አንደኛ ሳሙኤል 2:1-36

  • የሐና ጸሎት (1-11)

  • ሁለቱ የኤሊ ወንዶች ልጆች የፈጸሙት ኃጢአት (12-26)

  • ይሖዋ በኤሊ ቤት ላይ ያስተላለፈው ፍርድ (27-36)

2  ከዚያም ሐና እንዲህ ስትል ጸለየች፦ “ልቤ በይሖዋ ሐሴት አደረገ፤+ቀንዴም* በይሖዋ ከፍ ከፍ አለ። አፌ በጠላቶቼ ላይ ተከፈተ፣በማዳን ሥራዎችህ ደስ ብሎኛልና።   እንደ ይሖዋ ያለ ቅዱስ ማንም የለም፣ያለአንተ ማንም የለም፤+እንደ አምላካችን ያለ ዓለት የለም።+   በትዕቢት መናገራችሁን ተዉ፤የእብሪት ቃል ከአፋችሁ አይውጣ፣ይሖዋ ሁሉን የሚያውቅ አምላክ ነውና፣+ተግባርን ሁሉ በትክክል የሚመዝን እሱ ነው።   የኃያላን ቀስቶች ተሰባብረዋል፣የተንገዳገዱት ግን ብርታት አግኝተዋል።+   ጠግበው የነበሩት ለምግብ ሲሉ ተቀጥረው ለመሥራት ተገደዱ፤የተራቡት ግን ከእንግዲህ አይራቡም።+ መሃን የነበረችው ሴት ሰባት ልጆች ወለደች፤+ብዙ ወንዶች ልጆች የነበሯት ግን ብቻዋን ቀረች።*   ይሖዋ ይገድላል፤ ሕይወትንም ያድናል፤*ወደ መቃብር* ያወርዳል፤ ከዚያም ያወጣል።+   ይሖዋ ያደኸያል፤ እንዲሁም ያበለጽጋል፤+እሱ ያዋርዳል፤ ከፍ ከፍም ያደርጋል።+   ችግረኛውን ከአቧራ ላይ ያነሳል፤ድሃውንም ከአመድ ቁልል* ላይ ያነሳል፤+ከመኳንንትም ጋር ያስቀምጣቸዋል፤የክብር ወንበርም ይሰጣቸዋል። የምድር ምሰሶዎች የይሖዋ ናቸው፤+ፍሬያማ የሆነችውን ምድር በእነሱ ላይ አስቀምጧል።   እሱ የታማኞቹን እርምጃ ይጠብቃል፤+ክፉዎች ግን በጨለማ ውስጥ ጸጥ እንዲሉ ይደረጋሉ፤+ሰው የበላይ የሚሆነው በኃይሉ አይደለምና።+ 10  ይሖዋ ከእሱ ጋር የሚዋጉትን ያደቃቸዋል፤*+እሱም ከሰማይ ነጎድጓድ ይለቅባቸዋል።+ ይሖዋ እስከ ምድር ዳርቻ ድረስ ይፈርዳል፤+ለንጉሡ ኃይል ይሰጣል፤+የእሱ ቅቡዕ የሆነውንም ቀንዱን* ከፍ ከፍ ያደርጋል።”+ 11  ከዚያም ሕልቃና በራማ ወደሚገኘው ቤቱ ሄደ፤ ልጁ ግን በካህኑ በኤሊ ፊት የይሖዋ አገልጋይ ሆነ።*+ 12  የኤሊ ወንዶች ልጆች ምግባረ ብልሹ ነበሩ፤+ ለይሖዋ አክብሮት አልነበራቸውም። 13  ከሕዝቡ ላይ የካህናቱን ድርሻ በሚቀበሉበት ጊዜ እንዲህ ያደርጉ ነበር፦+ ማንኛውም ሰው መሥዋዕት በሚያቀርብበት ጊዜ ሥጋው እየተቀቀለ ሳለ የካህኑ አገልጋይ ሦስት ጣት ያለው ሹካ ይዞ ይመጣና 14  ሹካውን ወደ ሰታቴው ወይም ወደ ምንቸቱ ወይም ወደ አፍላሉ* ወይም ወደ ባለ አንድ ጆሮው ድስት ይከተዋል። መንሹ ይዞ የሚወጣውንም ካህኑ ለራሱ ይወስድ ነበር። ወደ ሴሎ በሚመጡት እስራኤላውያን ሁሉ ላይ እንዲሁ ያደርጉ ነበር። 15  ሌላው ቀርቶ መሥዋዕቱን የሚያቀርበው ሰው ስቡን ከማቃጠሉ+ በፊት የካህኑ አገልጋይ መጥቶ “ለካህኑ የሚጠበስ ሥጋ ስጠው። ጥሬ ሥጋ ብቻ እንጂ የተቀቀለ ሥጋ ከአንተ አይቀበልም” ይለው ነበር። 16  ሰውየውም “በመጀመሪያ ስቡን ያቃጥሉ፤+ ከዚያ በኋላ የፈለግከውን* ውሰድ” ይለው ነበር። እሱ ግን “አይሆንም፤ አሁኑኑ ስጠኝ፤ ካልሆነ ግን ነጥቄ እወስዳለሁ!” ይለዋል። 17  ሰዎቹ የይሖዋን መባ ያቃልሉ ስለነበር የአገልጋዮቹ ኃጢአት በይሖዋ ፊት እጅግ ታላቅ ሆነ።+ 18  በዚህ ጊዜ ሳሙኤል ገና አንድ ፍሬ ልጅ የነበረ ቢሆንም ከበፍታ የተሠራ ኤፉድ+ ለብሶ* በይሖዋ ፊት ያገለግል ነበር።+ 19  እናቱም ዓመታዊውን መሥዋዕት ለማቅረብ ከባሏ ጋር ስትወጣ እጅጌ የሌለው ትንሽ ቀሚስ እየሠራች በየዓመቱ ታመጣለት ነበር።+ 20  ኤሊም ሕልቃናንና ሚስቱን እንዲህ ሲል ባረካቸው፦ “ለይሖዋ በተሰጠው* ልጅ ምትክ ይሖዋ ከዚህች ሚስትህ ልጅ ይስጥህ” አለው።