አንደኛ ሳሙኤል 13:1-23

  • ሳኦል ወታደሮችን መረጠ (1-4)

  • ሳኦል የትዕቢት እርምጃ ወሰደ (5-9)

  • ሳሙኤል ሳኦልን ገሠጸው (10-14)

  • እስራኤላውያን ያለ ጦር መሣሪያ ተዋጉ (15-23)

13  ሳኦል በነገሠ ጊዜ ዕድሜው . . .* ነበር፤+ እሱም በእስራኤል ላይ ሁለት ዓመት ገዛ።  ሳኦል ከእስራኤላውያን መካከል 3,000 ሰዎችን መረጠ፤ ከእነዚህም መካከል 2,000ዎቹ በሚክማሽና በቤቴል ተራራማ አካባቢ ከሳኦል ጋር ሆኑ፤ ሌሎቹ 1,000 ሰዎች ደግሞ በቢንያም ግዛት በጊብዓ+ ከዮናታን+ ጋር ሆኑ። የቀሩትን ሰዎች እያንዳንዳቸውን ወደየድንኳናቸው አሰናበታቸው።  ዮናታንም በጌባ+ የነበረውን የፍልስጤማውያንን+ የጦር ሰፈር መታ፤ ፍልስጤማውያንም ይህን ሰሙ። ሳኦልም “ዕብራውያን ይስሙ!” በማለት በምድሩ ሁሉ ቀንደ መለከት አስነፋ።+  እስራኤላውያን በሙሉ “ሳኦል የፍልስጤማውያንን የጦር ሰፈር መታ፤ እስራኤላውያንም በፍልስጤማውያን ዘንድ እንደ ግም ተቆጠሩ” ሲባል ሰሙ። በመሆኑም ሕዝቡ ሳኦልን ለመከተል በጊልጋል ተሰበሰበ።+  ፍልስጤማውያንም 30,000 የጦር ሠረገሎች፣ 6,000 ፈረሰኞችና በባሕር ዳር እንዳለ አሸዋ እጅግ ብዙ የሆነ ሠራዊት ይዘው ከእስራኤላውያን ጋር ለመዋጋት ተሰባሰቡ፤+ እነሱም ወጥተው ከቤትአዌን+ በስተ ምሥራቅ በሚክማሽ ሰፈሩ።  የእስራኤል ሰዎችም አደጋ እንደተጋረጠባቸው ስላዩ ከፍተኛ ውጥረት ውስጥ ገብተው ነበር፤ በመሆኑም ሕዝቡ በየዋሻው፣ በየጉድጓዱ፣ በየዓለቱ፣ በየጎሬውና በየውኃ ማጠራቀሚያ ጉድጓዱ ውስጥ ተደበቀ።+  እንዲያውም አንዳንድ ዕብራውያን ዮርዳኖስን ተሻግረው ወደ ጋድና ወደ ጊልያድ+ ምድር ሄዱ። ሳኦል ግን እዚያው ጊልጋል ነበር፤ የተከተሉት ሰዎችም ሁሉ በፍርሃት ይንቀጠቀጡ ነበር።  እሱም ሳሙኤል የቀጠረው ጊዜ እስኪደርስ ድረስ ለሰባት ቀን ጠበቀ፤ ሳሙኤል ግን ወደ ጊልጋል አልመጣም፤ ሕዝቡም ሳኦልን ትቶ መበታተን ጀመረ።  በመጨረሻም ሳኦል “የሚቃጠለውን መሥዋዕትና የኅብረት መሥዋዕቶቹን አምጡልኝ” አለ። ከዚያም የሚቃጠለውን መሥዋዕት አቀረበ።+ 10  ሆኖም ሳኦል የሚቃጠለውን መሥዋዕት አቅርቦ እንደጨረሰ ሳሙኤል መጣ። በመሆኑም ሳኦል ሊቀበለውና ሊባርከው ወጣ። 11  ከዚያም ሳሙኤል “ያደረግከው ነገር ምንድን ነው?” አለው። ሳኦልም እንዲህ ሲል መለሰ፦ “ሕዝቡ ትቶኝ መበታተን እንደጀመረና+ አንተም በተቀጠረው ጊዜ እንዳልመጣህ እንዲሁም ፍልስጤማውያኑ በሚክማሽ+ እየተሰባሰቡ መሆናቸውን አየሁ። 