የሐዋርያት ሥራ 16:1-40

  • ጳውሎስ ጢሞቴዎስን መረጠ (1-5)

  • “ወደ መቄዶንያ ተሻገርና እርዳን” (6-10)

  • በፊልጵስዩስ ሊዲያ ክርስትናን ተቀበለች (11-15)

  • ጳውሎስና ሲላስ ታሰሩ (16-24)

  • የእስር ቤቱ ጠባቂና ቤተሰቡ ተጠመቁ (25-34)

  • “እነሱ ራሳቸው መጥተው ይዘውን ይውጡ” (35-40)

16  ከዚያም ጳውሎስ ወደ ደርቤና ወደ ልስጥራ+ ሄደ። በዚያም አማኝ የሆነች አይሁዳዊት እናትና ግሪካዊ አባት ያለው ጢሞቴዎስ+ የሚባል አንድ ደቀ መዝሙር ነበር፤  እሱም በልስጥራና በኢቆንዮን ባሉ ወንድሞች፣ በመልካም ምግባሩ የተመሠከረለት ነበር።  ጳውሎስ፣ ጢሞቴዎስ አብሮት እንዲሄድ እንደሚፈልግ ገለጸ፤ አባቱ ግሪካዊ መሆኑን ሁሉም ሰው ያውቅ ስለነበረም በእነዚያ አካባቢዎች ስላሉት አይሁዳውያን ሲል ወስዶ ገረዘው።+  በየከተሞቹ ሲያልፉም በዚያ ለሚያገኟቸው ሁሉ በኢየሩሳሌም ያሉት ሐዋርያትና ሽማግሌዎች ያስተላለፏቸውን ውሳኔዎች እንዲጠብቁ ጉዳዩን ያሳውቋቸው ነበር።+  ጉባኤዎቹም በእምነት እየጠነከሩና ከዕለት ወደ ዕለት በቁጥር እየጨመሩ ሄዱ።  ከዚህም ሌላ መንፈስ ቅዱስ ቃሉን በእስያ አውራጃ እንዳይናገሩ ስለከለከላቸው በፍርግያና በገላትያ አድርገው አለፉ።+  ደግሞም ወደ ሚስያ በወረዱ ጊዜ ወደ ቢቲኒያ+ ሊገቡ ሞከሩ፤ ሆኖም የኢየሱስ መንፈስ አልፈቀደላቸውም።  ስለዚህ በሚስያ በኩል አልፈው* ወደ ጥሮአስ ወረዱ።  ጳውሎስም ሌሊት በራእይ አንድ የመቄዶንያ ሰው በዚያ ቆሞ “ወደ መቄዶንያ ተሻገርና እርዳን” ብሎ ሲለምነው አየ። 10  ጳውሎስ ይህን ራእይ እንዳየም ‘አምላክ ምሥራቹን እንድንሰብክላቸው ጠርቶናል’ የሚል መደምደሚያ ላይ ስለደረስን ወደ መቄዶንያ ለመሄድ ሞከርን። 11  ስለዚህ ከጥሮአስ መርከብ ተሳፍረን በቀጥታ ወደ ሳሞትራቄ ሄድን፤ በማግስቱ ደግሞ ወደ ኔያጶሊስ ተጓዝን፤ 12  ከዚያም ተነስተን የሮማውያን ቅኝ ግዛትና የመቄዶንያ አውራጃ ቁልፍ ከተማ ወደሆነችው ወደ ፊልጵስዩስ+ መጣን። በዚህች ከተማም ለተወሰኑ ቀናት ቆየን። 13  በሰንበት ቀን የጸሎት ስፍራ ይገኝበታል ብለን ወዳሰብነው ከከተማው በር ውጭ ወዳለ አንድ ወንዝ ዳር ሄድን፤ በዚያም ተቀምጠን ተሰብስበው ለነበሩት ሴቶች መናገር ጀመርን። 