+ እነሱም ወደ ቤታቸው ተመለሱ። 21  ይሖዋም ሐናን አሰባት፤ እሷም ፀነሰች፤+ ሌሎች ሦስት ወንዶችና ሁለት ሴቶች ልጆችም ወለደች። ብላቴናው ሳሙኤልም በይሖዋ ፊት እያደገ ሄደ።+ 22  በዚህ ጊዜ ኤሊ በጣም አርጅቶ ነበር፤ ሆኖም ወንዶች ልጆቹ በሁሉም እስራኤላውያን ላይ ምን እንደሚያደርጉ+ እንዲሁም በመገናኛ ድንኳኑ መግቢያ ላይ ከሚያገለግሉት ሴቶች ጋር እንደሚተኙ+ አንድም ሳይቀር ሰምቶ ነበር። 23  እሱም እንዲህ ይላቸው ነበር፦ “እንዲህ ያለ ነገር ለምን ታደርጋላችሁ? ሰዎች ሁሉ ስለ እናንተ መጥፎ ነገር ሲናገሩ እሰማለሁ። 24  ልጆቼ፣ ትክክል አይደላችሁም፤ በይሖዋ ሕዝቦች መካከል ሲናፈስ የምሰማው ወሬ ጥሩ አይደለም። 25  አንድ ሰው ሌላውን ቢበድል ሌላ ሰው ይሖዋን ይለምንለት ይሆናል፤* ሆኖም አንድ ሰው ይሖዋን ቢበድል+ ማን ሊጸልይለት ይችላል?” እነሱ ግን የአባታቸውን ቃል ለመስማት ፈቃደኞች አልሆኑም፤ ምክንያቱም ይሖዋ ሊገድላቸው ወስኖ ነበር።+ 26  ይህ በእንዲህ እንዳለ ብላቴናው ሳሙኤል በይሖዋም ሆነ በሰዎች ፊት በአካል እያደገና ይበልጥ ሞገስ እያገኘ ሄደ።+ 27  አንድ የአምላክ ሰው ወደ ኤሊ መጥቶ እንዲህ አለው፦ “ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ ‘የአባትህ ቤት በግብፅ በፈርዖን ቤት በባርነት ያገለግል በነበረበት ጊዜ ራሴን በይፋ ገልጬለት አልነበረም?+ 28  ካህን ሆኖ እንዲያገለግለኝ፣ መሥዋዕት ለማቅረብ ወደ መሠዊያዬ እንዲወጣ፣+ ዕጣን እንዲያጥንና* በፊቴ ኤፉድ እንዲለብስ ከእስራኤል ነገዶች ሁሉ መካከል ተመርጦ ነበር፤+ እኔም እስራኤላውያን* በእሳት የሚያቀርቧቸውን መባዎች በሙሉ ለአባትህ ቤት ሰጠሁ።+ 29  ታዲያ እናንተ በማደሪያዬ እንዲቀርብ ያዘዝኩትን መሥዋዕቴንና መባዬን የናቃችሁት* ለምንድን ነው?+ ሕዝቤ እስራኤል ከሚያመጣው ከእያንዳንዱ መባ ላይ ምርጡን ወስዳችሁ ራሳችሁን በማደለብ ከእኔ ይልቅ ልጆችህን ያከበርከው ለምንድን ነው?+ 30  “‘ስለዚህ የእስራኤል አምላክ የይሖዋ ቃል እንዲህ ይላል፦ “የአንተ ቤትና የአባትህ ቤት ምንጊዜም በፊቴ እንደሚሄዱ ተናግሬ ነበር።”+ አሁን ግን ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ “ይህ ፈጽሞ የማላስበው ነገር ነው፤ ምክንያቱም የሚያከብሩኝን አከብራለሁ፤+ የሚንቁኝ ግን ይናቃሉ።” 31  በቤትህ እስከ ሽምግልና ድረስ በሕይወት የሚቆይ ሰው እንዳይኖር የአንተንም ሆነ የአባትህን ቤት ብርታት* የምቆርጥበት ቀን ይመጣል።+ 32  ለእስራኤል በተደረገው ብዙ መልካም ነገር መካከል በማደሪያዬ ውስጥ ተቀናቃኝ ታያለህ፤+ በቤትህም ዳግመኛ አረጋዊ የሚባል አይገኝም። 33  በመሠዊያዬ ፊት እንዲያገለግል የምተወው የአንተ የሆነ ሰው ዓይኖችህ እንዲፈዙና ለሐዘን እንድትዳረግ* ያደርጋል፤ ከቤትህ ሰዎች መካከል ግን አብዛኞቹ በሰዎች ሰይፍ ይሞታሉ።+ 34  በሁለቱ ልጆችህ በሆፍኒ እና በፊንሃስ ላይ የሚደርሰው ነገር ምልክት ይሆንሃል፦ ሁለቱም በአንድ ቀን ይሞታሉ።+ 35  ከዚያም ለራሴ ታማኝ የሆነ ካህን አስነሳለሁ።+ እሱም ከልቤ ፍላጎት* ጋር የሚስማማ ተግባር ይፈጽማል፤ እኔም ዘላቂ የሆነ ቤት እሠራለታለሁ፤ እሱም እኔ በቀባሁት ፊት ሁልጊዜ ይሄዳል። 36  ከቤትህ የሚተርፍ ሰው ቢኖር የሚከፈለው ገንዘብና ቁራሽ ዳቦ ለማግኘት ሲል መጥቶ ይሰግድለታል፤ ከዚያም “እባክህ፣ ቁራሽ ዳቦ እንዳገኝ በማንኛውም የክህነት ሥራ ላይ መድበኝ” ይላል።’”+

