ለቆሮንቶስ ሰዎች የተጻፈ የመጀመሪያው ደብዳቤ 11:1-34

  • “የእኔን አርዓያ ተከተሉ” (1)

  • የራስነት ሥርዓትና ራስን መሸፈን (2-16)

  • የጌታ ራትን ማክበር (17-34)

11  እኔ የክርስቶስን አርዓያ እንደምከተል እናንተም የእኔን አርዓያ ተከተሉ።+  በሁሉም ነገር ስለምታስቡኝና ለእናንተ ያስተላለፍኳቸውን ወጎች አጥብቃችሁ ስለያዛችሁ አመሰግናችኋለሁ።  ይሁንና የወንድ ሁሉ ራስ ክርስቶስ፣+ የሴትም ራስ ወንድ፣+ የክርስቶስ ራስ ደግሞ አምላክ እንደሆነ እንድታውቁ እወዳለሁ።+  ራሱን ሸፍኖ የሚጸልይ ወይም ትንቢት የሚናገር ወንድ ሁሉ የእሱን ራስ ያዋርዳል፤  ራሷን ሳትሸፍን የምትጸልይ ወይም ትንቢት የምትናገር+ ሴት ሁሉ ደግሞ የእሷን ራስ ታዋርዳለች፤ እንዲህ የምታደርግ ሴት ራሷን እንደተላጨች ሴት ትቆጠራለች።  አንዲት ሴት ራሷን የማትሸፍን ከሆነ ፀጉሯን ትቆረጥ፤ ፀጉሯን መቆረጧ ወይም መላጨቷ የሚያሳፍራት ከሆነ ግን ትሸፈን።  ወንድ የአምላክ አምሳልና+ ክብር ስለሆነ ራሱን መሸፈን የለበትም፤ ሴት ግን የወንድ ክብር ናት።  ሴት ከወንድ ተገኘች እንጂ ወንድ ከሴት አልተገኘምና።+  ከዚህም በተጨማሪ ሴት ለወንድ ተፈጠረች እንጂ ወንድ ለሴት አልተፈጠረም።+ 10  ከዚህ የተነሳም ሆነ ለመላእክት ሲባል ሴት በሥልጣን ሥር መሆኗን የሚያሳይ ምልክት በራሷ ላይ ታድርግ።+ 11  ይሁንና በጌታ ተከታዮች ዘንድ ሴት ያለወንድ አትኖርም፤ ወንድም ያለሴት አይኖርም። 12  ሴት ከወንድ እንደተገኘች ሁሉ+ ወንድም የተገኘው በሴት አማካኝነት ነውና፤ ሆኖም ሁሉም ነገሮች የተገኙት ከአምላክ ነው።+ 13  እስቲ እናንተ ራሳችሁ ፍረዱ፦ ሴት ሳትሸፈን ወደ አምላክ ብትጸልይ ተገቢ ይሆናል? 14  ወንድ ፀጉሩን ቢያስረዝም ውርደት እንደሚሆንበት ተፈጥሮ ራሱ እንኳ አያስተምራችሁም? 15  ሴት ግን ፀጉሯን ብታስረዝም ለእሷ ክብር አይደለም? ፀጉሯ የተሰጣት በመሸፈኛ ምትክ ነውና። 16  ይሁን እንጂ ማንም ሰው ሌላ ልማድ መከተል አለብን በሚል ለመከራከር ቢፈልግ እኛም ሆን የአምላክ ጉባኤ ከዚህ የተለየ ልማድ የለንም። 17  ሆኖም ስብሰባችሁ ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ ስለሚያመዝን እነዚህን መመሪያዎች ስሰጣችሁ ላመሰግናችሁ አልፈልግም። 18  በመጀመሪያ ደረጃ፣ በጉባኤ በምትሰበሰቡበት ጊዜ በመካከላችሁ ክፍፍል እንዳለ እሰማለሁ፤ ደግሞም ይህ በተወሰነ መጠን እውነትነት እንዳለው አምናለሁ። 