አንደኛ ሳሙኤል 9:1-27

  • ሳሙኤል ሳኦልን አገኘው (1-27)

9  የቢንያም ሰው የሆነ ቂስ+ የተባለ አንድ እጅግ ባለጸጋ ሰው ነበር፤ እሱም የቢንያማዊው+ የአፊያ ልጅ፣ የቤኮራት ልጅ፣ የጸሮር ልጅ፣ የአቢዔል ልጅ ነበር።  ይህ ሰው ሳኦል+ የተባለ መልከ መልካም ወጣት ልጅ ነበረው፤ ከእስራኤላውያንም መካከል እንደ እሱ ያለ መልከ መልካም ወንድ አልነበረም፤ እሱም ከትከሻው በላይ ዘለግ ያለ ሲሆን ቁመቱ ከሌሎቹ ሁሉ ይበልጥ ነበር።  የሳኦል አባት ቂስ አህዮቹ* በጠፉበት ጊዜ ልጁን ሳኦልን “እባክህ ከአገልጋዮቹ መካከል አንዱን ይዘህ ሂድና አህዮቹን ፈልጋቸው” አለው።  እነሱም የኤፍሬምን ተራራማ አካባቢና የሻሊሻን ምድር አቋርጠው ሄዱ፤ ሆኖም አህዮቹን አላገኟቸውም። ከዚያም የሻአሊምን ምድር አቋርጠው ተጓዙ፤ አህዮቹ ግን በዚያ አልነበሩም። እነሱም መላውን የቢንያማውያንን ምድር አቋርጠው ሄዱ፤ ይሁንና አህዮቹን አላገኟቸውም።  እነሱም ወደ ጹፍ ምድር መጡ፤ ሳኦልም አብሮት የነበረውን አገልጋዩን “አባቴ ስለ አህዮቹ ማሰቡን ትቶ ስለ እኛ መጨነቅ እንዳይጀምር፣ ና እንመለስ” አለው።+  አገልጋዩ ግን እንዲህ አለው፦ “እነሆ፣ በዚህ ከተማ የሚኖር አንድ የተከበረ የአምላክ ሰው አለ። የሚናገረው ነገር በሙሉ መሬት ጠብ አይልም።+ ስለዚህ ወደዚያ እንሂድ። ምናልባት በየትኛው መንገድ መሄድ እንዳለብን ሊነግረን ይችላል።”  በዚህ ጊዜ ሳኦል አገልጋዩን እንዲህ አለው፦ “መሄዱንስ እንሂድ፤ ግን ለሰውየው ምን ይዘንለት እንሄዳለን? በከረጢታችን ውስጥ የያዝነው ዳቦ እንደሆነ አልቋል፤ ለእውነተኛው አምላክ ሰው ስጦታ አድርገን የምንሰጠው ምንም ነገር የለንም። ታዲያ ምን ብናደርግ ይሻላል?”  አገልጋዩም መልሶ ሳኦልን “እንግዲህ ሩብ ሰቅል* ብር በእጄ አለ። ይህን ለእውነተኛው አምላክ ሰው እሰጠዋለሁ፤ እሱም በየትኛው መንገድ መሄድ እንዳለብን ይነግረናል” አለው።  (ቀደም ባሉት ጊዜያት በእስራኤል ውስጥ አንድ ሰው አምላክን ለመፈለግ ሲሄድ “ኑ፣ ወደ ባለ ራእዩ+ እንሂድ” ይል ነበር። ምክንያቱም በዛሬው ጊዜ ነቢይ የሚባለው ቀደም ባሉት ጊዜያት ባለ ራእይ ይባል ነበር።) 10  ከዚያም ሳኦል አገልጋዩን “የተናገርከው ነገር መልካም ነው። በል ና፣ እንሂድ” አለው። በመሆኑም የእውነተኛው አምላክ ሰው ወደሚገኝበት ከተማ ሄዱ። 11  እነሱም ወደ ከተማዋ የሚወስደውን አቀበት እየወጡ ሳለ ውኃ ለመቅዳት የወጡ ልጃገረዶችን አገኙ። በመሆኑም “ባለ ራእዩ+ እዚህ ነው ያለው?” አሏቸው። 12  እነሱም እንዲህ ሲሉ መለሱላቸው፦ “አዎ እዚህ ነው። እነሆ፣ ከፊታችሁ ነው ያለው! ፈጠን ብላችሁ ሂዱ፣ በዛሬው ዕለት ሕዝቡ ከፍ ባለው ቦታ+ ላይ መሥዋዕት ስለሚያቀርብ+ ወደ ከተማዋ መጥቷል። 13  ልክ ወደ ከተማዋ እንደገባችሁ ለመብላት ወደ ኮረብታው ከመውጣቱ በፊት ታገኙታላችሁ። መሥዋዕቱን የሚባርከው እሱ ስለሆነ ሕዝቡ እሱ ካልመጣ መብላት አይጀምርም። ከዚያ በኋላ የተጋበዙት ይበላሉ። በሉ አሁኑኑ ውጡ፤ ታገኙታላችሁ።” 