አንደኛ ሳሙኤል 17:1-58

  • ዳዊት ጎልያድን አሸነፈ (1-58)

    • ጎልያድ እስራኤላውያንን ተገዳደረ (8-10)

    • ዳዊት ጎልያድን ሊገጥመው ተስማማ (32-37)

    • ዳዊት በይሖዋ ስም ተዋጋ (45-47)

17  ፍልስጤማውያን+ ሠራዊታቸውን ለውጊያ አሰባሰቡ። እነሱም በይሁዳ በምትገኘው በሶኮህ+ ከተሰባሰቡ በኋላ በሶኮህ እና በአዜቃ+ መካከል በምትገኘው በኤፌስዳሚም+ ሰፈሩ።  ሳኦልና የእስራኤል ሰዎች ደግሞ ተሰባስበው በኤላህ ሸለቆ*+ ውስጥ ሰፈሩ፤ እነሱም ለጦርነት ተሰልፈው ፍልስጤማውያንን ለመግጠም ወጡ።  ፍልስጤማውያን በአንድ በኩል ያለውን ተራራ ያዙ፣ እስራኤላውያን ደግሞ በሌላ በኩል ያለውን ተራራ ያዙ፤ በመካከላቸውም ሸለቆ ነበር።  በዚህ ጊዜ አንድ ኃያል ተዋጊ ከፍልስጤማውያን ሰፈር ብቅ አለ፤ እሱም የጌት+ ሰው ሲሆን ስሙ ጎልያድ+ ይባላል፤ ቁመቱም ስድስት ክንድ ከአንድ ስንዝር* ነበር።  እሱም ከመዳብ የተሠራ የራስ ቁር ደፍቶ ነበር፤ እንዲሁም ከተነባበሩ ጠፍጣፋ መዳቦች የተሠራ ጥሩር ለብሶ ነበር። የጥሩሩም+ ክብደት 5,000 ሰቅል* ነበር።  ቅልጥሙ ላይ ከመዳብ የተሠራ ገምባሌ አድርጎ ነበር፤ በትከሻውና በትከሻውም መካከል ከመዳብ የተሠራ ጦር+ አንግቶ ነበር።  የጭሬውም ዘንግ የሸማኔ መጠቅለያ ያህል ነበር፤+ ከብረት የተሠራው የጭሬው ጫፍ 600 ሰቅል* ነበር፤ ጋሻ ጃግሬውም ከፊት ከፊቱ ይሄድ ነበር።  ከዚያም ጎልያድ ከቆመበት ቦታ ሆኖ የተሰለፈውን የእስራኤል ሠራዊት+ በመጣራት እንዲህ አላቸው፦ “ለውጊያ ተሰልፋችሁ የወጣችሁት ለምንድን ነው? እኔ ፍልስጤማዊ፣ እናንተ ደግሞ የሳኦል አገልጋዮች አይደላችሁም? እንግዲህ አንድ ሰው ምረጡና ወደ እኔ ይውረድ።  ከእኔ ጋር ተዋግቶ እኔን መግደል ከቻለ እኛ የእናንተ አገልጋዮች እንሆናለን። እኔ ባሸንፈውና ብገድለው ግን እናንተ የእኛ አገልጋዮች ትሆናላችሁ፤ እኛንም ታገለግላላችሁ።” 10  በመቀጠልም ፍልስጤማዊው “ዛሬ፣ ለውጊያ የተሰለፈውን የእስራኤል ሠራዊት እሳለቅበታለሁ።*+ በሉ አሁን አንድ ሰው ምረጡና እንጋጠም!” አለ። 11  ሳኦልና እስራኤላውያን በሙሉ ፍልስጤማዊው የተናገረውን ይህን ቃል ሲሰሙ ተሸበሩ፤ እንዲሁም በጣም ፈሩ። 