14  ከትያጥሮን+ ከተማ የመጣች፣ ሐምራዊ ጨርቅ የምትሸጥና* አምላክን የምታመልክ ሊዲያ የተባለች አንዲት ሴት እያዳመጠች ነበር፤ ይሖዋም* ጳውሎስ የሚናገረውን በማስተዋል እንድትሰማ ልቧን በደንብ ከፈተላት። 15  እሷና በቤቷ የሚኖሩ ሰዎች ከተጠመቁ+ በኋላ “ለይሖዋ* ታማኝ እንደሆንኩ አድርጋችሁ ከቆጠራችሁኝ ወደ ቤቴ ገብታችሁ እረፉ” ብላ ተማጸነችን። እንድንገባም አስገደደችን። 16  አንድ ቀን ወደ ጸሎት ስፍራ እየሄድን ሳለ መንፈስ ይኸውም የጥንቆላ+ ጋኔን ያደረባት አንዲት አገልጋይ አገኘችን። እሷም በጥንቆላ ሥራዋ ለጌቶቿ ብዙ ትርፍ ታስገኝላቸው ነበር። 17  ይህች ሴት ጳውሎስንና እኛን እየተከተለች “እነዚህ ሰዎች የመዳንን መንገድ የሚያውጁላችሁ የልዑሉ አምላክ ባሪያዎች ናቸው” በማለት ትጮኽ ነበር።+ 18  ለብዙ ቀናት እየደጋገመች ይህንኑ ትናገር ነበር። በመጨረሻም ጳውሎስ በዚህ ነገር በመሰላቸቱ ዞር ብሎ ያን መንፈስ “ከእሷ እንድትወጣ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አዝሃለሁ” አለው። መንፈሱም በዚያው ቅጽበት ወጣ።+ 19  ጌቶቿ የገቢ ምንጫቸው መቋረጡን+ ባዩ ጊዜ ጳውሎስንና ሲላስን ይዘው እየጎተቱ ገዢዎቹ ወደሚገኙበት ወደ ገበያ ስፍራው* ወሰዷቸው።+ 20  ከዚያም የከተማዋ ሕግ አስከባሪዎች ፊት አቅርበዋቸው እንዲህ አሉ፦ “እነዚህ ሰዎች ከተማችንን ክፉኛ እያወኩ ነው።+ እነሱ አይሁዳውያን ናቸው፤ 21  ደግሞም እኛ ሮማውያን ልንቀበለውም ሆነ ልንፈጽመው የማይገባንን ልማድ እያስፋፉ ነው።” 22  ሕዝቡም በአንድነት በእነሱ ላይ ተነሳ፤ የከተማዋ ሕግ አስከባሪዎችም ልብሳቸውን ከገፈፏቸው በኋላ በበትር እንዲደበደቡ አዘዙ።+ 23  በጣም ከደበደቧቸው በኋላ እስር ቤት አስገቧቸው፤ የእስር ቤቱንም ጠባቂ በደንብ እንዲጠብቃቸው አዘዙት።+ 24  እሱም እንዲህ ያለ ትእዛዝ ስለተሰጠው ወደ እስር ቤቱ ውስጠኛ ክፍል አስገብቶ እግራቸውን በእግር ግንድ አሰረው። 25  ይሁንና እኩለ ሌሊት ገደማ ጳውሎስና ሲላስ እየጸለዩና አምላክን በመዝሙር እያወደሱ ነበር፤+ ሌሎቹ እስረኞችም ያዳምጧቸው ነበር። 26  ድንገት ከባድ የምድር ነውጥ በመከሰቱ የእስር ቤቱ መሠረት ተናጋ። በተጨማሪም በሮቹ ወዲያውኑ የተከፈቱ ሲሆን ሁሉም የታሰሩበት ማሰሪያ ተፈታ።