19  በዚህ ሁኔታ በእናንተ መካከል ኑፋቄዎች ብቅ ማለታቸው አይቀርም፤+ ይህም መሆኑ ከእናንተ መካከል ተቀባይነት የሚያገኙት ሰዎች ተለይተው እንዲታወቁ ያስችላል። 20  አንድ ላይ በምትሰበሰቡበት ጊዜ፣ የምትሰበሰቡት የጌታ ራትን+ ለመብላት ነው ለማለት አያስደፍርም። 21  የጌታ ራትን በምትበሉበት ጊዜ አንዳንዶች አስቀድመው የራሳቸውን ራት ስለሚበሉ አንዱ ይራባል ሌላው ደግሞ ይሰክራል። 22  የምትበሉበትና የምትጠጡበት ቤት የላችሁም? ወይስ የአምላክን ጉባኤ በመናቅ ምንም የሌላቸውን ታሳፍራላችሁ? እንግዲህ ምን ልበላችሁ? ላመስግናችሁ? በዚህ ነገርስ አላመሰግናችሁም። 23  እኔ ከጌታ የተቀበልኩትን ለእናንተ አስተላልፌአለሁና፤ ጌታ ኢየሱስ አልፎ በተሰጠበት ሌሊት+ ቂጣ አንስቶ 24  ካመሰገነ በኋላ ቆርሶ “ይህ ስለ እናንተ የሚሰጠውን ሥጋዬን ያመለክታል።+ ይህን ሁልጊዜ ለመታሰቢያዬ አድርጉት” አለ።+ 25  በተጨማሪም ራት ከበሉ በኋላ ጽዋውን+ አንስቶ ልክ እንደዚሁ አደረገ፤ እንዲህም አለ፦ “ይህ ጽዋ በደሜ+ አማካኝነት የሚመሠረተውን አዲሱን ቃል ኪዳን+ ያመለክታል። ከዚህ ጽዋ በጠጣችሁ ቁጥር ይህን ሁልጊዜ ለመታሰቢያዬ አድርጉት።”+ 26  ይህን ቂጣ በበላችሁና ከዚህ ጽዋ በጠጣችሁ ቁጥር ጌታ እስከሚመጣ ድረስ ሞቱን ታውጃላችሁ። 27  እንግዲህ የማይገባው ሆኖ ሳለ ከቂጣው የሚበላ ወይም ከጌታ ጽዋ የሚጠጣ ከጌታ አካልና ደም ጋር በተያያዘ ተጠያቂ ይሆናል። 28  አንድ ሰው የሚገባው እንደሆነ ለማወቅ በቅድሚያ ራሱን ይመርምር፤+ ቂጣውን መብላትና ጽዋውን መጠጣት የሚችለው ይህን ካደረገ ብቻ ነው። 29  ምክንያቱም አካሉ ምን ትርጉም እንዳለው ሳይገነዘብ የሚበላና የሚጠጣ በራሱ ላይ ፍርድ የሚያመጣበትን ነገር መብላትና መጠጣት ይሆንበታል። 30  ከእናንተ መካከል ብዙዎቹ የተዳከሙትና ታማሚ የሆኑት እንዲሁም ጥቂት የማይባሉት በሞት ያንቀላፉት* በዚህ ምክንያት ነው።+ 31  ሆኖም ራሳችንን መርምረን ብናውቅ ኖሮ ባልተፈረደብን ነበር። 32  ይሁን እንጂ በሚፈረድብን ጊዜ፣ ከዓለም ጋር አብረን እንዳንኮነን+ ሲል ይሖዋ* ይገሥጸናል።+ 33  ስለዚህ ወንድሞቼ፣ ይህን ራት ለመብላት በምትሰበሰቡበት ጊዜ እርስ በርሳችሁ ተጠባበቁ። 34  የምትሰበሰቡት ለፍርድ እንዳይሆን የራበው ሰው ካለ እዚያው ቤቱ ይብላ።+ የቀሩትን ጉዳዮች ግን ስመጣ አስተካክላለሁ።

የግርጌ ማስታወሻ

ይህ አባባል በመንፈሳዊ መሞትን ሊያመለክት ይችላል።
ከተጨማሪው መረጃ ላይ ሀ5ን ተመልከት።