12  ዳዊት በይሁዳ በምትገኘው በቤተልሔም+ የሚኖረው የኤፍራታዊው+ የእሴይ ልጅ ነበር፤ እሴይ+ ስምንት ወንዶች ልጆች+ የነበሩት ሲሆን በሳኦል የንግሥና ዘመን ዕድሜው ገፍቶ ነበር። 13  ሦስቱ የእሴይ ትላልቅ ልጆች ሳኦልን ተከትለው ወደ ውጊያው ሄደው ነበር።+ ወደ ውጊያው የሄዱት ሦስቱ ወንዶች ልጆቹ የበኩር ልጁ ኤልያብ፣+ ሁለተኛ ልጁ አቢናዳብና+ ሦስተኛ ልጁ ሻማህ+ ነበሩ። 14  ዳዊት የሁሉም ታናሽ ነበር፤+ ትላልቆቹ ሦስቱ ሳኦልን ተከትለው ሄደው ነበር። 15  ዳዊት ሳኦልን ያገለግል እንዲሁም ከዚያ እየተመላለሰ በቤተልሔም የአባቱን በጎች ይጠብቅ ነበር።+ 16  ይህ በእንዲህ እንዳለ ፍልስጤማዊው 40 ቀን ሙሉ ጠዋትና ማታ ወደ እነሱ በመቅረብ ፊታቸው ቆሞ ይገዳደራቸው ነበር። 17  ከዚያም እሴይ ልጁን ዳዊትን እንዲህ አለው፦ “እስቲ እባክህ ይህን አንድ የኢፍ* መስፈሪያ ቆሎና እነዚህን አሥር ዳቦዎች ይዘህ በጦር ሰፈሩ ውስጥ ላሉት ወንድሞችህ ቶሎ አድርስላቸው። 18  እንዲሁም ይህን አሥር የአይብ ጥፍጥፍ ለሺህ አለቃው ውሰድለት፤ በተጨማሪም ወንድሞችህ እንዴት እንደሆኑ አይተህ ደህንነታቸውን የሚያረጋግጥ ማስረጃ ይዘህ ና።” 19  የዳዊት ወንድሞች ከሳኦልና ከሌሎቹ የእስራኤል ሰዎች ጋር ሆነው በኤላህ ሸለቆ*+ ከፍልስጤማውያን ጋር እየተዋጉ ነበር።+ 20  በመሆኑም ዳዊት በማለዳ ተነስቶ በጎቹን ለጠባቂ ሰጠ፤ ከዚያም ዕቃዎቹን ይዞ እሴይ ባዘዘው መሠረት ሄደ። እሱም ወደ ጦር ሰፈሩ ሲደርስ የጦር ሠራዊቱ እየፎከረ ወደ ጦር ግንባሩ እየወጣ ነበር። 21  ለጦርነት የተሰለፉት እስራኤላውያንና ፍልስጤማውያንም ፊት ለፊት ተፋጠው ነበር። 22  ዳዊትም ወዲያውኑ ዕቃውን ስንቅ ጠባቂው ጋ አስቀምጦ ወደ ጦር ግንባሩ እየሮጠ ሄደ። እዚያም ሲደርስ የወንድሞቹን ደህንነት መጠየቅ ጀመረ።+ 23  እሱም ከእነሱ ጋር እየተነጋገረ ሳለ የጌት ሰው የሆነው ጎልያድ+ የተባለው ኃያል ፍልስጤማዊ ተዋጊ መጣ። እሱም ለውጊያ ከተሰለፉት ፍልስጤማውያን መካከል ብቅ ብሎ እንደ በፊቱ መደንፋት ጀመረ፤+ ዳዊትም ሰማው። 24  የእስራኤልም ሰዎች በሙሉ ሰውየውን ሲመለከቱት እጅግ ተሸብረው ከፊቱ ሸሹ።+ 25  እነሱም እንዲህ ይሉ ነበር፦ “እየመጣ ያለውን ይህን ሰው አያችሁት? የሚመጣው እኮ በእስራኤል ላይ ለመሳለቅ ነው።