14  ስለዚህ ወደ ከተማዋ ወጡ። ከተማዋ መሃል ሲደርሱም ሳሙኤል ከእነሱ ጋር ተገናኝቶ ወደ ኮረብታው ለመውጣት ወደ እነሱ እየመጣ ነበር። 15  ይሖዋ፣ ሳኦል ከመምጣቱ ከአንድ ቀን በፊት ለሳሙኤል እንዲህ ብሎት* ነበር፦ 16  “ነገ በዚህ ጊዜ ገደማ ከቢንያም ምድር+ የመጣ አንድ ሰው ወደ አንተ እልካለሁ። አንተም በሕዝቤ በእስራኤል ላይ መሪ አድርገህ ቀባው፤+ እሱም ሕዝቤን ከፍልስጤማውያን እጅ ያድናቸዋል። ምክንያቱም የሕዝቤን መከራ አይቻለሁ፤ ጩኸታቸውም ወደ እኔ ደርሷል።”+ 17  ሳሙኤል፣ ሳኦልን ባየው ጊዜ ይሖዋ “‘ሕዝቤን የሚገዛው* እሱ ነው’ ብዬ የነገርኩህ ሰው ይህ ነው” አለው።+ 18  ከዚያም ሳኦል በሩ መሃል ላይ ወደነበረው ወደ ሳሙኤል ቀርቦ “እባክህ፣ የባለ ራእዩ ቤት የት እንደሆነ ትነግረኛለህ?” አለው። 19  ሳሙኤልም ለሳኦል እንዲህ ሲል መለሰለት፦ “ባለ ራእዩ እኔ ነኝ። ከእኔ ቀድመህ ወደ ኮረብታው ውጣ፤ ዛሬ አብራችሁኝ ትበላላችሁ።+ በማለዳም አሰናብትሃለሁ፤ ማወቅ የምትፈልገውንም ነገር ሁሉ* እነግርሃለሁ። 20  ከሦስት ቀን በፊት ስለጠፉብህ አህዮች አትጨነቅ፤+ ምክንያቱም ተገኝተዋል። በእስራኤል ውስጥ ያለው ምርጥ ነገር ሁሉ የማን ነው? የአንተና የመላው የአባትህ ቤት አይደለም?”+ 21  በዚህ ጊዜ ሳኦል እንዲህ አለው፦ “እኔ ከእስራኤል ነገዶች ሁሉ አነስተኛ ከሆነው ከቢንያም ነገድ የተገኘሁ ቢንያማዊ አይደለሁም?+ ቤተሰቤስ ቢሆን ከቢንያም ነገድ ቤተሰቦች መካከል እዚህ ግባ የሚባል ሆኖ ነው? ታዲያ እንዲህ የምትለኝ ለምንድን ነው?” 22  ከዚያም ሳሙኤል ሳኦልንና አገልጋዩን ወደ መመገቢያ አዳራሹ ይዟቸው ሄደ፤ እነሱንም በተጋበዙት ሰዎች ፊት በክብር ቦታ አስቀመጣቸው፤ ተጋባዦቹም 30 ገደማ ነበሩ። 23  ሳሙኤልም ምግብ የሚያበስለውን ሰው “‘ለይተህ አስቀምጠው’ ብዬ የሰጠሁህን ድርሻ አምጣው” አለው። 24  በዚህ ጊዜ ምግብ የሚያበስለው ሰው ጭኑንና ላዩ ላይ የነበረውን አንስቶ ሳኦል ፊት አስቀመጠው። ሳሙኤልም እንዲህ አለው፦ “ተለይቶ ተቀምጦ የነበረው ፊትህ ቀርቦልሃል። ይህ ለዚህ ጊዜ ብለው ለይተው ያስቀመጡልህ ስለሆነ ብላ። ምክንያቱም ‘እንግዶች ጋብዣለሁ’ ብዬ ነግሬያቸዋለሁ።” በመሆኑም ሳኦል በዚያ ቀን ከሳሙኤል ጋር በላ። 25  ከዚያም ከኮረብታው+ ወደ ከተማው ወረዱ፤ ሳሙኤልም ከሳኦል ጋር በቤቱ ሰገነት ላይ ሲነጋገር ቆየ። 26  እነሱም በማለዳ ተነሱ፤ ጎህ እንደቀደደም ሳሙኤል ሳኦልን ወደ ቤቱ ሰገነት ጠርቶ “በል ተዘጋጅና ላሰናብትህ” አለው። ስለዚህ ሳኦል ተዘጋጀ፤ ከዚያም እሱና ሳሙኤል ወደ ውጭ ወጡ። 27  እነሱም በከተማዋ ዳርቻ ቁልቁል እየወረዱ ሳሉ ሳሙኤል ሳኦልን “አገልጋይህ+ ቀድሞን እንዲሄድ ንገረው” አለው፤ እሱም ቀድሞ ሄደ። ሳሙኤልም “አንተ ግን የአምላክን ቃል እንዳሰማህ እዚሁ ቁም” አለው።

የግርጌ ማስታወሻ

ቃል በቃል “እንስት አህዮቹ።”
አንድ ሰቅል 11.4 ግራም ነው። ከተጨማሪው መረጃ ላይ ለ14ን ተመልከት።
ቃል በቃል “ጆሮውን ከፍቶለት።”
ወይም “ሕዝቤን የሚቆጣጠረው።”
ቃል በቃል “በልብህ ያለውንም ነገር ሁሉ።”