12  በመሆኑም ‘እንግዲህ ፍልስጤማውያን ወደ ጊልጋል ወርደው ሊወጉኝ ነው፤ እኔ ደግሞ ይሖዋ ሞገስ እንዲያሳየኝ አለመንኩም’ ብዬ አሰብኩ። ስለሆነም የሚቃጠለውን መሥዋዕት ማቅረብ ግድ ሆነብኝ።” 13  በዚህ ጊዜ ሳሙኤል ሳኦልን እንዲህ አለው፦ “የፈጸምከው የሞኝነት ድርጊት ነው። አምላክህ ይሖዋ የሰጠህን ትእዛዝ አልጠበቅክም።+ ጠብቀህ ቢሆን ኖሮ ይሖዋ መንግሥትህን በእስራኤል ላይ ለዘላለም ባጸናልህ ነበር። 14  አሁን ግን መንግሥትህ አይዘልቅም።+ ይሖዋ እንደ ልቡ የሚሆንለት ሰው ያገኛል፤+ ይሖዋም በሕዝቡ ላይ መሪ አድርጎ ይሾመዋል፤+ ምክንያቱም አንተ የይሖዋን ትእዛዝ አልጠበቅክም።”+ 15  ከዚያም ሳሙኤል ተነስቶ ከጊልጋል በቢንያም ግዛት ወደምትገኘው ወደ ጊብዓ ወጣ፤ ሳኦልም ሕዝቡን ቆጠረ፤ አብረውት ያሉት ሰዎች ብዛታቸው 600 ገደማ ነበር።+ 16  ሳኦልና ልጁ ዮናታን እንዲሁም አብረዋቸው የቀሩት ሰዎች በቢንያም ግዛት በምትገኘው በጌባ+ ሰፍረው የነበረ ሲሆን ፍልስጤማውያን ደግሞ በሚክማሽ+ ሰፍረው ነበር። 17  በሦስት ምድብ የተከፈለው የወራሪዎች ቡድን ከፍልስጤማውያን ሰፈር ይወጣል። አንደኛው ቡድን ወደ ሹአል ምድር ወደ ኦፍራ ወደሚወስደው መንገድ ያቀናል፤ 18  ሌላኛው ቡድን ወደ ቤትሆሮን+ ወደሚወስደው መንገድ ይሄዳል፤ ሦስተኛው ቡድን ደግሞ የጸቦይምን ሸለቆ ቁልቁል ወደሚያሳየው ወሰን ይኸውም ወደ ምድረ በዳው ወደሚወስደው መንገድ ያቀናል። 19  በመላው የእስራኤል ምድር አንድም ብረት ቀጥቃጭ አልነበረም፤ ምክንያቱም ፍልስጤማውያን “ዕብራውያን ሰይፍ ወይም ጦር እንዳይሠሩ” ብለው ነበር። 20  ስለዚህ እስራኤላውያን በሙሉ ማረሻቸውን ወይም ዶማቸውን አሊያም መጥረቢያቸውን ወይም ማጭዳቸውን ለማሳል ወደ ፍልስጤማውያን ይወርዱ ነበር። 21  ማረሻ፣ ዶማ፣ መንሽና መጥረቢያ ለማሳል እንዲሁም የበሬ መውጊያ ለማሳሰር ዋጋው አንድ ፊም* ነበር። 22  ውጊያው በተደረገበት ቀን ከሳኦልና ከዮናታን ጋር ባሉት ሰዎች እጅ አንድም ሰይፍ ወይም ጦር አልተገኘም፤ መሣሪያ የነበራቸው ሳኦልና ልጁ ዮናታን ብቻ ነበሩ።+ 23  በዚህ ጊዜ አንደኛው የፍልስጤማውያን ጦር በሚክማሽ+ ወደሚገኝ ጠባብ ሸለቆ ወጥቶ ነበር።

የግርጌ ማስታወሻ

በዕብራይስጡ ጽሑፍ ላይ ቁጥሩ አይገኝም።
ይህ ጥንታዊ መለኪያ ሲሆን የሰቅል ሁለት ሦስተኛ ገደማ ይሆናል።