+ እሱን ለሚገድል ሰው ንጉሡ ብዙ ሀብት ይሰጠዋል፤ ሴት ልጁንም ይድርለታል፤+ የአባቱንም ቤት በእስራኤል ውስጥ ከማንኛውም ዓይነት ግዴታ ነፃ እንዲሆን ያደርጋል።” 26  ዳዊትም አጠገቡ ቆመው የነበሩትን ሰዎች እንዲህ አላቸው፦ “ለመሆኑ ያን ፍልስጤማዊ ገድሎ እንዲህ ያለውን ውርደት ከእስራኤል ላይ ለሚያስወግድ ሰው ምን ይደረግለታል? ደግሞስ ይህ ያልተገረዘ ፍልስጤማዊ ሕያው በሆነው አምላክ ሠራዊት ላይ የሚሳለቀው ማን ስለሆነ ነው?”+ 27  ሰዎቹም “ለሚገድለው ሰውማ እንዲህ እንዲህ ይደረግለታል” በማለት ቀደም ሲል የተናገሩትን ነገር ደገሙለት። 28  ታላቅ ወንድሙ ኤልያብም+ ዳዊት ከሰዎቹ ጋር ሲነጋገር ሲሰማ በእሱ ላይ እጅግ ተቆጥቶ እንዲህ አለው፦ “ወደዚህ የወረድከው ለምንድን ነው? ለመሆኑ እነዚያን ጥቂት በጎች ምድረ በዳ ላይ ለማን ተውካቸው?+ እኔ ትዕቢትህንና የልብህን ክፉ ሐሳብ መች አጣሁት፤ ወደዚህ የመጣኸው ለሌላ ሳይሆን ውጊያውን ለማየት ነው።” 29  ዳዊትም መልሶ “ቆይ አሁን ምን አጠፋሁ? ጥያቄ እኮ ነው የጠየቅኩት!” አለ። 30  ከዚያም ከእሱ ዞር ብሎ ያንኑ ጥያቄ ሌላ ሰው ጠየቀ፤+ ሰዎቹም እንደቀድሞው ያንኑ መልስ ሰጡት።+ 31  ዳዊት የተናገረው ነገር ተሰማ፤ ለሳኦልም ተነገረው። ስለዚህ ሳኦል ልኮ አስጠራው። 32  ዳዊትም ሳኦልን “በዚህ ሰው የተነሳ የማንም ሰው ልብ አይቅለጥ።* አገልጋይህ ሄዶ ከዚህ ፍልስጤማዊ ጋር ይዋጋል” አለው።+ 33  ሳኦል ግን ዳዊትን “አንተ ገና አንድ ፍሬ ልጅ ነህ፤+ እሱ ግን ከልጅነቱ ጀምሮ ጦረኛ ነው፤ ስለዚህ ይህን ፍልስጤማዊ ልትገጥመው አትችልም” አለው። 34  ዳዊትም ሳኦልን እንዲህ አለው፦ “አገልጋይህ የአባቱን መንጋ በሚጠብቅበት ጊዜ አንበሳ+ እንዲሁም ድብ ይመጣና ከመንጋው መካከል አንድ በግ ነጥቆ ይወስድ ነበር። 35  እኔም ተከትዬው በመሄድ እመታውና በጉን ከአፉ አስጥለው ነበር። ሊያጠቃኝ በተነሳ ጊዜም ጉሮሮውን አንቄ* በመምታት እገድለው ነበር። 36  አገልጋይህ አንበሳውንም ሆነ ድቡን ገድሏል፤ ይህ ያልተገረዘ ፍልስጤማዊም ሕያው በሆነው አምላክ ሠራዊት ላይ ስለተሳለቀ መጨረሻው ከእነሱ እንደ አንዱ ይሆናል።”+ 37  ዳዊትም በመቀጠል “ከአንበሳና ከድብ ጥፍር የታደገኝ ይሖዋ አሁንም ከዚህ ፍልስጤማዊ እጅ ይታደገኛል” አለ።