ለፊልጵስዩስ ሰዎች የተጻፈ ደብዳቤ 3:1-21

  • “በሥጋ አንመካም” (1-11)

    • “ሁሉንም ነገር እንደ ኪሳራ እቆጥረዋለሁ” (7-9)

  • ግቡ ላይ ለመድረስ እጣጣራለሁ (12-21)

    • “የሰማይ ዜጎች ነን” (20)

3  በመጨረሻም ወንድሞቼ፣ ምንጊዜም በጌታ ደስ ይበላችሁ።+ ያንኑ ነገር ደግሜ ብጽፍላችሁ እኔን አይታክተኝም፤ ይህ ደግሞ ለእናንተ ጠቃሚ ነው።  ከውሾች ተጠንቀቁ፤ ጎጂ ነገር ከሚያደርጉ ሰዎች ተጠንቀቁ፤ ሥጋን ከሚቆርጡ* ሰዎች ተጠንቀቁ።+  እውነተኛውን ግርዘት የተገረዝነው እኛ ነንና፤+ እኛ በአምላክ መንፈስ፣ ቅዱስ አገልግሎት እናቀርባለን፤ በክርስቶስ ኢየሱስ እንኩራራለን፤+ ደግሞም በሥጋ አንመካም፤  ይሁንና በሥጋ የምመካበት ነገር አለኝ የሚል ማንም ቢኖር ያ ሰው እኔ ነኝ። በሥጋ የሚመካበት ነገር እንዳለው አድርጎ የሚያስብ ሌላ ማንም ሰው ቢኖር እኔ እበልጣለሁ፦  በስምንተኛው ቀን የተገረዝኩና+ ከእስራኤል ብሔር፣ ከቢንያም ነገድ የተገኘሁ ስሆን ከዕብራውያን የተወለድኩ ዕብራዊ ነኝ፤+ ስለ ሕግ ከተነሳ ፈሪሳዊ ነበርኩ፤+  ስለ ቅንዓት ከተነሳ በጉባኤው ላይ ስደት አደርስ ነበር፤+ ሕጉን በመታዘዝ ስለሚገኘው ጽድቅ ከተነሳ ደግሞ እንከን የማይገኝብኝ መሆኔን አስመሥክሬአለሁ።  ሆኖም ለእኔ ትርፍ የነበረውን ነገር ሁሉ ለክርስቶስ ስል እንደ ኪሳራ ቆጥሬዋለሁ።*+  ከዚህም በላይ ስለ ጌታዬ ስለ ክርስቶስ ኢየሱስ ከሚገልጸው የላቀ ዋጋ ያለው እውቀት አንጻር ሁሉንም ነገር እንደ ኪሳራ እቆጥረዋለሁ። ለእሱ ስል ሁሉንም ነገር አጥቻለሁ፤ ያጣሁትንም ነገር ሁሉ እንደ ጉድፍ* እቆጥረዋለሁ፤ ይህም ክርስቶስን አገኝ ዘንድ ነው።  እንዲሁም ሕግ በመጠበቅ ባገኘሁት በራሴ ጽድቅ ሳይሆን በክርስቶስ በማመን+ በሚገኘው ጽድቅ+ ይኸውም በእምነት ላይ በተመሠረተው ከአምላክ በሚገኘው ጽድቅ+ ከክርስቶስ ጋር አንድ ለመሆን ነው። 10  ፍላጎቴ እሱንና የትንሣኤውን ኃይል+ ማወቅ እንዲሁም እሱ ለሞተው ዓይነት ሞት ራሴን አሳልፌ በመስጠት+ የሥቃዩ ተካፋይ+ መሆን ነው፤ 11  ደግሞም በተቻለ መጠን መጀመሪያ ላይ ትንሣኤ ከሚያገኙት መካከል መሆን ነው።+ 12  አሁን ሽልማቱን አግኝቻለሁ ወይም አሁን ወደ ፍጽምና ደርሻለሁ ማለት አይደለም፤ ነገር ግን ክርስቶስ ኢየሱስ እኔን የመረጠበትን ያን ነገር የራሴ ማድረግ እችል እንደሆነ ለማየት ጥረት እያደረግኩ ነው።+ 13  ወንድሞች፣ እኔ እንዳገኘሁት አድርጌ አላስብም፤ ነገር ግን ስለ አንድ ነገር እርግጠኛ ነኝ፦ ከኋላዬ ያሉትን ነገሮች እየረሳሁ+ ከፊቴ ወዳሉት ነገሮች እንጠራራለሁ፤+ 14  አምላክ በክርስቶስ ኢየሱስ በኩል የሚሰጠውን የሰማያዊውን ሕይወት+ ሽልማት አገኝ ዘንድ ግቡ ላይ ለመድረስ እየተጣጣርኩ ነው።+ 15  እንግዲህ ጎልማሳ+ የሆንነው እኛ ይህ አስተሳሰብ ይኑረን፤ በማንኛውም ረገድ ከዚህ የተለየ ሐሳብ ቢኖራችሁ አምላክ ትክክለኛውን አስተሳሰብ ይገልጥላችኋል። 16  ያም ሆነ ይህ ምንም ያህል እድገት ያደረግን ብንሆን በዚሁ መንገድ በአግባቡ ወደፊት መጓዛችንን እንቀጥል። 17  ወንድሞች፣ ሁላችሁም የእኔን ምሳሌ ተከተሉ፤+ እንዲሁም እኛ ከተውንላችሁ ምሳሌ ጋር በሚስማማ መንገድ የሚመላለሱትን ሁሉ ልብ ብላችሁ ተመልከቱ። 18  የክርስቶስ የመከራ እንጨት* ጠላቶች ሆነው የሚመላለሱ ብዙዎች አሉና፤ ከዚህ በፊት ደጋግሜ እጠቅሳቸው ነበር፤ ሆኖም አሁን በእንባ ጭምር እጠቅሳቸዋለሁ። 19  መጨረሻቸው ጥፋት ነው፤ ሆዳቸው* አምላካቸው ነው፤ ሊያፍሩበት በሚገባው ነገር ይኩራራሉ፤ አእምሯቸው ደግሞ ያተኮረው በምድራዊ ነገሮች ላይ ነው።+ 20  እኛ ግን የሰማይ+ ዜጎች ነን፤+ ከዚያ የሚመጣውንም አዳኝ ይኸውም ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን በጉጉት እንጠባበቃለን፤+ 21  እሱም ክብር የተላበሰውን አካሉን እንዲመስል፣* ታላቅ ኃይሉን ተጠቅሞ ደካማውን አካላችንን ይለውጠዋል፤+ እንዲሁም ሁሉንም ነገር ለራሱ ያስገዛል።+

የግርጌ ማስታወሻ

የግርዘት ልማድን የሚደግፉ ሰዎችን ያመለክታል።
“በፈቃደኝነት ትቼዋለሁ” ማለትም ሊሆን ይችላል።
ወይም “ቆሻሻ፤ ትርኪ ምርኪ።”
ወይም “ሥጋዊ ፍላጎታቸው።”
ቃል በቃል “(ከክቡር አካሉ ጋር) እንዲስማማ።”