+ 27  የእስር ቤቱ ጠባቂም ከእንቅልፉ ነቅቶ የእስር ቤቱ በሮች መከፈታቸውን ሲያይ እስረኞቹ ያመለጡ መስሎት ራሱን ለመግደል ሰይፉን መዘዘ።+ 28  ጳውሎስ ግን ድምፁን ከፍ አድርጎ “በራስህ ላይ ክፉ ነገር አታድርግ! ሁላችንም እዚህ አለን” ሲል ተናገረ። 29  በዚህ ጊዜ የእስር ቤቱ ጠባቂ መብራት እንዲያመጡለት ጠይቆ ወደ ውስጥ ዘሎ ገባ፤ እየተንቀጠቀጠም በጳውሎስና በሲላስ ፊት ተደፋ። 30  ወደ ውጭ ካወጣቸውም በኋላ “ጌቶቼ፣ ለመዳን ምን ማድረግ ይኖርብኛል?” አለ። 31  እነሱም “በጌታ ኢየሱስ እመን፤ አንተም ሆንክ ቤተሰብህ ትድናላችሁ” አሉት።+ 32  ከዚያም ለእሱና በቤቱ ላሉት ሰዎች ሁሉ የይሖዋን* ቃል ነገሯቸው። 33  ጠባቂውም ሌሊት በዚያው ሰዓት ይዟቸው ሄዶ ቁስላቸውን አጠበላቸው። ከዚያም እሱና መላው ቤተሰቡ ወዲያውኑ ተጠመቁ።+ 34  ወደ ቤቱም ወስዶ ማዕድ አቀረበላቸው፤ በአምላክ በማመኑም ከመላው ቤተሰቡ ጋር እጅግ ተደሰተ። 35  ሲነጋም የከተማዋ ሕግ አስከባሪዎች “እነዚያን ሰዎች ልቀቃቸው” ብለው እንዲነግሩት መኮንኖቹን ላኩበት። 36  የእስር ቤቱ ጠባቂ የላኩትን መልእክት እንዲህ ሲል ለጳውሎስ ነገረው፦ “የከተማዋ ሕግ አስከባሪዎች ሁለታችሁ እንድትፈቱ ሰዎች ልከዋል። ስለዚህ አሁን ወጥታችሁ በሰላም ሂዱ።” 37  ጳውሎስ ግን እንዲህ አላቸው፦ “እኛ የሮም ዜጎች+ ሆነን ሳለ ያለፍርድ በሕዝብ ፊት ገርፈው እስር ቤት ወረወሩን። ታዲያ አሁን በድብቅ አስወጥተው ሊጥሉን ይፈልጋሉ? እንዲህማ አይሆንም! እነሱ ራሳቸው መጥተው ይዘውን ይውጡ።” 38  መኮንኖቹም ይህን ነገር ለከተማዋ ሕግ አስከባሪዎች ነገሯቸው። እነሱም ሰዎቹ የሮም ዜጎች መሆናቸውን ሲሰሙ ፍርሃት አደረባቸው።+ 39  በመሆኑም መጥተው ለመኗቸው፤ ከእስር ቤቱም ይዘዋቸው ከወጡ በኋላ ከተማዋን ለቀው እንዲሄዱ ጠየቋቸው። 40  እነሱ ግን ከእስር ቤቱ ወጥተው ወደ ሊዲያ ቤት አመሩ፤ እዚያም ወንድሞችን አግኝተው ካበረታቷቸው+ በኋላ ከተማዋን ለቀው ሄዱ።

የግርጌ ማስታወሻ

ወይም “ሚስያን አቋርጠው።”
ወይም “ሐምራዊ ቀለም ያለው ማቅለሚያ የምትሸጥና።”
ከተጨማሪው መረጃ ላይ ሀ5ን ተመልከት።
ከተጨማሪው መረጃ ላይ ሀ5ን ተመልከት።
ሰዎች የሚገበያዩበት እንዲሁም ሕዝባዊ ስብሰባ የሚካሄድበት ገላጣ ስፍራ።
ከተጨማሪው መረጃ ላይ ሀ5ን ተመልከት።