+ በዚህ ጊዜ ሳኦል ዳዊትን “እሺ ሂድ፤ ይሖዋ ከአንተ ጋር ይሁን” አለው። 38  ከዚያም ሳኦል ለዳዊት የራሱን ልብሶች አለበሰው። በራሱም ላይ ከመዳብ የተሠራ ቁር ደፋለት፤ ጥሩርም አለበሰው። 39  በኋላም ዳዊት ሰይፉን በልብሱ ላይ ታጥቆ ለመራመድ ሞከረ፤ ሆኖም ከዚህ በፊት እንደዚህ ዓይነት ትጥቅ ታጥቆ ስለማያውቅ መራመድ አልቻለም። ዳዊትም ሳኦልን “እንዲህ ያሉ ትጥቆችን ታጥቄ ስለማላውቅ እነሱን አድርጌ መራመድ አልቻልኩም” አለው። በመሆኑም ዳዊት ከላዩ ላይ አወለቃቸው። 40  ከዚያም በትሩን በእጁ ያዘ፤ አምስት ድቡልቡል ድንጋዮችንም ከወንዝ* ከመረጠ በኋላ በእረኛ ኮሮጆው ውስጥ ጨመራቸው፤ በእጁም ወንጭፉን+ ይዞ ነበር። ከዚያም ወደ ፍልስጤማዊው ቀረበ። 41  ፍልስጤማዊውም ወደ ዳዊት እየቀረበ መጣ፤ ጋሻ ጃግሬውም ከፊት ከፊቱ ይሄድ ነበር። 42  ፍልስጤማዊውም ዳዊትን ትኩር ብሎ ሲያየው ዳዊት የቀይ ዳማና መልከ መልካም የሆነ አንድ ፍሬ ልጅ+ ስለነበር ናቀው። 43  በመሆኑም ፍልስጤማዊው ዳዊትን “በትር ይዘህ ወደ እኔ የምትመጣው እኔ ውሻ ነኝ?”+ አለው። በአማልክቱም ስም ረገመው። 44  ከዚያም “እስቲ ወደ እኔ ና፤ ሥጋህን ለሰማይ አሞሮችና ለምድር አራዊት እሰጣለሁ” አለው። 45  ዳዊትም መልሶ ፍልስጤማዊውን እንዲህ አለው፦ “አንተ ሰይፍ፣ ጭሬና ጦር+ ይዘህ ትመጣብኛለህ፤ እኔ ግን አንተ በተሳለቅክበት፣+ የእስራኤል ተዋጊዎች አምላክ በሆነው በሠራዊት ጌታ በይሖዋ ስም+ እመጣብሃለሁ። 46  ዛሬ ይሖዋ አንተን በእጄ አሳልፎ ይሰጥሃል፤+ እኔም አንተን ገድዬ ራስህን እቆርጠዋለሁ፤ በዚህ ቀን የፍልስጤማውያንን ሠራዊት ሬሳ ለሰማይ አሞሮችና ለምድር አራዊት እሰጣለሁ፤ በመላው ምድር የሚኖሩ ሰዎችም በእስራኤል አምላክ እንዳለ ያውቃሉ።+ 47  እዚህ የተሰበሰቡትም ሁሉ ይሖዋ የሚያድነው በሰይፍ ወይም በጦር እንዳልሆነ ያውቃሉ፤+ ምክንያቱም ውጊያው የይሖዋ ነው፤+ እሱም ሁላችሁንም በእጃችን አሳልፎ ይሰጣችኋል።”+ 48  ፍልስጤማዊውም ተነስቶ ዳዊትን ለመግጠም ወደ እሱ እየተራመደ መጣ፤ ዳዊትም ፍልስጤማዊውን ለመግጠም ወደ ጦር ግንባሩ እየተንደረደረ ሄደ። 