የግርጌ ማስታወሻ

ወይም “ብርታቴም።” የቃላት መፍቻውን ተመልከት።
ቃል በቃል “መነመነች።”
ወይም “ሕያው ያደርጋል።”
ወይም “ሲኦል።” የሰው ልጆችን ሁሉ መቃብር ያመለክታል። የቃላት መፍቻውን ተመልከት።
“ከቆሻሻ መጣያ” ማለትም ሊሆን ይችላል።
“ከይሖዋ ጋር የሚፎካከሩ ይሸበራሉ” ማለትም ሊሆን ይችላል።
ወይም “ብርታቱን።” የቃላት መፍቻውን ተመልከት።
ወይም “ይሖዋን ያገለግል ነበር።”
ትልቅ ድስት።
ወይም “ነፍስህ የጓጓችለትን።”
ቃል በቃል “ታጥቆ።”
በዕብራይስጥ “በውሰት በተሰጠው።”
“አምላክ ይፈርድለታል” ማለትም ሊሆን ይችላል።
ቃል በቃል “የእስራኤል ወንዶች ልጆች።”
“የመሥዋዕት ጭስ እንዲያጨስና” ማለትም ሊሆን ይችላል።
ቃል በቃል “በርግጫ ያላችሁት።”
ቃል በቃል “ክንድ።”
ወይም “ነፍስህ እንድትመነምን።”
ወይም “በልቤ ውስጥና በነፍሴ ውስጥ ካለው።”