አንደኛ ሳሙኤል 12:1-25

  • የሳሙኤል የመሰነባበቻ ንግግር (1-25)

    • ‘ከንቱ ነገሮችን አትከተሉ’ (21)

    • ይሖዋ ሕዝቡን አይተውም (22)

12  በመጨረሻም ሳሙኤል እስራኤላውያንን ሁሉ እንዲህ አላቸው፦ “እንግዲህ እኔ ያላችሁኝን ሁሉ አድርጌአለሁ፤* የሚገዛችሁም ንጉሥ አንግሼላችኋለሁ።+  የሚመራችሁ* ንጉሥ ይኸው!+ እኔ ዕድሜዬ ገፍቷል፤ ፀጉሬም ሸብቷል፤ እነሆ፣ ልጆቼ አብረዋችሁ ናቸው፤+ እኔ እንደሆንኩ ከልጅነቴ ጀምሮ እስከዚህ ቀን ድረስ ስመራችሁ ቆይቻለሁ።+  አሁንም ያለሁት በፊታችሁ ነው። እስቲ የምከሰስበት ነገር ካለ በይሖዋና እሱ በቀባው+ ፊት ንገሩኝ፦ የማንን በሬ ወይም የማንን አህያ ወስጃለሁ?+ ወይስ ማንን አታልያለሁ? ደግሞስ በማን ላይ ግፍ ፈጽሜአለሁ? አይቼ እንዳላየሁ ለመሆንስ ከማን እጅ ጉቦ ተቀብያለሁ?+ እንዲህ አድርጌ ከሆነ እመልስላችኋለሁ።”+  በዚህ ጊዜ እነሱ “አታለኸንም ሆነ ግፍ ፈጽመህብን ወይም ደግሞ ከማንም ሰው እጅ ምንም ነገር ተቀብለህ አታውቅም” አሉት።  በመሆኑም ሳሙኤል “እኔን የምትከሱበት ምንም ነገር እንዳላገኛችሁ* ይሖዋም ሆነ እሱ የቀባው ዛሬ በእናንተ ላይ ምሥክሮች ናቸው” አላቸው። እነሱም “እሱ ምሥክር ነው” አሉ።  ሳሙኤልም ለሕዝቡ እንዲህ አለ፦ “ሙሴንና አሮንን የመረጠው እንዲሁም አባቶቻችሁን ከግብፅ ምድር ያወጣው+ ይሖዋ ምሥክር ነው።  እንግዲህ እናንተ ባላችሁበት ቁሙ፤ እኔም ይሖዋ ለእናንተና ለአባቶቻችሁ ባደረጋቸው የጽድቅ ሥራዎች መሠረት በይሖዋ ፊት እፋረዳችኋለሁ።  “ያዕቆብ ወደ ግብፅ በገባና+ አባቶቻችሁም ይሖዋ እንዲረዳቸው በጮኹ ጊዜ+ ይሖዋ አባቶቻችሁን ከግብፅ መርተው እንዲያወጧቸውና በዚህ ስፍራ እንዲያኖሯቸው+ ሙሴንና አሮንን ላከ።+  እነሱ ግን አምላካቸውን ይሖዋን ረሱ፤ እሱም የሃጾር ሠራዊት አለቃ ለነበረው ለሲሳራ፣+ ለፍልስጤማውያንና ለሞዓብ+ ንጉሥ እጅ+ አሳልፎ ሸጣቸው፤+ እነሱም ወጓቸው። 10  በዚህ ጊዜ ይሖዋ እንዲረዳቸው ጮኹ፤+ እንዲህም አሉ፦ ‘ባአልንና+ የአስታሮትን+ ምስሎች ለማገልገል ስንል ይሖዋን ስለተውን ኃጢአት ሠርተናል፤+ ስለሆነም እንድናገለግልህ አሁን ከጠላቶቻችን እጅ ታደገን።’ 11  ከዚያም ይሖዋ ያለስጋት መኖር እንድትችሉ የሩባአልን፣+ ቤዳንን፣ ዮፍታሔንና+ ሳሙኤልን+ ልኮ በዙሪያችሁ ካሉት ጠላቶቻችሁ ሁሉ እጅ ታደጋችሁ።+ 12  የአሞናውያን ንጉሥ የሆነው ናሃሽ+ በእናንተ ላይ ጥቃት ለመሰንዘር እንደመጣ ስታዩ ምንም እንኳ አምላካችሁ ይሖዋ ንጉሣችሁ ቢሆንም+ ‘አይሆንም፣ ንጉሥ እንዲነግሥልን እንፈልጋለን!’ አላችሁኝ።+ 13  እንግዲህ የመረጣችሁትና የጠየቃችሁት ንጉሥ ይኸውላችሁ። እነሆ፣ ይሖዋ በላያችሁ ንጉሥ አንግሦአል።+ 14  ይሖዋን ብትፈሩና+ ብታገለግሉ፣+ ቃሉን ብትታዘዙና+ በይሖዋ ትእዛዝ ላይ ባታምፁ እንዲሁም እናንተም ሆናችሁ በላያችሁ የሚገዛው ንጉሥ አምላካችሁን ይሖዋን ብትከተሉ መልካም ይሆንላችኋል። 15  ሆኖም የይሖዋን ቃል ባትታዘዙና በይሖዋ ትእዛዝ ላይ ብታምፁ የይሖዋ እጅ በእናንተና በአባቶቻችሁ ላይ ይሆናል።+ 16  ስለሆነም አሁን ባላችሁበት ቆማችሁ ይሖዋ ዓይናችሁ እያየ የሚፈጽመውን ይህን ታላቅ ነገር ተመልከቱ። 17  ዛሬ የስንዴ መከር የሚታጨድበት ጊዜ አይደለም? ይሖዋን ነጎድጓድና ዝናብ እንዲልክ እጠይቀዋለሁ፤ እናንተም ንጉሥ እንዲነግሥላችሁ በመጠየቅ በይሖዋ ፊት ምን ያህል ታላቅ በደል እንደፈጸማችሁ ታውቃላችሁ፤ ደግሞም ታስተውላላችሁ።”+ 18  ከዚያም ሳሙኤል ይሖዋን ጠየቀ፤ ይሖዋም በዚያ ቀን ነጎድጓድና ዝናብ ላከ፤ በመሆኑም ሕዝቡ ሁሉ ይሖዋንና ሳሙኤልን እጅግ ፈራ። 19  ሕዝቡም ሳሙኤልን “ሌላው ኃጢአታችን ሳያንሰን ንጉሥ እንዲነግሥልን በመለመን ተጨማሪ በደል ስለፈጸምን እንዳንሞት ስለ አገልጋዮችህ ወደ አምላክህ ወደ ይሖዋ ጸልይልን”+ አለው። 20  በመሆኑም ሳሙኤል ሕዝቡን እንዲህ አለ፦ “አትፍሩ። እርግጥ ይህን ሁሉ ክፋት ፈጽማችኋል። ብቻ ይሖዋን ከመከተል ዞር አትበሉ፤+ ይሖዋንም በሙሉ ልባችሁ አገልግሉት።+ 21  ምንም ዋጋ የሌላቸውንና+ ማዳን የማይችሉ ከንቱ+ ነገሮችን* ወደ መከተል ዞር አትበሉ፤ ምክንያቱም እነሱ ከንቱ* ነገሮች ናቸው። 22  ይሖዋ ስለ ታላቁ ስሙ ሲል+ ሕዝቡን አይተውም፤+ ምክንያቱም ይሖዋ እናንተን የራሱ ሕዝብ ሊያደርጋችሁ ፈልጓል።+ 23  እኔም ብሆን ስለ እናንተ መጸለዬን በመተው በይሖዋ ላይ ኃጢአት መሥራት ፈጽሞ የማላስበው ነገር ነው፤ እንዲሁም መልካምና ትክክለኛ የሆነውን መንገድ እናንተን ማስተማሬን እቀጥላለሁ። 24  ብቻ እናንተ ይሖዋን ፍሩ፤+ በሙሉ ልባችሁም በታማኝነት* አገልግሉት፤ ለእናንተ ያደረጋቸውን ታላላቅ ነገሮች አስታውሱ።+ 25  ሆኖም በግትርነት መጥፎ ነገር ማድረጋችሁን ብትቀጥሉ እናንተም ሆናችሁ ንጉሣችሁ+ ተጠራርጋችሁ ትጠፋላችሁ።”+

የግርጌ ማስታወሻ

ቃል በቃል “ቃላችሁን ሁሉ ሰምቻለሁ።”
ቃል በቃል “ፊት ፊታችሁ የሚሄደው።”
ቃል በቃል “በእጄ ምንም ነገር እንዳላገኛችሁ።”
ወይም “የማይጨበጡ ነገሮችን።”
ወይም “የማይጨበጡ።”
ወይም “በእውነት።”