49  ከዚያም ዳዊት እጁን ወደ ኮሮጆው በመስደድ አንድ ድንጋይ አውጥቶ ወነጨፈው። ፍልስጤማዊውንም ግንባሩ ላይ መታው፤ ድንጋዩም ግንባሩ ውስጥ ገብቶ ተቀረቀረ፤ ሰውየውም በአፍጢሙ መሬት ላይ ተደፋ።+ 50  በዚህ ሁኔታ ዳዊት ፍልስጤማዊውን በወንጭፍና በድንጋይ አሸነፈው፤ ዳዊት በእጁ ሰይፍ ባይዝም ፍልስጤማዊውን መትቶ ገደለው።+ 51  ከዚያም ዳዊት እየሮጠ ሄዶ ላዩ ላይ ቆመ። የፍልስጤማዊውንም ሰይፍ+ ከሰገባው ውስጥ በመምዘዝ አንገቱን ቆርጦ ገደለው። ፍልስጤማውያንም ጀግናቸው መሞቱን ሲያዩ ሸሹ።+ 52  በዚህ ጊዜ የእስራኤልና የይሁዳ ሰዎች ተነስተው እየጮኹ ፍልስጤማውያኑን ከሸለቆው+ አንስቶ እስከ ኤቅሮን+ በሮች ድረስ አሳደዷቸው፤ የፍልስጤማውያኑም ሬሳ ከሻአራይም+ አንስቶ እስከ ጌት እና እስከ ኤቅሮን ድረስ በየመንገዱ ወድቆ ነበር። 53   እስራኤላውያን ፍልስጤማውያኑን ከማሳደድ ከተመለሱ በኋላ ሰፈሮቻቸውን በዘበዙ። 54  ዳዊትም የፍልስጤማዊውን ራስ ወደ ኢየሩሳሌም አመጣው፤ የፍልስጤማዊውን የጦር መሣሪያዎች ግን በራሱ ድንኳን ውስጥ አስቀመጣቸው።+ 55  ዳዊት፣ ፍልስጤማዊውን ለመግጠም በሚሄድበት ጊዜ ሳኦል ዳዊትን ተመልክቶ የሠራዊቱን አዛዥ አበኔርን+ “አበኔር፣ ለመሆኑ ይህ የማን ልጅ ነው?”+ አለው። አበኔርም መልሶ “ንጉሥ ሆይ፣ በሕያውነትህ እምላለሁ፣* አላውቅም!” አለው። 56  ንጉሡም “ይህ ወጣት የማን ልጅ እንደሆነ አጣራ” አለው። 57   ስለዚህ ዳዊት ፍልስጤማዊውን ገድሎ ሲመለስ አበኔር ዳዊትን ወስዶ የፍልስጤማዊውን ራስ+ በእጁ እንደያዘ ንጉሡ ፊት አቀረበው። 58  ሳኦልም “አንተ ወጣት፣ የማን ልጅ ነህ?” ሲል ጠየቀው፤ ዳዊትም መልሶ “የቤተልሔም+ ሰው የሆነው የአገልጋይህ የእሴይ+ ልጅ ነኝ” አለው።

የግርጌ ማስታወሻ

ወይም “ረባዳማ ሜዳ።”
ቁመቱ 2.9 ሜትር ገደማ ነበር። ከተጨማሪው መረጃ ላይ ለ14ን ተመልከት።
ወደ 57 ኪሎ ግራም ገደማ ነው። ከተጨማሪው መረጃ ላይ ለ14ን ተመልከት።
ወደ 6.84 ኪሎ ግራም ገደማ ነው። ከተጨማሪው መረጃ ላይ ለ14ን ተመልከት።
ወይም “እገዳደራለሁ።”
አንድ ኢፍ 22 ሊትር ነው። ከተጨማሪው መረጃ ላይ ለ14ን ተመልከት።
ወይም “ረባዳማ ሜዳ።”
ወይም “ማንም ሰው ወኔ አይክዳው።”
ወይም “መንጋጋውን ይዤ።” ቃል በቃል “ጺሙን ጨምድጄ።”
ወይም “ከደረቁ ወንዝ።”
ወይም “በሕያው ነፍስህ እምላለሁ።”