ጋር የፈርዖን አገልጋዮች በሙሉ ሄዱ፤ በቤተ መንግሥቱም ያሉ ሽማግሌዎች፣+ በግብፅ ምድር የሚገኙ ሽማግሌዎች በሙሉ፣  በዮሴፍ ቤት ያሉ ሁሉ፣ ወንድሞቹና የአባቱ ቤተሰቦች ሄዱ።+ በጎሸን ምድር የቀሩት ትናንሽ ልጆቻቸው፣ መንጎቻቸውና ከብቶቻቸው ብቻ ነበሩ።  ሠረገሎችና+ ፈረሰኞችም አብረውት ወጡ፤ ያጀበውም ሰው እጅግ ብዙ ነበር። 10  ከዚያም በዮርዳኖስ ክልል ወደሚገኘው አጣድ የተባለ አውድማ ደረሱ፤ በዚያም እየጮኹ ምርር ብለው አለቀሱ፤ እሱም ለአባቱ ሰባት ቀን ለቅሶ ተቀመጠ። 11  በዚያ የሚኖሩ ከነአናውያንም ሰዎቹ በአጣድ አውድማ ሲያለቅሱ ሲመለከቱ “መቼም ይህ ለግብፃውያን ከባድ ሐዘን መሆን አለበት!” አሉ። በዮርዳኖስ ክልል የሚገኘው የዚህ ስፍራ ስም አቤልምጽራይም* የተባለው በዚህ የተነሳ ነው። 12  በመሆኑም ልጆቹ ልክ በሰጣቸው መመሪያ መሠረት አደረጉለት።+ 13  ወንዶች ልጆቹም ወደ ከነአን ምድር ወስደው አብርሃም ለመቃብር ቦታ ብሎ ከሂታዊው ከኤፍሮን በገዛው ከማምሬ ፊት ለፊት በሚገኘው እርሻ ማለትም በማክፈላ እርሻ ውስጥ ባለው ዋሻ ቀበሩት።+ 14  ዮሴፍም አባቱን ከቀበረ በኋላ ከወንድሞቹና ለአባቱ ቀብር አብረውት ከሄዱት ሁሉ ጋር ወደ ግብፅ ተመለሰ። 15  የዮሴፍ ወንድሞች አባታቸው መሞቱን ባዩ ጊዜ “ምናልባት እኮ ዮሴፍ በፈጸምንበት በደል የተነሳ ቂም ይዞ ይበቀለን ይሆናል” አሉ።+ 16  ስለዚህ ለዮሴፍ እንዲህ የሚል መልእክት ላኩበት፦ “አባትህ ከመሞቱ በፊት እንዲህ የሚል ትእዛዝ አስተላልፎ ነበር፦ 17  ‘ዮሴፍን እንዲህ በሉት፦ “የወንድሞችህን በደል እንዲሁም በአንተ ላይ እንዲህ ያለ ጉዳት በማድረስ የሠሩትን ኃጢአት ይቅር እንድትል እማጸንሃለሁ።”’ እናም እባክህ የአባትህን አምላክ አገልጋዮች በደል ይቅር በል።” ዮሴፍም እንዲህ ሲሉት አለቀሰ። 18  ከዚያም ወንድሞቹ መጡ፤ በፊቱም ተደፍተው በመስገድ “እኛ የአንተ ባሪያዎች ነን!” አሉት።+ 19  ዮሴፍም እንዲህ አላቸው፦ “አይዟችሁ አትፍሩ። ለመሆኑ እኔን በአምላክ ቦታ ያስቀመጠኝ ማን ነው? 20  ምንም እንኳ እኔን ለመጉዳት አስባችሁ የነበረ ቢሆንም+ አምላክ ግን ይኸው ዛሬ እንደምታዩት ነገሩን ለመልካም አደረገው፤ የብዙ ሰዎችንም ሕይወት ለማዳን ተጠቀመበት።+ 21  ስለሆነም አትፍሩ። ለእናንተም ሆነ ለትናንሽ ልጆቻችሁ የሚያስፈልገውን እህል እሰጣችኋለሁ።”+ እሱም በዚህ መንገድ አጽናናቸው፤ እንዲሁም አረጋጋቸው። 22  ዮሴፍ ከአባቱ ቤተሰቦች ጋር በግብፅ መኖሩን ቀጠለ፤ ዮሴፍም 110 ዓመት ኖረ። 23  እሱም የኤፍሬምን ወንዶች ልጆች እስከ ሦስት ትውልድ ድረስ አየ፤+ እንዲሁም የምናሴን ልጅ የማኪርን ወንዶች ልጆች አየ።+ እነዚህ የተወለዱት በዮሴፍ ጭን ላይ ነበር።* 24  ከጊዜ በኋላ ዮሴፍ ወንድሞቹን እንዲህ አላቸው፦ “እንግዲህ እኔ የምሞትበት ጊዜ ቀርቧል፤ ይሁንና አምላክ ፊቱን ወደ እናንተ እንደሚመልስ የተረጋገጠ ነው፤+ ደግሞም ያለጥርጥር ከዚህ ምድር አውጥቶ ለአብርሃም፣ ለይስሐቅና ለያዕቆብ ወደማለላቸው ምድር ያስገባችኋል።”+ 25  በመሆኑም ዮሴፍ የእስራኤልን ወንዶች ልጆች “አምላክ ፊቱን ወደ እናንተ እንደሚመልስ ጥርጥር የለውም። አደራ፣ በዚያን ጊዜ አፅሜን ከዚህ ይዛችሁ እንድትወጡ” በማለት አስማላቸው።+ 26  ዮሴፍም በ110 ዓመቱ ሞተ፤ እነሱም አስከሬኑን መድኃኒት ቀቡት፤+ ከዚያም በሬሳ ሣጥን ውስጥ አድርገው በግብፅ አስቀመጡት።

የግርጌ ማስታወሻ

ወይም “ቤተሰቦች።”
“የግብፃውያን ሐዘን” የሚል ትርጉም አለው።
እንደ ልጆቹ ይመለከታቸውና በጣም ይወዳቸው እንደነበር ያመለክታል።